በሰው ሰራሽ አስተውሎት ዘርፍ በላቀ ክህሎት ሀገራቸውን የሚያስጠሩ በርካታ ባለተሰጥኦ ወጣቶች እየተፈጠሩ ነው

አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 18/2016(ኢዜአ)፦ በሰው ሰራሽ አስተውሎት በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪና ሀገራቸውን የሚያስጠሩ በርካታ ባለተሰጥኦ ወጣቶች እየተፈጠሩ መሆኑን የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ወርቁ ጋቸና (ዶ/ር ኢ/ር) ገለጹ፡፡

ኢንስቲትዩቱ የታዳጊ ወጣቶችን የቴክኖሎጂና ፈጠራ አቅም ለማሳደግ ከመደበኛ ትምህርታቸው ጎን ለጎን የክረምት ሥልጠና እየሰጠ ይገኛል።

በዘንድሮው ዓመትም ለሶስተኛ ዙር የሰው ሰራሽ አስተውሎት የክረምት ሥልጠና ከመጀመሪያና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች 200 ተማሪዎችን አወዳድሮ ለይቷል፡፡

የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ወርቁ ጋቸና (ዶ/ር ኢ/ር)፤ በሰው ሰራሽ አስተውሎት ዘርፍ በትኩረት መስራት ለሀገር እድገት መሰረት መሆኑን ገልጸዋል።

በመሆኑም ኢንስቲትዩቱ ለዘርፉ እድገት እየሰራ መሆኑን ጠቅሰው ለተማሪዎች ከመደበኛ ትምህርታቸው ባሻገር አዳዲስ እውቀት የሚያገኙበት የተደራጀ የክረምት ስልጠና እየሰጠ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

በመጀመሪያውና ሁለተኛው ዙር ሥልጠና ተሰጥኦዎቻቸውን ወደ ውጤት በመቀየር ከግል ተቋማት ጋር በትብብር መሥራት የሚችሉበት እድል ስለመፈጠሩም አስታውሰዋል።

በመሆኑም የክረምት የታዳጊዎች ስልጠና ኢትዮጵያን በምርምርና ቴክኖሎጂ ዘርፍ ከፍ የሚያደርጉ ዓለምን የሚለውጡ ወጣቶች ይገኛሉ ተብሎ ይጠበቃል ብለዋል፡፡

የሰው ሰራሽ አስተውሎት የክረምት የታዳጊዎች ሥልጠና ኢትዮጵያ በቴክኖሎጂና ፈጠራ ዘርፍ ዓለምን የሚያስጠሩ ባለተሰጥኦ ወጣቶች ባለቤት መሆኗን አሳይቶናል ነው ያሉት፡፡

ወጣቶች የላቀ እውቀትና ሀሳብ እንዳላቸው ገልጸው፤ አቅማቸውን አውጥተው መጠቀም የሚችሉበትን እድል ማመቻቸት ደግሞ የእኛ ድርሻ ነው ብለዋል፡፡

በመሆኑም ለሥልጠናው በዘርፉ የካበተ ልምድ ያላቸው መምህራን፣ ምቹ የቴክኖሎጂ መሳሪያዎች፣ ቤተ ሙከራዎች እና መሰል ግብዓቶች የተሟሉለት ማዕከል መገንባቱን ገልጸዋል፡፡

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም