ሳይንስና ቴክኖሎጂ
በክልሉ መገናኛ ብዙሃን ለልማትና ለሰላም ግንባታ ያላቸውን አስተዋጽኦ ከግምት ያስገባ የተቋማቱ ተደራሽነት ይጠናከራል
Aug 4, 2024 179
ሚዛን አማን ፤ ሐምሌ 28/2016(ኢዜአ)፦ በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል መገናኛ ብዙሃን ለልማትና ለሰላም ግንባታ ያላቸውን አስተዋጽኦ ከግምት ያስገባ የተቋማቱ ተደራሽነት እንደሚጠናከር የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር) አስታወቁ። ምክትል ርዕሰ መስተዳድሩ የደቡብ ራዲዮና ቴሌቪዥን ድርጅት ማሻ ቅርንጫፍ ጣቢያን ዛሬ መርቀው ከፍተዋል።   በምረቃ መርሃ ግብሩ ላይ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር) እንደገለጹት፤ መገናኛ ብዙሃን ሕዝብና መንግስትን ድልድይ ሆኖ በማገናኘት ምትክ የለሽ ሚና ስላለው አገልግሎቱን ለማስፋፋት የክልሉ መንግሥት አበክሮ እየሰራ ይገኛል። በተለይ መገናኛ ብዙሃን ለልማትና ለሰላም ግንባታ ያላቸውን አስተዋጽናኦ የሕዝብን ተጠቃሚነት የሚያስጠብቅ በመሆኑ የሚዲያ ተቋማትን ተደራሽነትን የማጠናከር ስራን የክልሉ መንግሥት እየሰራ መሆኑን ጠቁመው በሸካ ዞን የተከፈተው ጣቢያም የዚሁ እንቅስቃሴ አካል መሆኑን አስረድተዋል። የክልሉ ሚዲያ ኔትዎርክ መቋቋሙን ጠቅሰው በክልሉ ውስጥ የሚገኙ መገናኛ ብዙሃንን በቴክኖሎጂ ለማብቃት ጥረት እንደሚደረግም አስታውቀዋል። መገናኛ ብዙሃን ባሉበት አካባቢ ብቻ ሳይገደቡ ሀገር አቀፍ እና ዓለም አቀፍ ተደራሽነታቸው እንዲጎላ አስፈላጊውን ግብዓት እና የሰው ኃይል በማሟላት መንቀሳቀስ እንዳለባቸው አመልክተዋል። በክልሉ ውስጥ እየሠሩ ያሉ መገናኛ ብዙሃን የቱሪዝም ሀብትን በማስተዋወቅና መልካም እሴቶችን በማጉላት የሕዝቦችን አብሮነት በሚያጠናክር መልኩ እንዲሠሩም አሳስበዋል። የክልሉ መንግስት ዋና ተጠሪ አቶ ፀጋዬ ማሞ በበኩላቸው መገናኛ ብዙሃን ኅብረተሰቡ ያለውን እምቅ የተፈጥሮ ሀብት ወደ ኢኮኖሚ መቀየር የሚችልበትን መንገድ ማመላከት ላይ ትኩረት አድርገው ሊሰሩ ይገባል ብለዋል። መገናኛ ብዙሃኑ የመልካም አስተዳደር እጥረቶችን ተከታትለው በመዘገብ ችግር ፈቺ ተቋም ለመሆን ጥረት ማድረግና የአካባቢውን የመለወጥ ተስፋን ተደራሽ የማድረግ ኃላፊነት እንዳለባቸውም አመልክተዋል። የማሻ ራዲዮ ጣቢያ ሥራ አስኪያጅ አቶ ታምሩ ጎዱ ከክልሉ መንግስት በተገኘ የ25 ሚሊዮን ብር ድጋፍ የስቱዲዮ ግብዓት በሟሟላት በአጭር ጊዜ ውስጥ አገልግሎት መጀመር መቻሉን ጠቅሰዋል። ዛሬ የተመረቀው የማሻ ኤፍ ኤም 103 ነጥብ 8 ራዲዮ ጣቢያ አማርኛን ጨምሮ በሸካ ዞን ውስጥ ባሉ የሸክኛ እና መዠንግርኛ ቋንቋዎች መረጃን ለማኅበረሰቡ ተደራሽ እንደሚያደርጉም አመላክተዋል።
ከ2017 ዓ.ም ጀምሮ ተቋማት ንብረት የማስወገድ ስራቸውን በኤሌክትሮኒክስ ስርዓት ብቻ ያካሒዳሉ - ባለስልጣኑ
Aug 3, 2024 344
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 27/2016(ኢዜአ)፦ ከ2017 ዓ.ም ጀምሮ ተቋማት ንብረት የማስወገድ ስራቸውን በኤሌክትሮኒክስ ስርዓት ብቻ እንደሚያካሒዱ የመንግስት ግዢና ንብረት ባለስልጣን አስታወቀ። የመንግስት ግዢና ንብረት ባለስልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር ወልደአብ ደምሴ፤ ለኢዜአ እንደገለጹት የመንግሥት ግዥና አስተዳደር ሥርዓትን ዘመናዊ ከማድረግ አንፃር አበረታች ውጤቶች ተመዝግበዋል። በአሁኑ ወቅትም የከፍተኛ ትምህርት ተቋማትን ጨምሮ በ169 ተቋማት የኤሌክትሮኒክ ግዥ ስርዓት በሙከራ ደረጃ እየተተገበረ እንደሚገኝ ተናግረዋል። ይሁን እንጂ የንብረት ማስወገድ ተግባሩ አሁንም በዘመናዊ ቴክኖሎጂ የተደገፈ ባለመሆኑ ውጤታማነቱ በቂ አለመሆኑን ጠቅሰዋል። ለተቋማት የግዥ ስርዓት እንዲያገለግል የለማው (e-GP) የተሰኘው ቴክኖሎጂ ከግዥ ስራው ጎን ለጎን የንብረት ማስወገድ ተግባሩንም ያካተተ በመሆኑ ዘርፉን በማዘመን ረገድ ጉልህ አስተዋጽኦ ያበረክታል ብለዋል። በመሆኑም ከ2017 ዓ.ም ጀምሮ ተቋማት ንብረት የሚያስወግዱበት መንገድ በዚሁ ቴክኖሎጂ በተደገፈ አሰራር ብቻ እንደሚሆን አስታውቀዋል። ሌላው ሰኔ 6 ቀን 2016 ዓ.ም የጸደቀው የመንግስት ግዥና ንብረት አስተዳደር አዋጅ የተቋሙን የአሰራር ስርዓት የሚያዘምንና የሚያቀላጥፍ በመሆኑ ከ2017 ዓ.ም ጀምሮ ሙሉ በሙሉ ወደ ትግበራ ይገባል ብለዋል። አዋጁ በዋናነት ሶስት ዋና ዋና ጉዳዮችን ያካተተ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ በዚህም በዲጂታል ቴክኖሎጂ የታገዘ የግዥና ንብረት ማስወገድ አሰራር መተግበር፣ ለሀገር ውስጥ አምራቾችና ምርት ቅድሚያ የሚሰጥ፣ መልሶ በመጠቀም ሒደት ከብክለት የጸዳ አረንጓዴ የማስወገድ ስርዓትን እውን የሚያደርግ እንደሆነም ጠቅሰዋል። በዚህ ሒደት በተለይም የሀገር ውስጥ አምራቾችን ተጠቃሚነት ከማረጋገጥ ባለፈ ሴቶችንና አካል ጉዳተኞችን የሚያበረታታ መሆኑን አስታውቀዋል፡፡ በተጨማሪም ለዜጎች ሰፊ የስራ እድል በመፍጠር ረገድ አበርክቶው የጎላ ነው ብለዋል። የጸደቀው አዋጅ የተቋሙን የአሰራር ስርዓት በማሻሻል በዘርፉ የሚፈጠሩ የመልካም አስተዳደር ችግሮችን እንደሚያቃልልም ገልጸዋል። አዋጁን ተከትሎ የሚወጡ የአሰራር መመሪያዎች መዘጋጀታቸውን ገልጸው ከ2017 በጀት ዓመት ጀምሮ የተቋሙ አሰራር ሙሉ በሙሉ በአዲሱ አዋጅ ላይ ተመስርቶ የሚከናወን መሆኑን አስታውቀዋል።
የኤሌክትሮኒክ ፓስፖርት ለማስጀመር የቅድመ ምዝገባና ማረጋገጫ ሂደት ተጀመረ
Aug 3, 2024 203
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 27/2016(ኢዜአ)፦የኤሌክትሮኒክ ፓስፖርት ለማስጀመር የቅድመ ምዝገባና ማረጋገጫ ሂደት መጀመሩን የኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት አስታወቀ። ኢትዮጵያ በቀጣይ ዓመት ተግባራዊ ለማድረግ ያቀደችውን የኤሌክትሮኒክ ፓስፖርት አለማቀፍ ተቀባይነት እንዲኖረው ለማስቻል ያለመ ምክክር ከአለማቀፉ የሲቪል አቪዬሽን ድርጅት ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች ጋር ተካሂዷል። በኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር ወይዘሮ ሰላማዊት ዳዊት የተመራ ልዑክ በካናዳ ሞንትሪያል ከአለማቀፉ የሲቪል አቪዬሽን ድርጅት ዋና ዳይሬክተር ጁዋን ካርሎስ ሳላዛር ጋር በመገናኘት ምክክር አድርገዋል። ዋና ዳይሬክተሯ በዚህ ወቅትም ኢትዮጵያ በአቪዬሽን ዘርፍ የዳበረ ልምድ ያላትና አለምን በአገልግሎት እያስተሳሰረ ያለ ግዙፍ የአየርመንገድ ባለቤት መሆኗን አስታውሰዋል። አለማቀፉ የአቪዬሽን ድርጅት ከጉዞ ሰነድ የደህንነት ስራዎች ጋር በተያያዘ እያደረገ ላለው ድጋፍ ዋና ዳይሬክተሯ ምስጋና አቅርበዋል። ድርጅቱ በቀጣይም ኢትዮጵያ ወደ ኤሌክትሮኒክ ፓስፖርት ስርዓት በምታደርገው የቴክኖሎጂ ሽግግር ላይ የአቅም ግንባታ ስልጠናን ጨምሮ ልዩ ልዩ ድጋፎች እንዲያደርግ ወይዘሮ ሰላማዊት ጠይቀዋል። ዋና ዳይሬክተር ጁዋን ካርሎስ በበኩላቸው ኢትዮጵያ ወደ ኤሌክትሮኒክ ፓስፖርት ስርዓት ለመግባት ያሳለፈችውን ውሳኔ በማድነቅ በቀጣይ ተቋማቸው የማይቋረጥ ድጋፍ እንደሚያደርግ አረጋግጠዋል። ልዑኩ ከዚህ በተጨማሪ በየብስ የድንበር ቁጥጥር ላይ ተግባራዊ የሚደረገው ቴክኖሎጂ ከአለማቀፉ የሲቪል አቪዬሽን ድርጅት ደረጃ ጋር የተጣጣመ መሆኑን ለማረጋገጥ ከሚመለከታቸው የተቋሙ ሃላፊዎች ጋር ምክክር ተካሒዷል። በቀጣይ ቀናትም ተመሳሳይ ምክክሮች እንደሚካሄዱ ከኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
በኢትዮጵያ አገልግሎት አሰጣጥን ለማዘመንና ምርታማነትን ለማሳደግ ለቴክኖሎጂ ልማት ትኩረት ተሰጥቷል - ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ 
Aug 1, 2024 499
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 25/2016(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ የመንግሥት አገልግሎት አሰጣጥን ለማዘመንና ምርታማነትን ለማሳደግ ለቴክኖሎጂና ለሰው ኃይል ልማት ትኩረት መሰጠቱን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ የአማራ ክልል ውሃና ኢነርጂ ቢሮ ያለማቸውን የንብረት፣ የሰው ኃይልና የፕሮጀክት አስተዳደር የዲጂታል ስርዓትን መርቀው ስራ አስጀምረዋል። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ፥ ኢትዮጵያን ከልመና ለማላቀቅና የአፍሪካ የብልፅግና ተምሳሌት ለማድረግ ለግብርና፣ ኢንዱስትሪ፣ ማዕድን፣ ቱሪዝምና የኢንፎርሜሽን ኮሙኒኬሽን ቴክኖሎጂ ዘርፍ ትኩረት መሰጠቱን አንስተዋል። የአማራ ክልል በግብርናው መስክ ለሀገር ዕድገት ትልቅ አበርክቶ እንዳለው ገልጸዋል።   በቱሪዝም ዘርፉም ከነባር ቅርሶች ባሻገር እንደጎርጎራ ያሉ ውብ መዳረሻዎች መገንባታቸው ለዘርፉ ዕድገት ወሳኝ ነው ብለዋል። በቴክኖሎጂ ዘርፍ የአገልግሎት አሰጣጥ ስርዓትን በማዘመን ለህዝቡ ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት እየተሠራ እንደሆነም አንስተዋል። ከዚህ አኳያ የአማራ ክልል ውሃና ኢነርጂ ቢሮ የንብረት፣ የሰው ኃይልና የፕሮጀክት አስተዳደርን ለማዘመንና ስራን ውጤታማ ለማድረግ ያስጀመራቸው የአይሲቲ መሠረተ ልማቶች የሚያበረታቱ ናቸው ብለዋል። የውሃ ፕሮጀክቶችን አፈጻጸም በአግባቡና በግልፅ ለመምራት የተጀመረው የዲጂታል ስርዓት አበረታች ስለመሆኑ ገልጸዋል። የዲጂታል ዘርፉን በአግባቡ የሚመራና የሚያስፈጽም የሰው ኃይል ግንባታ ትኩረት ሊሰጠው እንደሚገባ ተናግረዋል። በተለይም የቴክኖሎጂ መሠረተ ልማቱን ከዘመኑ ዕድገትና ለውጥ አኳያ በየጊዜው ማሻሻል አስፈላጊ ነው ብለዋል። የለሙ መሠረተ ልማቶችን ከዘራፊዎችና ከሳይበር ጥቃት መከላከል የግድ እንደሆነም ጠቁመዋል። ከሌሎች ተቋማት ጋር የተናበበ አገልግሎትን መዘርጋትም አስፈላጊ መሆኑን ጠቅሰዋል። ቴክኖሎጂ አሰራርን ለማዘመንና አገልግሎትን ለማፋጠን ጉልህ ሚና እንዳለው በመግለጽ ይህንን በውጤታማነት ለመጠቀም ለሰው ኃይል ግንባታ ትኩረት መስጠት ይገባል ነው ያሉት። የውሃና ኢነርጂ ቢሮ በቴክኖሎጂ ለተደገፈ ዘመናዊ አሰራር ያሳየው ተነሳሽነት ተስፋ ሰጪ ነው ብለዋል። የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ፥ የኢኮኖሚያችን አንዱ ምሰሶ የቴክኖሎጂ ልማት ነው ብለዋል። ከዚህ አኳያ የውሃና ኢነርጂ ቢሮ ያስጀመራቸው የዲጂታል አገልግሎቶች በተለይ የህዝብ የአገልግሎት እርካታን ለማሻሻል የጎላ አበርክቶ እንደሚኖራቸው ተናግረዋል። ቴክኖሎጂው በአግባቡ ውጤት እንዲያመጣ የሰው ኃይል ሙያዊነት እውቀትና ስነምግባር ላይ ትኩረት መስጠት ያስፈልጋል ብለዋል። መሰል የዲጂታል አገልግሎት ፕሮጀክቶችን በዘላቂነት ችግሮችን መፍታት እንዲችሉ መሥራት ያስፈልጋል ብለዋል። የዲጂታል አገልግሎቱ የህዝብን ቅሬታ የፈታ መሆኑን በየጊዜው መፈተሽ ወሳኝ እንደሆነ ተናግረዋል። በ2017 በሁሉም ዘርፎች ዲጂታላይዜሽንን ለመተግበር መስራት እንደሚገባም አንስተዋል።  
የኤሌክትሮኒክ የመንግሥት ግዥ ሥርዓትን ወደ ክልሎችና ከተማ መስተዳደሮች ለማስፋት በቅንጅት እየተሰራ ነው 
Aug 1, 2024 205
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 25/2016(ኢዜአ)፦ በፌዴራል ደረጃ ተግባራዊ እየተደረገ ያለውን ኤሌክትሮኒክ የመንግሥት ግዥ ሥርዓትን ወደ ክልሎችና ከተማ መስተዳደሮች ለማስፋት እየተሰራ መሆኑን የመንግሥት ግዥና ንብረት ባለሥልጣን ገለጸ። ባለሥልጣኑ የ2016 በጀት ዓመት አፈጻጸም በመገምገም ቀጣይ አቅጣጫ ላይ ተወያይቷል። የባለሥልጣኑ ዋና ዳይሬክተር መሰረት መስቀሌ፤ በበጀት ዓመቱ የመንግሥት ግዥና አስተዳደር ሥርዓትን ዘመናዊ በማድረግ ረገድ የተከናወኑ ተግባራት አበረታች መሆናቸውን ገልፀዋል። በኦዲት ፍተሻ፣ የተገልጋይ እርካታን በማረጋገጥ፣ የተቋሙን አዳዲስ የአሠራር ሥርዓቶችን በማስተዋወቅና ቅንጅታዊ አሠራርን በማረጋገጥም መልካም ጅምሮች እንዳሉ አንስተዋል። በዋናነት የኤሌክትሮኒክ ግዥ ሥርዓትን ከማጠናከር አኳያ በአሁኑ ወቅት ከፍተኛ የትምህርት ተቋማትን ጨምሮ በ169 ተቋማት ተግባራዊ እየተደረገ መሆኑን አብራርተዋል።   ይህ አሠራር የኔትዎርክ መሠረተ-ልማት አቅርቦት አነስተኛ መሆንና በዘርፉ የሰው ኃብት አቅም ውስንነት የተስተዋለበት በመሆኑ አሠራሩ ላይ ክፍተቶች እንዳሉበት አብራርተዋል። በመሆኑም መሠረተ-ልማቱን ካለማው ተቋም ጋር በመተባበር ይበልጥ የማዘመን ሥራው ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ጠቁመው፤ በቀጣይ ሁሉም ተቋማት በቴክኖሎጂው እንዲጠቀሙ ይደረጋል ብለዋል። በባለሥልጣኑ የዕቅድና ስትራቴጂክ ዳይሬክተር ሉዋም አስፋው በፌዴራል ደረጃ ተግባራዊ እየተደረገ የሚገኘውን ኤሌክትሮኒክ የመንግሥት ግዥ ወደ ክልሎችና ከተማ መስተዳድሮች ለማስፋትም በቅንጅት እየተሰራ መሆኑን አመላክተዋል።   የኤሌክትሮኒክ ግዥ ሥርዓት ሙከራ ከተደረገባቸው መካከል አዲስ አበባ፣ ኦሮሚያና ሲዳማ ክልሎች ተጠቃሽ መሆናቸውንም አብራርተዋል። በፌዴራል መሥሪያ ቤቶች የተሽከርካሪ ሥምሪትና አስተዳደርን ማዘመን የሚያስችል የኢ-ፊሊት ማኔጀመንት ሶፍትዌር በማበልፀግ በተመረጡ 13 የፌዴራል ተቋማት ላይ በ2017 በጀት ዓመት የሙከራ ሥራ ተግባራዊ ማድረግ የሚያስችል ዝግጅት ስለመጠናቀቁም አንስተዋል። በቀጣይ በትኩረት ከሚከናወኑ ተግባራት መካከል የተቋማት የግዥ ሥርዓትን ሙሉ በሙሉ ኤሌክትሮኒክ ማድረግ፣ የተሽከርካሪዎች የነዳጅ ብክነት መቀነስ፣ አዳዲስ የአሠራር ማሻሻያዎችን ፈጥኖ ተግባራዊ ማድረግ ተጠቃሽ ናቸው ብለዋል።        
የተማሪዎች ምዘገባ በቴክኖሎጂ መታገዙ ጊዜን ከመቆጠብ ባለፈ የተደራጀ መረጃ ለመያዝ አጋዥ ነው
Aug 1, 2024 187
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 25/2016(ኢዜአ)፦ የተማሪዎች ምዘገባ በቴክኖሎጂ መታገዙ ጊዜን ከመቆጠብ ባለፈ የተደራጀ መረጃ ለመያዝ አጋዥ መሆኑን ወላጆችና የትምህርት ባለሙያዎች ተናገሩ፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮ ከአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ኢኖቬሽን እና ቴክኖሎጂ ቢሮ ጋር በጋራ በመሆን የተማሪዎችን ምዝገባ በኦን ላይን ለማካሄድ የኢ ስኩል ቴክኖሎጂን ተግባራዊ አድርጎ ወደ ስራ ገብቷል፡፡ በዚህም በመዲናዋ የሚገኙ ሁሉም የመንግስት ትምህርት ቤቶች ተማሪዎችን ኦንላይን በመመዝገብ ላይ ይገኛሉ፡፡ ኢዜአ የተማሪዎች ምዝገባን በኦንላይን እየሰጡ ባሉ ትምህርት ቤቶች ቅኝት በማድረግ ወላጆችና ርዕሳነ መምህራንን አነጋግሯል ። ወይዘሮ አልማዝ አስረስ የተባሉ ወላጅ ቀደም ሲል የነበረው የተማሪዎች ምዝገባ ወላጆችን ውጥረት ውስጥ የሚከትና ምልልስ የበዛበት እንደነበር አስታውሰዋል፡፡ የተማሪዎች ምዝገባ በዘመናዊ አሰራር መደገፉ ጊዜና ገንዘብን ለመቆጠብ ከማገዙ ባለፈ ያጋጥማቸው የነበረውን እንግልት እንዳስቀረላቸው የተናገሩት ወይዘሮ ሰናይት ወንድሙ የተባሉ ወላጅ ናቸው።   በቴክኖሎጂ የታገዘው የምዝገባ ሂደት ወላጆች ሰዓታቸውን በአግባቡ እንዲጠቀሙ የሚያደርግ በመሆኑ በቀጣይም ተጠናክሮ ሊቀጥል ይገባል ያሉት አስር አለቃ አዚዝ አደምኑር ናቸው። የአለም ብርሃን የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤት ርዕሰ መምህር አቶ ይድነቃቸው አሰፋ፤በበኩላቸው ቀደም ሲል የተማሪዎች ምዝገባ ዲጂታል ካለመሆኑ ጋር ተያይዞ የተማሪዎችን መረጃ በተደራጀና በአግባቡ ለመያዝ በርካታ ተግዳሮቶች ነበሩብን ብለዋል።   የተጀመረው ዘመናዊ አሰራር መረጃዎች ዘመኑ ባፈራው ቴክኖሎጂ እንዲያዙ በማድረግ ለትምህርት ቤቶች ቀልጣፋ አገልግሎት አሰጣጥ መሰረት የሚጥል ነው ሲሉ ተናግረዋል። በተጨማሪም መንግስት ለተማሪዎች ለሚያቀርባቸው አገልግሎቶች የሚመድበው በጀት ለታለመለት አላማ መዋሉን ለማረጋገጥ የሚያስችል እንደሆነ ጠቁመዋል።   ቴክኖሎጂው የወረቀት አሰራርን በማስቀረት የሰው ኃይል ብክነትን ከመቀነስ ባለፈ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታን ያነገበ ነው ያሉት ደግሞ የአጼ ፋሲል አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ምክትል ርዕሰ መምህር አቶ ኃይለገብርኤል አንዱአለም ናቸው።   የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ ወንድሙ ዑመር ቴክኖሎጂውን በመጠቀም የተማሪዎችን ውጤትና ስነ ምግባር ለመከታታል እንደሚቻል ተናግረዋል፡፡ በተጨማሪም ቴክኖሎጂው የተማሪዎችን አጠቃላይ መረጃ አጣምሮ የያዘ በመሆኑ ለትምህርት ቤት ፣ለወላጆችና ተማሪዎች እፎይታን የሚሰጥ እንደሆነ አብራርተዋል።    
የመገናኛ ብዙሃን ባለሙያዎች የህዝብ እና የሀገር ጥቅምን በማስቀደም ለዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ሚናቸውን መወጣት ይጠበቅባቸዋል
Jul 31, 2024 231
አሶሳ ፤ ሐምሌ 24/2016(ኢዜአ)፦የመገናኛ ብዙሃን ባለሙያዎች የህዝብ እና የሀገር ጥቅምን በማስቀደም ለዴሞክራሲ ስርዓት መጎልበት ሚናቸውን መወጣት እንደሚጠበቅባቸው ተገለጸ። የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙሃን ምክር ቤት ከባለድርሻ አካላት ጋር በመቀናጀት በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ለሚገኙ ጋዜጠኞች ያዘጋጀው ስልጠና ዛሬ በአሶሳ ተጀምሯል።   የኢትዮጵያ ሚዲያ ካውንስል ስራ አስፈጻሚ አባል አቶ ሞላልኝ መለሰ በወቅቱ እንዳሉት፤ ምክር ቤቱ የመገናኛ ብዙሃንን አቅም በማጠናከር ረገድ የድርሻውን እየተወጣ ነው። መገናኛ ብዙሃን ህጋዊነትን ተከትለው ከሰሩ ለአገር ጥቅም ያላቸው ሚና የጎላ መሆኑን ገልጸው፤ በአንጻሩ የመገናኛ ብዙሃን የይዘት አቀራረብ አገር ሊጎዳ እንደሚችልም አስረድተዋል። በተለይም 'ስፖንሰር ሺፓች' እና መረጃ ሰጪ ምንጮች መገናኛ ብዙሃንን በመጠቀም ድብቅ ዓላማቸውን ለማሳካት የሚያደርጉት ጥረት ሊኖር ስለሚችል ትኩረት የሚሻ ጉዳይ መሆኑን አብራርተዋል። ምክር ቤቱም የአሰራር ስነ ምግባር ደንብ አዘጋጅቶ የምክር ቤቱ አባል በሆኑ ማህበራዊና ዲጂታል ሚዲያዎችን ጨምሮ በመገናኛ ብዙሃን እንዲተገበር የሚያደርገው ጥረት እንዳለም ጠቅሰዋል። በመሆኑም የመገናኛ ብዙሃን ባለሙያዎች በዘገባቸው ወቅት የህዝብ እና የአገር ጥቅምን በማስቀደም ለዴሞክራሲ ስርዓት መጎልበት ሚናቸውን ማጠናከር እንዳለባቸው አስገንዝበዋል። መገናኛ ብዙሃን መፍትሄን መሠረት ያደረጉ ዘገባዎችን በመስራት ለማህበረሰብ ደህንነት ሃላፊነታቸው መወጣት እንዳለባቸው ገልጸዋል። በተለይም መገናኛ ብዙሃን ባለሙያዎቹ ለኤዲቶሪያል ፖሊሲያቸው፣ ለህገ መንግስቱ እና ለሌሎችም ህጎች ተገዢ መሆን እንዳለባቸው ጠቅሰው፤ በዘገባቸው ላይ የህዝብን ምላሽ ማዳመጥ እንዳለባቸውም አስገንዝበዋል። እንዲሁም ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በርካታ የመገናኛ ብዙሃን ባለሙያዎች የሌላውን ዘገባ በተወሰነ ደረጃ ቀባብቶ በማሳመር የራሳቸው አስመስለው ማቅረብ እየታየ በመሆኑን ሊስተካከለ እንደሚገባም ጠቅሰዋል። በስልጠናው በክልሉ የሚገኙ 40 የሚጠጉ የመገናኛ ብዙሃን ባለሙያዎች እየተሳተፉ ሲሆን፤ ስልጠናው እስከ ነገ ይቀጥላል።    
ከወዳደቁ ቁሳቁስ አነስተኛ የእርሻ ትራክተር ሰርቶ ለአገልግሎት ያበቃው የሽሬ እንዳስላሴው ወጣት
Jul 31, 2024 178
ሸሬ እንዳስላሴ፤ ሐምሌ 24/2016(ኢዜአ)፦ በችግር ፈቺ የፈጠራ ስራ የተሰማራው ወጣት የወዳደቁ ቁሳቁስን በመጠቀም አነስተኛ የእርሻ ትራክተር ሰርቶ ለአገልግሎት ማብቃቱ ተገለፀ። ወጣቱ ከዚህ ቀደም አንድ ሄሊኮፕተር ሰርቶ ለሶስት ደቂቃ በአየር ላይ እንድትንሳፈፍ በማድረግ በአገር አቀፍ የፈጠራ ስራ ውድድር ተሸላሚ መሆንም ችሏል። ሥራ ፈጣሪው ወጣት ዕበ ለገሰ ይባላል። የሽሬ እንዳስላሴ ከተማ ነዋሪ ነዉ። የሽሬ እንዳስላሴ ከተማ ባዘጋጀው የፈጠራና የሥራ እድል ፈጠራ ውድድር ተሳታፊ ለመሆን ከወዳደቁ ቁሳቁስ የሰራትን አነስተኛ የእርሻ ትራክተር ይዞ በመቅረብ በውድድሩ ከተሳተፉት ስምንት ስራ ፈጣሪ ወጣቶች ቀዳሚ በመሆን የገንዘብ ተሸላሚ ሆኗል። የእርሻ ትራክተሯ ከሞተርዋ ውጭ ሌላ አካልዋ ከወዳደቁ ብረታ ብረቶችና የፕላስቲክ ውጤቶች የተሰራች መሆኑን የተናገረው ወጣቱ በአራት ሰዓት አንድ ሄክታር ማሳ የማረስ አቅም እንዳላትም አስረድቷል። ባለ ትዳርና የሁለት ልጆች አባት የሆነው የ36 ዓመቱ ስራ ፈጣሪ ወጣት የእርሻ ትራክተሯን 56 ሺህ ብር ወጪ በማድረግ ለአገልግሎት ማብቃቱን ተናግሯል። የትራክተር ስራውን በፕሮጀክት መልክ በማስቀጠልና የፈጠራ ስራውን በማስፋት በቋሚነት ትራክተር እየገጣጠመ ለገበያ ለማቅረብ የባለ ድርሻ አካላት ድጋፍ ወሳኝ መሆኑን ገልጿል። ዘመናዊ የግብርና አሰራርን ተግባራዊ በማድረግ የአርሶ አደሩን ምርትና ምርታማነት ለማሳደግ መሰል የፈጠራ ስራዎች ጠቀሜታቸው የጎላ ከመሆኑም ባሻገር ለሌሎች የስራ ዕድል ተጠቃሚ ስለሚያደርግም የሚመለከታቸው ባለ ድርሻ አካላት ድጋፍ ሊያደርጉ እንደሚገባም ወጣቱ በአፅንኦት ጠይቋል። በአሁኑ ወቅት ትራክተሯ በሰው ጉልበት እየተገፋች የምታርስና በቤንዚን የምትሰራ ብትሆንም በየጊዜው እየተሻሻለች እንደምትሰራም ወጣቱ ተናግሯል። በአራት ጥማድ በሬዎች አንድ ቀን ሙሉ የሚፈጀውን ስራ ትራክተሯ በአራት ሰዓት ስታጠናቅቅ ግርምትን እንዳጫረባቸው በአካል ተገኝተው የተመለከቱ አርሶ አደሮች ገልፀዋል። በአክሱም ዩኒቨርሲቲ የሽሬ ካምፓስ ዲን ዶክተር ዳዊት ማሞ በበኩላቸው የወጣቱ የፈጠራ ስራ የሆነችዉ ይህቺ አነስተኛ የእርሻ ትራክተር አስገራሚና በእጅጉ የሚበረታታ መሆኑን አስተያየታቸውን ሰጥተዋል። የፈጠራ ስራው እንዲሰፋም የባለ ድርሻ አካላት ሚና ጉልሀ መሆኑን ገልፀው ለወጣቱ ድጋፍ ሊያደርጉለት እንደሚገባም አመልክተዋል። የአክሱም ዩኒቨርሲቲ ሽሬ ካምፓስም አስፈላጊውን የቴክኒክ ድጋፍ እንደሚያደርግም አረጋግጠዋል። ወጣት ዕበ የኢትዮጵያ ሲቪል አቪዬሽን ባለስልጣን ባዘጋጀው የሳይንስና ቴክኖሎጁ የፈጠራ ውድድር ላይ ከተለያዩ ቁሳቁስ የሰራትን ሄሊኮፕተር ይዞ በመቅረብ የውድድሩ አሸናፊ ከመሆኑም በላይ የአንድ መቶ ሺህ ብር ተሸላሚ ሆኖ እንደነበርም ይታወሳል።
የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የመማር ማስተማርና ምርምር ሥራቸውን በዲጂታል ሥርዓት የመደገፉ ሥራ ተጠናክሮ መቀጠል አለበት
Jul 27, 2024 444
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 20/2016(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የመማር ማስተማርና ምርምር ሥራቸውን በዲጂታል ሥርዓት የመደገፉ ሥራ ይበልጥ ትኩረት ሊሰጠው እንደሚገባ ተጠቆመ። 13ኛው የመንግሥት ዩኒቨርስቲዎች ጉባኤ "ዲጂታል ቴክኖሎጂ ለከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ሽግግር ያለው እድልና ፈተና" በሚል መሪ ኃሳብ ዛሬ ተካሂዷል።   በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የጥራት ማረጋገጥ ዳይሬክተር ፕሮፌሰር አበባው ይርጋ በዚሁ ጊዜ፤ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የዲጂታል ሽግግር እድሎችና ፈተናዎች ላይ ያተኮረ ጽሁፍ አቅርበዋል። ዲጂታል ቴክኖሎጂ አሁን የደረሰበትን ደረጃና ለከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የዕለት ተዕለት ሥራቸውን ከማቀላጠፍ አኳያ ያለውን ፋይዳ በጹሁፋቸው ዳሰዋል። በኢትዮጵያ አብዛኞቹ ዩኒቨርስቲዎች በወረቀት የነበረውን አሰራር ወደ ዲጂታል በመቀየር የተሻለ አፈጻጻም እንዳላቸው ጠቁመዋል። ይሁን እንጂ የምርምርን፣ የመማር ማስተማርን፣ አስተዳደራዊ ሥራንና የማኅበረሰብ አገልግሎትን ዘመኑን የዋጀ ከማድረግ አንጻር ጅምር ላይ መሆናቸውን አንስተዋል። የመሰረተ-ልማት ክፍተት፣ የኢንተርኔት ተደራሽነት ውስንነትና ሌሎች ተያያዥ ችግሮች ዲጂታል ቴክኖሎጂ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት በፍጥነት እንዳያድግ ካደረጉት ውስጥ ጠቅሰዋል። በመሆኑም የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ብቁና ተወዳዳሪ ለመሆን እነዚህን ችግሮች ለመፍታት መሥራት እንዳለባቸው ተናግረዋል።   የመንግሥት ዩኒቨርስቲዎች የምክክር መድረክ የወቅቱ ሰብሳቢና የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ተጠባባቂ ፕሬዝዳንት ሳሙኤል ክፍሌ (ዶ/ር) ዲጂታላይዜሽን ለከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ያለው ፋይዳ ታምኖበት በምክክሩ ትኩረት መደረጉን ጠቁመዋል። አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የመማር ማስተማር፣ የምርምርና የአስተዳደር ሥራዎችን ዲጂታላይዝ ለማድረግ እየሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ዩኒቨርስቲው ከዋናው ስድስት ኪሎ ካምፓስ በመጀመር ወደ ሌሎች ለማስፋት በእቅድ ይዞ እየሰራ ነው ብለዋል። በትምህርት ሚኒስቴር የከፍተኛ ትምህርት ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ ኮራ ጡሽኔ በበኩላቸው ትምህርት ሚኒስቴር በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የዲጂታል መሰረተ-ልማትን ለማስፋት እየሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። እንደ ሚኒስትር ዴኤታው ገለጻ፤ በትምህርት ሚኒስቴር በቀጥታ የሚተዳደሩ 47 ዩኒቨርስቲዎች የዲጂታል መሰረተ-ልማት ቴክኖሎጂ እየተሟላ ይገኛል። በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት በበየነ መረብ የታገዘ ትምህርት በመስጠት የትምህርት ተደራሽነትን ለማስፋትም ትኩረት መሰጠቱን ተናግረዋል።      
አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ በመንግሥት አሰራሮች፣ በማምረቻ ኢንዱስትሪ፣ በንግድ፣ በትምህርት እና በሌሎች መስኮች መሠረታዊ ለውጥ እያመጣ ይገኛል
Jul 26, 2024 535
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 19/2016(ኢዜአ)፦ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ በመንግሥት አሰራሮች፣ በማምረቻ ኢንዱስትሪ፣ በንግድ፣ በትምህርት እና ሌሎችም መስኮች መሠረታዊ ለውጥ እያመጣ መሆኑን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ፡፡ አቶ ተመስገን በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ቴክኖሎጂ ዙሪያ የተዘጋጀውን ዐውደ ጥናት ተካፍለናል ብለዋል፡፡ ዐውደ ጥናቱ ከፍተኛ የመንግሥት የስራ ኃላፊዎች የተገኙበት እና በቢግ ዳታ፣ ጄኔሬቲቭ ኤ.አይ፣ በአመራሮች ውሳኔ አሰጣጥ፣ በፖሊሲ እና ሕዝብን በማገልገል ሂደት ውስጥ ቴክኖሎጂውን በመጠቀም ውጤታማነትን እንዴት ማሳደግ እንደሚቻል ግንዛቤ የተወሰደበት ነበርም ብለዋል በመልዕክታቸው፡፡   አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ዛሬ ላይ በሁሉም መስኮች አገልግሎት ላይ እየዋለ ነው ሲሉም ገልጸዋል፡፡ በዚህም በመንግሥት አሰራሮች፣ በማምረቻ ኢንዱስትሪ፣ በንግድ፣ በትምህርት እና ሌሎችም መስኮች መሠረታዊ ለውጥ እያመጣ ይገኛል ብለዋል፡፡ እኛም በዚህ ዘርፍ በርትተን በመስራት እና የሕዝባችንን ችግሮች መፍታት የሚችሉ የተለያዩ የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ሥርዓቶችን በማበልፀግ መጠቀም ይገባናል ሲሉም ገልጸዋል፡፡ የቴክኖሎጂውን ሙሉ አቅም ተገንዝቦ ወደ ተግባር የሚለውጥ የሰው ኃይል መገንባት ደግሞ ሌላኛው ቁልፍ ጉዳይ ነው ብለዋል፡፡ ከዚህ አንጻር እንደነዚህ ያሉ ዐውደ ጥናቶች ጉልህ ሚና እንዳለቸው እናምናለን ሲሉም ገልጸዋል፡፡ በወዳጅ ሀገር የተባበሩት አረብ ኤምሬትስ ተቀማጭነቱን ባደረገው ፕሪሳይት በተባለው ተቋም ለሦስት ቀናት የተዘጋጀው ዐውደ ጥናት በዘርፉ ያቀድነውን ወደ መሬት ለማውረድ ከሚሰጠው አቅጣጫ አንጻር ስኬታማ ነበርም ብለዋል ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመልዕክታቸው፡፡
ብሔራዊ የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ፖሊሲን ማስተግበሪያ ስትራቴጂና ማስፈጸሚያ ፕሮግራሞች ተዘጋጅተዋል
Jul 26, 2024 362
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 19/2016(ኢዜአ)፦ ብሔራዊ የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ፖሊሲን መተግበር የሚያስችሉ ስትራቴጂና ማስፈጸሚያ ፕሮግራሞች መዘጋጀታቸውን የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ገለጸ፡፡ የተለያዩ የዓለም ሀገራት አርቲፊሻል ኢንተለጀንስን ከመዝናኛና የመገልገያ ዘዴዎች እስከ ብሔራዊ ደህንነትና መረጃ አገልግሎት ላሉ ቁልፍ ጉዳዮች ጭምር ጥቅም ላይ እያዋሉት ነው፡፡ ኢትዮጵያም ቴክኖሎጂውን ለማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ፖለቲካዊ አገልግሎት ለማዋል፣ ፀጥታና ደህንነት ለማስጠበቅና በዘርፉ ተወዳዳሪ አቅም ለመፍጠር በርካታ ስራዎች ተከናውነዋል፡፡ በተለይም ከለውጡ በኋላ ዘርፉን የሚመራ ተቋም በመመስረት የኢትዮጵያን ትልሞች ለማሳካት እየተሰራ ነው። ከዚህም ባለፈ የሚኒስትሮች ምክር ቤት ሰኔ 20 ቀን 2016 ዓ.ም ባካሄደው 37ኛ መደበኛ ስብሰባ ብሔራዊ የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ፖሊሲ ስራ ላይ እንዲውል ወስኗል፡፡ የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ወርቁ ጋቸና(ዶ/ር ኢ/ር) ለኢዜአ እንዳሉት፤ ፖሊሲውን ለማዘጋጀት ከሁለት ዓመት በላይ ጊዜ ወስዷል፡፡ ፖሊሲው መንግስት በዘርፉ ሊደርስበት የፈለገውን ግብ ማሳካት እንዲችል የተለያዩ ባለሙያዎችን በማሳተፍና የሀገራትን ልምድ በመቀመር ስለመዘጋጀቱም ነው ያብራሩት። በርካታ ሀገራት የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ፖሊሲ እንደሌላቸው የጠቀሱት ዋና ዳይሬክተሩ የኢትዮጵያ መንግስት ፖሊሲው ወደ ስራ እንዲገባ መወሰኑ ለዘርፉ የሰጠውን ትኩረት ማሳያ ነው ብለዋል፡፡ ፖሊሲው ማንኛውም በውጭ የሚኖር ኢትዮጵያዊ ወደ ሀገሩ በመምጣት በዘርፉ በመሰማራት ራሱንና ሀገሩን በቴክኖሎጂ ማሳደግ የሚችልበትን እድል እንደሚፈጥርም አንስተዋል። ብሔራዊ የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ፖሊሲን በፍጥነት ሥራ ላይ ለማዋል የሚያግዙ ስትራቴጂና የማስፈጸሚያ ፕሮግራሞች መዘጋጀታቸውንም ዋና ዳይሬክተሩ ተናግረዋል።    
ቻይና በቴክኖሎጂና በወጣቶች በጎ ፈቃድ አገልግሎት ዘርፍ የኢትዮጵያ ወጣቶችን ለማብቃት አስፈላጊውን እገዛ እንደምታደርግ ገለጸች
Jul 26, 2024 345
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 19/2016(ኢዜአ)፦ ቻይና በቴክኖሎጂና በወጣቶች በጎ ፈቃድ አገልግሎት ዘርፍ የኢትዮጵያ ወጣቶችን ለማብቃት አስፈላጊውን እገዛ እንደምታደርግ ገልጻለች። የኢትዮጵያ ወጣቶች ምክር ቤት ፕሬዝዳንት ፉአድ ገና ከብሪክስ የወጣቶች ጉባኤ ጎን ለጎን ከቻይና የወጣቶች ፌዴሬሽን ምክትል ፕሬዝዳንት ጎንግ ጂንሎንግ ጋር ተወያይተዋል፡፡ መሪዎቹ በቻይና አፍሪካ የትብብር ማዕቀፍ ስር በትምህርት ፤ በስራ ፈጠራ፤ በወጣቶች በጎ ፈቃድ አገልግሎትና በቴክኖሎጂ ሽግግር ዙሪያ በጋራ ለመስራት ተስማምተዋል፡፡   በቻይና በየዓመቱ በሚካሄደው የአለም ወጣቶች ዴቨሎፕመንት ፎረም ላይ ኢትዮጵያውያን ወጣቶች በስፋት የሚሳተፉበትን እድል ለማመቻቸት በሚያስችሉ ነጥቦች ላይም ተወያይተዋል፡፡ የሁለቱን ሀገራት የወጣት ለወጣት ግንኙነት ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋር እንደሚሰሩ ያረጋገጡት መሪዎቹ በኢትዮጵያ የቻይንኛ ቋንቋ ማስተማሪያ ማዕከላትን ለማስፋፋትም ከስምምነት ደርሰዋል፡፡ ኢትዮጵያ በቻይና የቤልት ኤንድ ሮድ ኢኒሼቲቭ ማዕቀፍ ስር ተጠቃሚ የምትሆንበትን አማራጭ ለማስፋትም አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርጉ ምክትል ፕሬዝዳንት ገልጸዋል፡፡ ኢትዮጵያ የአፍሪካ-ቻይና ወጣቶች ጉባኤን በ2025 እንደምታስተናግድ የወጣቶች ምክር ቤት በማህበራዊ ትስስር ገጹ አስታውቋል።
ኢትዮጵያና ቻይና  በሳይንስና ቴክኖሎጂ ያላቸውን ትብብር አጠናክረው እንደሚቀጥሉ  ገለፁ
Jul 25, 2024 230
አዲስ አበባ፤ሐምሌ 18/2016 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያና ቻይና በሳይንስና ቴክኖሎጂ ልማት ያላቸውን ትብብር ይበልጥ አጠናክረው እንደሚቀጥሉ ገለፁ። የኢትዮጵያና ቻይና ሦስተኛው የሳይንስና ቴክኖሎጂ የጋራ ኮሚቴ ስብሰባ በአዲስ አበባ ተካሂዷል። ያለፉት ዓመታት የሳይንስና ቴክኖሎጂ የትብብር ማዕቀፎችን በመገምገም በቀጣይ አምስት ዓመታት በአዳዲስ ዘርፎች ላይ አብሮ ለመስራትም የመግባቢያ ስምምነት ተፈርሟል። የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትሩ በለጠ ሞላ (ዶ/ር) በንግግራቸው፥ ኢትዮጵያ ዲጂታል ትራንስፎርሜሽንን እውን የማድረግ ጉዞን መጀመሯን ገልጸው፥ ለውጤታማነቱም ምቹ ምህዳር ተፈጥሯል ብለዋል።   ለሳይንስ፣ ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ በተሰጠው ትኩረት በማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ መስኮች አበረታች ውጤቶች እየተመዘገቡ ስለመሆኑም አንስተዋል። የዜጎችን ህይወት ለማሻሻልና የሀገርን እድገት ለማፋጠን ቴክኖሎጂ ወሳኝ ነው ያሉት ሚኒስትሩ፥ ለስኬቱም ከአጋር አካላት ጋር በትብብር እየተሰራ ነው ብለዋል። በሁኔታዎች የማይለዋወጥ ስትራቴጂካዊ አጋርነት ያላቸው ኢትዮጵያና ቻይና በሳይንስና ቴክኖሎጂ ዘርፍም በትብብር እየሰሩ እንደሆነ ጠቅሰዋል።   የሀገራቱ ትብብር ለኢትዮጵያ የዲጅታል ሽግግር መሳካት የላቀ ሚና እንዳለው በማንሳት፥ በቀጣይም የቴክኖሎጂ ፈጠራን በሚያሳድጉ የትምህርትና ስልጠናና ሌሎች ትብብሮች ተጠናክረው ይቀጥላሉ ብለዋል። ዛሬ የተፈረመው የመግባቢያ ስምምነትም ባለሙያዎች በሳይንስና ቴክኖሎጂ የእውቀት ሽግግርና የልምድ ልውውጥ እንዲያደርጉ እንዲሁም በዘርፉ የጋራ የጥናትና ምርምሮችን ለማድረግ ያስችላል ነው ያሉት። የቻይና ሳይንስና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ሊን ዢን በበኩላቸው የዛሬው መድረክ የሀገራቱን የፈጠራ ስራ ትብብር ለማጠናከር የሚያግዝ እንደሆነ ተናግረዋል። ቻይና ከኢትዮጵያ ጋር በሳይንስና ቴክኖሎጂ ዘርፍ ያላትን ትብብር ይበልጥ አጠናክራ እንደምትቀጥልም አረጋግጠዋል።    
በሰው ሰራሽ አስተውሎት ዘርፍ በላቀ ክህሎት ሀገራቸውን የሚያስጠሩ በርካታ ባለተሰጥኦ ወጣቶች እየተፈጠሩ ነው
Jul 25, 2024 168
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 18/2016(ኢዜአ)፦ በሰው ሰራሽ አስተውሎት በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪና ሀገራቸውን የሚያስጠሩ በርካታ ባለተሰጥኦ ወጣቶች እየተፈጠሩ መሆኑን የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ወርቁ ጋቸና (ዶ/ር ኢ/ር) ገለጹ፡፡ ኢንስቲትዩቱ የታዳጊ ወጣቶችን የቴክኖሎጂና ፈጠራ አቅም ለማሳደግ ከመደበኛ ትምህርታቸው ጎን ለጎን የክረምት ሥልጠና እየሰጠ ይገኛል። በዘንድሮው ዓመትም ለሶስተኛ ዙር የሰው ሰራሽ አስተውሎት የክረምት ሥልጠና ከመጀመሪያና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች 200 ተማሪዎችን አወዳድሮ ለይቷል፡፡ የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ወርቁ ጋቸና (ዶ/ር ኢ/ር)፤ በሰው ሰራሽ አስተውሎት ዘርፍ በትኩረት መስራት ለሀገር እድገት መሰረት መሆኑን ገልጸዋል። በመሆኑም ኢንስቲትዩቱ ለዘርፉ እድገት እየሰራ መሆኑን ጠቅሰው ለተማሪዎች ከመደበኛ ትምህርታቸው ባሻገር አዳዲስ እውቀት የሚያገኙበት የተደራጀ የክረምት ስልጠና እየሰጠ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በመጀመሪያውና ሁለተኛው ዙር ሥልጠና ተሰጥኦዎቻቸውን ወደ ውጤት በመቀየር ከግል ተቋማት ጋር በትብብር መሥራት የሚችሉበት እድል ስለመፈጠሩም አስታውሰዋል። በመሆኑም የክረምት የታዳጊዎች ስልጠና ኢትዮጵያን በምርምርና ቴክኖሎጂ ዘርፍ ከፍ የሚያደርጉ ዓለምን የሚለውጡ ወጣቶች ይገኛሉ ተብሎ ይጠበቃል ብለዋል፡፡ የሰው ሰራሽ አስተውሎት የክረምት የታዳጊዎች ሥልጠና ኢትዮጵያ በቴክኖሎጂና ፈጠራ ዘርፍ ዓለምን የሚያስጠሩ ባለተሰጥኦ ወጣቶች ባለቤት መሆኗን አሳይቶናል ነው ያሉት፡፡ ወጣቶች የላቀ እውቀትና ሀሳብ እንዳላቸው ገልጸው፤ አቅማቸውን አውጥተው መጠቀም የሚችሉበትን እድል ማመቻቸት ደግሞ የእኛ ድርሻ ነው ብለዋል፡፡ በመሆኑም ለሥልጠናው በዘርፉ የካበተ ልምድ ያላቸው መምህራን፣ ምቹ የቴክኖሎጂ መሳሪያዎች፣ ቤተ ሙከራዎች እና መሰል ግብዓቶች የተሟሉለት ማዕከል መገንባቱን ገልጸዋል፡፡
የኢትዮጵያና የቻይና የሳይንስና ቴክኖሎጂ የትብብር መድረክ በአዲስ አበባ እየተካሄደ ነው
Jul 25, 2024 167
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 18/2016(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያና የቻይና ሦስተኛው የሳይንስና ቴክኖሎጂ የትብብር መድረክ በአዲስ አበባ እየተካሄደ ነው። በጉባዔው የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር በለጠ ሞላ (ዶ/ር)፣ የቻይና ሳይንስና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ሊበ ዢን እና ሌሎችም ከፍተኛ የመንግስት የስራ ሃላፊዎችና ጥሪ የተደረገላቸው እንገዶች ተገኝተዋል። በመድረኩ ላይ ንግግር ያደረጉት የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትሩ በለጠ ሞላ (ዶ/ር)፤ ኢትዮጵያ ዲጂታል ትራንስፎርሜሽንን እውን ለማድረግ በሚያስችል ጥረት ውስጥ መሆኗን ገልጸዋል። የኢትዮጵያና ቻይና ዲፕሎማሲ በጠንካራ ግንኙነት መቀጠሉን ጠቅሰው፤ የሳይንስና ቴክኖሎጂ ድጋፍና ትብብሩም ለድጅታል ትራንስፎርሜሸን እቅድ መሳካት የላቀ ሚና እንደሚኖረው ተናግረዋል። ሁለቱ አገሮች በኢንቨስትመንት፣ ግብርና፣ ኢንዱስትሪ፣ በመሠረተ-ልማትና ሌሎችም መስኮች ተቀራርበው መስራታቸውን አጠናክረው ይቀጥላሉ ብለዋል። የዛሬው መድረክም የዘርፉ ባለሙያዎች በሳይንስና ቴክኖሎጂ የእውቀት ሽግግርና የልምድ ልውውጥ የሚያደርጉበት ይሆናል ነው ያሉት።  
የአምስት ሚሊዮን ኢትዮጵያዊያን ኮደርስ ኢኒሼቲቭ  ከስራ ፈጠራ ባሻገር ለአገልግሎት ዘርፍ ኢንቨስትመንት መጎልበት ሚናው የጎላ ነው
Jul 23, 2024 554
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 16/2016(ኢዜአ)፦የአምስት ሚሊዮን ኢትዮጵያዊያን ኮደርስ ኢኒሼቲቭ ከስራ ፈጠራ ባሻገር ለአገልግሎት ዘርፍ ኢንቨስትመንት መጎልበት ሚናው የጎላ መሆኑ ተገለጸ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የአምስት ሚሊየን ኮደርስ ኢኒሼቲቭን በዛሬው ዕለት በይፋ አስጀምረዋል፡፡ ኢኒሼቲቩ በተባበሩት አረብ ኤምሬትስና የኢትዮጵያ መንግስታት የሚተገበር ሲሆን፤ በሀገር አቀፍ ደረጃ ያሉ 5 ሚሊዮን ወጣቶች በኦንላይን የኮዲንግ ስልጠና የሚወስዱበት ነው፡፡ ስልጠናውም በዋናነት በዌብ ፕሮግራሚንግ፣ በአንድሮይድ ማበልፀግ፣ ዳታ ሳይንስ እና አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ መሠረታዊ የዲጂታል ክህሎት ላይ ትኩረት ያደረገ ነው፡፡ ከኢኒሼቲቩ ማስጀመሪያው በተጓዳኝ የዲጂታል ኢትዮጵያ ጉዞ ላይ ትኩረት ያደረገ የፓናል ውይይት ተካሂዷል፡፡ በውይይቱ ከተሳተፉት መካከል የትምህርት ሚኒስትሩ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ፤ ኢኒሼቲቩ የትምህርት ዘርፉ ብቁ ትውልድ ለመገንባት በሚያከናውነው ስራ ላይ ከፍተኛ አበርክቶ እንዳለው አብራርተዋል፡፡   በተለይ ትውልዱ በንድፈ ሃሳብ የሚያገኛቸውን እውቀቶች በቀላሉ ወደ ተግባር እንዲለውጥ ምቹ እድል በመፍጠር በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ ያስችላል ነው ያሉት፡፡ የስራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪያት ካሚል በበኩላቸው ቴክኖሎጂ ከስራ ፈጠራ ጋር የሚተሳሰር ዘርፍ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡   የወጣቶችን ዲጂታል አቅም ለመገንባት የተሰጠው ትኩረት ደግሞ ግብርናን ጨምሮ የተለያዩ መስኮችን ለማዘመን የተያዘውን ውጥን እውን ለማድረግ እንደሚያግዝ ነው የተናገሩት፡፡ የተባበሩት አረብ ኤምሬትስ መንግስትን ወክለው በፓናሉ የተሳተፉት አብዱልአዚዝ አልጃዝሪ በኢትዮጵያ የዲጂታል ቴክኖሎጂን እውን በማደረግ ረገድ ከፍተኛ የሆነ የአመራር ቁርጠኝነት መኖሩን አንደታዘቡ ተናግረዋል፡፡   ይህ ደግሞ በኢኒሼቲቩ የተያዙ ግቦች እንዲሳኩ ከፍተኛ ሚና እንዳለው ጠቁመዋል፡፡ ቴክኖሎጂ የዓለምን ነባራዊ ሁኔታ በእጅጉ እየቀየረ ስለመሆኑ አንስተው፤ ከዚህ አኳያ ለዘርፉ ቅድሚያ መስጠት ይገባል ብለዋል፡፡ የአምስት ሚሊዮን ኢትዮጵያዊያን ኮደርስ ኢኒሼቲቭ ከ10 ዓመቱ መሪ የልማት አቅድ ጋር የሚጣጣም መሆኑን ያብራሩት ደግሞ የፕላንና ልማት ሚኒስትር ፍጹም አሰፋ (ዶ/ር) ናቸው፡፡   በእቅዱ ላይ ዲጂታል ክህሎትን መሰረት ያደረገ የሰው ኃይል ልማት ትኩረት እንደተሰጠው ጠቅሰው፤ ኢኒሼቲቩም ይህን እውን በማድረግ ረገድ ከፍተኛ ሚና አለው ብለዋል፡፡ በሌላ በኩል ኢኒሼቲቩ በኢትዮጵያ ክህሎት ያለው የሰው ሃይልን በመገንባት ትልልቅ ዓለም አቀፍ ኩባንያዎች በአገልግሎቱ ዘርፍ ኢንቨስት እንዲያደርጉ የሚያግዝ ነው ብለዋል፡፡ የፌደራል ሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽነር መኩሪያ ኃይሌ (ዶ/ር) ዘመናዊና ቀልጣፋ የአገልግሎት አሰጣጥን እውን ማድረግ መንግስት እያከናወነ ያለው የሲቪል ሰርቪስ ማሻሻያ አካል መሆኑን ጠቁመዋል፡፡   ለዚህ ደግሞ የመንግስት ሰራተኞች ዲጂታል ክህሎት ማደግ እንዳለበት ጠቅሰው፤ ኢኒሼቲቩም የሲቪል ሰርቪስ ማሻሻያውን የሚያግዝ ስለመሆኑ አብራርተዋል፡፡  
የአምስት ሚሊዮን ኢትዮጵያዊያን ኮደርስ ኢኒሼቲቭ ወጣቶች በዲጂታል ኢኮኖሚ ውስጥ በንቃት እንዲሳተፉ የሚያደርግ ነው - በለጠ ሞላ (ዶ/ር)
Jul 23, 2024 289
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 16/2016 (ኢዜአ)፦የአምስት ሚሊዮን ኢትዮጵያዊያን ኮደርስ ኢኒሼቲቭ ወጣቶች በዲጂታል ኢኮኖሚ ውስጥ በንቃት እንዲሳተፉ የሚያደርግ መሆኑን የኢኖቬሽን እና ቴክኖሎጂ ሚኒስትሩ በለጠ ሞላ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የአምስት ሚሊየን ኮደርስ ኢኒሼቲቭን በዛሬው ዕለት በይፋ አስጀምረዋል፡፡ ኢኒሼቲቩ በተባበሩት አረብ ኤምሬትስና ኢትዮጵያ መንግስታት የሚተገበር ሲሆን፤ በሀገር አቀፍ ደረጃ ያሉ 5 ሚሊዮን ወጣቶች በኦንላይን የኮዲንግ ስልጠና የሚወስዱበት ነው፡፡ ስልጠናውም በዋናነት በዌብ ፕሮግራሚንግ፣ በአንድሮይድ ማበልፀግ፣ ዳታ ሳይንስ እና አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ መሠረታዊ የዲጂታል ክህሎት ላይ ትኩረት ያደረገ ነው፡፡ የኢኖቬሽን እና ቴክኖሎጂ ሚኒስትሩ በለጠ ሞላ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት፤ ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ ወሳኝ ከሆኑት መሰረቶች አንዱ የዲጂታል ስነ ምህዳሩን ማስፋት መሆኑን አንስተዋል፡፡ የዲጂታል ስነ ምህዳሩን ከሚያሰፉ ስራዎች መካከል ዋነኛው የክህሎት ግንባታ መሆኑን ገልጸው፤ በዘርፉ እውቀትና ክህሎት ያለው የሰው ሀይል ማፍራት ላይ በትኩረት እየተሰራ እንደሆነም ጠቁመዋል፡፡ ከዚህ አኳያ የአምስት ሚሊዮን ኢትዮጵያዊያን ኮደርስ ኢኒሼቲቭ ወጣቶች በዲጂታል ስነ ምህዳር ውስጥ በንቃት እንዲሳተፉ የሚያስችላቸውን ክህሎት የሚያገኙበት መሆኑን ተናግረዋል። ኢትዮጵያ በቴክኖሎጂው መስክ ወደ ፊት እንድትራመድ በር የሚከፍት መሆኑንም እንዲሁ፡፡ ኢኒሼቲቭ መንግስት ወጣቶች ለማብቃት፤ ፈጠራን ለማጎልበት እንዲሁም የዲጂታል አቅም ለመጠቀም ያለውን ቁርጠኝነት የሚያሳይ መሆኑን ጠቁመዋል። ይህም ወጣቶች በዲጂታል ኢኮኖሚ ውስጥ ንቁ ተሳታፊ እና አምራች እንዲሆኑ የሚያስችላቸውን ክህሎት የሚያገኙበት መሆኑን ገልጸዋል። አንድ ሰው የዲጂታል ክህሎት አለው የሚያስብለው ከቴክኖሎጂው ባሻገር ዘመኑን የሚዋጅ አስተሳሰብን ሲላበስ መሆኑን ጠቅሰው፤ በመሆኑም ወጣቶች ከቴክኖሎጂ በተጨማሪ ህሊናዊና ባህሪያዊ የሆኑ የዲጂታል ዘመን ስብዕናን መገንባት እንዳለባቸው አስገንዝበዋል። ለኢኒሼቲቩ ስኬታማነት የፌደራል እና የክልል የመንግስት መዋቅሮች፤ የግሉ ዘርፍ የልማት አጋሮች እንዲሁም የሲቪል ማህበረሰብ እና ወላጆች የበኩላቸውን ሚና እንዲወጡም ጥሪ አቅርበዋል፡፡   የተባበሩት አረብ ኢምሬትስ የካቢኔ ጉዳዮች ሚኒስትር ዴኤታ አብዱላ ናስር፤ ኢኒሼቲቭ የኢትዮጵያና የተባበሩት አረብ ኢምሬትስ ያላቸውን አጋርነት ወደ አዲስ ምእራፍ የሚያሸጋግር መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በቀጣይም ሁለቱን አገራት በጋራ ተጠቃሚ በሚያደርጉ ሌሎች የትብብር መስኮች ለማስተሳሰር በትኩረት እንደሚሰራም አረጋግጠዋል፡፡ በተያያዘ ዜናም የአስፈጻሚ አመራሮች ስልጠና መርሃ ግብር ይፋ ተደርጓል፡፡ ስልጠናው ኢትዮጵያና የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች በትብብር የሚሰጡት ሲሆን፤ ከ15 የመንግስት ተቋማት የተወጣጡ አመራሮች ስልጠናውን የሚወስዱ ይሆናል፡፡ ስልጠናው ስድስት ወራት የሚወስድ ሲሆን፤ በኦንላይና አካል እንደሚሰጥ ተገልጿል፡፡  
ዲጂታል አቅምና ነገን የሚዋጅ አስተሳሰብ ያለው ትውልድ በመገንባት ለኢትዮጵያ ብልጽግና መሰረት የሚሆን ስራ እየተከናወነ ነው- ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ 
Jul 23, 2024 272
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 16/2016 (ኢዜአ)፦ዲጂታል አቅምና ነገን የሚዋጅ አስተሳሰብ ያለው ትውልድ በመገንባት ለኢትዮጵያ ብልጽግና መሰረት የሚሆን ስራ እየተከናወነ ነው ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ተናገሩ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የአምስት ሚሊየን ኮደርስ ኢኒሸቲቭን በዛሬው ዕለት በይፋ አስጀምረዋል፡፡ ኢኒሸቲቩ በተባበሩት አረብ ኤምሬትስና የኢትዮጵያ መንግስታት የሚተገበር ሲሆን፤ በሀገር አቀፍ ደረጃ ያሉ 5 ሚሊዮን ወጣቶች በኦንላይን የኮዲንግ ስልጠና የሚወስዱበት ነው፡፡ ስልጠናውም በዋናነት በዌብ ፕሮግራሚንግ፣ በአንድሮይድ ማበልፀግ፣ ዳታ ሳይንስ እና አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ መሠረታዊ የዲጂታል ክኅሎት ላይ ትኩረት ያደረገ ነው፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በዚሁ ጊዜ፤የተባበሩት አረብ ኤመሬትስ ፕሬዝዳንት ሸክ መሃመድ ቢን ዛይድ ኢትዮጵያን በጎበኙበት ወቅት ሁለቱ ሀገራት በተለያዩ መስኮች በጋራ ለመስራት ስምምነት መፈራረማቸውን አስታውሰዋል፡፡ ስልጠናውም የዚሁ ስምምነት አካል መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡   ኢትዮጵያ በአሳቢ ወጣት ዜጎቿ ተስፋ አላት ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ የኢትዮጵያ ብልጽግና የሚረጋገጠው ዲጂታል አቅምና ነገን የሚዋጅ አስተሳሰብ ያለው ትውልድ መገንባት ሲቻል ነው ብለዋል፡፡ ከዚህ አኳያ የአምስት ሚሊዮን ኮደርስ ኢኒሸቲቭ ይህን ታሳቢ ያደረገ ስራ መሆኑን አብራርተዋል፡፡ በኢነሸቲቩ እድሉን የሚያገኙ ወጣቶች በትብብርና በመደመር እሳቤ በዘርፉ ኢትዮጵያን ወደ ታሻለ ምእራፍ ለማሸጋገር መስራት እንደሚጠበቅባቸውም አስገንዝበዋል፡፡ በቀጣይም ብቁ ትውልድን በመገንባት ለኢትዮጵያ ብልጽግና መሰረት የሚሆኑ ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም ጠቁመዋል፡፡ ኢትዮጵያ የተባበሩት አረብ ኤምሬቶችን ጨምሮ ከመካከለኛው ምስራቅ አገራት ጋር ያላትን ትብብር ይበልጥ ለማጠናከር እየሰራች መሆኑንም ጠቅላይ ሚኒስትሩ ገልጸዋል፡፡ በተለይ ከተባበሩት ኤምሬቶች ጋር ትውልድን መገንባት በሚቻልባቸው ጉዳዮች ጋር በቅርበት እየሰራን ነው ብለዋል፡፡ በቀጣይም ትብብርን በማጠናከር የኢትዮጵያን ብልጽግና እውን ለማድረግ በትኩረት እንደሚሰራ አረጋግጠዋል፡፡
ኮደርስ መርሃ ግብር አምስት ሚሊዮን ኢትዮጵያውያንን በዌብ ፕሮግራሚንግ፣ በአንድሮይድ ማበልፀግ፣ ዳታ ሳይንስ እና አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ መሠረታዊ የዲጂታል ክሂሎት የሚያስጨብጥ ነው
Jul 23, 2024 297
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 16/2016(ኢዜአ)፦ ኮደርስ መርሃ ግብር አምስት ሚሊዮን ኢትዮጵያውያንን በዌብ ፕሮግራሚንግ፣ በአንድሮይድ ማበልፀግ፣ ዳታ ሳይንስ እና አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ መሠረታዊ የዲጂታል ክሂሎት የሚያስጨብጥ መሆኑን የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት አስታወቀ። የ''አምስት ሚሊዮን ኢትዮጵያውያን ኮደርስ’’ መርሃ ግብር በኢትዮጵያ እና በተባበሩት አረብ ኤምሬትስ መንግሥታት የተጀመረ የዲጂታል ሥራ ክሂሎቶችን የማሳደጊያ የትብብር ፕሮጀክት እንደሆነም ተገልጿል። በማደግ ላይ ባለው ዲጂታል ኢኮኖሚ ከባቢ የመጪው ትውልድ ኢትዮጵያውያንን ለማብቃት ታልሞ የተጀመረ እንደሆነም ተመላክቷል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ዛሬ በሳይንስ ሙዚየም አዲሱን መርሃግብር የዲጂታል እውቀትን ክፍተት ለማጥበብ የሚያስችል የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 አካል በማድረግ በይፋ ማስጀመራቸውን የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት መረጃ ያመለክታል። እ.ኤ.አ በ2026 መርሃግብሩ አምስት ሚሊዮን ኢትዮጵያውያንን በዌብ ፕሮግራሚንግ፣ በአንድሮይድ ማበልፀግ፣ ዳታ ሳይንስ እና አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ መሠረታዊ የዲጂታል ክሂሎት የሚያስጨብጥ መሆኑንም የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት አስታውቋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም