ኢኮኖሚ
በሀዋሳ ከተማ አስተዳደር የነዋሪዎችን የመኖሪያ ቤት ችግር በተለያዩ አማራጮች ለመፍታት እየተሰራ ነው
Aug 5, 2024 126
ሀዋሳ ፤ሐምሌ 29/2016 (ኢዜአ)፦የሀዋሳ ከተማ አስተዳደር የነዋሪዎችን የመኖሪያ ቤት ችግር በተለያዩ አማራጮች ለመፍታት ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑን አስታወቀ። የሀዋሳ ከተማ አስተዳደር ከተማ ልማት እና ኮንስትራክሽን መምሪያ ለ1 ሺህ 108 የመንግሥት ሠራተኞች ለጋራ መኖሪያ ቤት ግንባታ የሚሆን ቦታ ዛሬ በእጣ አስተላልፏል። በቦታ ርክክቡ ላይ የሀዋሳ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ መኩሪያ ማርሻዬ እንደገለጹት የቤት ጉዳይ ይበልጥ በከተሞች የመልካም አስተዳደር ጥያቄ ሆኖ ቆይቷል። ችግሩን ለማቃለል አስተዳደሩ ለስራው አመቺ የሆኑ መመሪያዎችን በማውጣት ለተግባራዊነቱ በሙሉ ቁርጠኝነት እየሰራ መሆኑንም ገልጸዋል። የተለያዩ አማራጮችን በመጠቀም የነዋሪዎችን የመኖሪያ ቤት ችግር ለመፍታት ጥረት እያደረገ ነው ሲሉም ጠቁመዋል። በተለይ የመንግሥት ሠራተኛውን በቤት ልማት አማራጮች ተጠቃሚ ለማድረግ እየተሠራ መሆኑን ጠቁመው፣ በዛሬው እለት ለ1ሺህ 108 የመንግሥት ሠራተኞች የቤት መስሪያ ቦታ ተላልፏል ብለዋል። መሠረተ ልማት የተሟላለት 51 ሺህ 950 ካሬ ሜትር ቦታ የተላለፈው በመኖሪያ ቤት ሕብረት ሥራ የተደራጁ 35 ማህበራት ለግንባታው ሂደት አስፈላጊውን ገንዘብ በመቆጠባቸው መሆኑንም ገልጸዋል። በቀጣይም ሁሉም የከተማዋ ነዋሪ በአቅሙ ልክ ሊሳተፍበት የሚችልበትን የኮንዶሚንየም ቤት አመራጭ አስተዳደሩ በማዘጋጀት በቅርቡ ምዝገባ እንደሚጀምርም አመልክተዋል። የሲዳማ ክልል ከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ቢሮ ኃላፊ አቶ አሻግሬ ጀንበሬ በበኩላቸው ከቅርብ ጊዜ ጀምሮ በክልሉ በከተሞች ለሰው ተኮር ልማት ልዩ ትኩረት በመሰጠቱ የህብረተሰቡ ችግር እየተቃለለ መጥቷል።   በክልሉ ልዩ ትኩረት ከተሰጣቸው አንዱ የቤት መስሪያ ቦታ ማመቻቸት መሆኑን ጠቅሰው፣ ቦታውን ያገኙት እድለኞች ደረጃውን የጠበቀ ግንባታ በማካሄድ ለከተማዋ ልማት የበኩላቸውን አስተዋጽኦ እንዲያደርጉ አሳስበዋል። ቢሮውም የዲዛይን ክትትልና ቁጥጥር ከማድረግ ባለፈ በግንባታ ሂደት የሚያጋጥሙ ችግሮችን በመፍታት ድጋፍ እንደሚያደርግ አስታውቀዋል። የመኖሪያ ቤት መስሪያ ቦታ ካገኙት መካከል አስተያየታቸውን የሰጡት አቶ ይሁንሰው አብርሃም ቦታ ለማግኘት በማህበር ተደራጅተው በየወሩ ሲቆጥቡ መቆየታቸውን ገልጸዋል። አሁን ላይ በከተሞች ያለው የመኖሪያ ቤት ኪራይ ዋጋ እየጨመረ መምጣቱ በተለይ ለመንግስት ሠራተኛውና ዝግቀተኛ ገቢ ላላቸው ነዋሪዎች ከአቅም በላይ መሆኑን ተናግረዋል። ከተማ አስተዳደሩ ይህን ችግር አይቶ የቤት መስሪያ ቦታ በመስጠቱ አመስግነው በቅርቡ የቤት ባለቤት የመሆን ተስፋ ሰንቂያለሁ ሲሉ ገልጸዋል።   የጤና በለሙያ አቶ ባርናባስ ተስፋዬ በበኩላቸው እሳቸውን ጨምሮ የቤት መስሪያ ቦታ የተሰጣቸው የመንግስት ሠራተኞች ለረጅም ጊዜ በኪራይ ቤት ሲኖሩ እንደነበር አስታውሰዋል። የተሰጣቸው የቤት መስሪያ ቦታ ከቤት ኪራይ ወጪ በዘላቂነት ለመገላገል ምቹ ሁኔታ እንደሚፈጥርላቸው ተናግረዋል። ሠራተኞቹ ከተማ አስተዳደሩ አሁን የጀመረው የመኖሪያ ቤት ችግር የመፍታት ጥረት አጠናክሮ መቀጠል እንዳለበትም ተናግረዋል።
በክልሉ በግብይት ወቅት ሕገ ወጥ ተግባር በፈጸሙ ነጋዴዎች ላይ እርምጃ እየተወሰደ ነው - የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ንግድና ገበያ ልማት ቢሮ
Aug 5, 2024 123
አርባ ምንጭ ፤ ሐምሌ 29/2016 (ኢዜአ)፦ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በግብይት ወቅት ሕገ ወጥ ተግባር የፈጸሙ ነጋዴዎች ላይ እርምጃ እየተወሰደ መሆኑን የክልሉ ንግድና ገበያ ልማት ቢሮ ገለጸ። የክልሉ ንግድና ገበያ ልማት ቢሮ በህገ-ወጥ የንግድ ስርአት ቁጥጥርና ገበያ ማረጋጋት ላይ በተዋረድ ከሚገኙ መዋቅር ሥራ ሃላፊዎች ጋር በአርባ ምንጭ ከተማ ዛሬ ውይይት አድርጓል። በዚህ ወቅት የቢሮ ሃላፊው አቶ ገሌቦ ጎልሞ እንደገለጹት፤ የማክሮ ኢኮኖሚ ፖሊሲ ማሻሻያን ተከትለው በግብይት ወቅት ሕገ ወጥ ተግባር የፈጸሙ ነጋዴዎች ላይ እርምጃ እየተወሰደ ይገኛል። በክልሉ አንዳንድ ነጋዴዎች በግብይት ወቅት ህገ ወጥ ተግባር እንደፈጸሙ ጠቁመው፤ በተለይ ምርቶችን የመደበቅና የማሸሽ ህገ ወጥ ተግባራት መኖራቸውን በተደረገ ምልከታ መረጋገጡን ተናግረዋል። በክልሉ በየደረጃው የአስተዳደር፣ የፀጥታ፣ የፍትህና ሌሎች ባለድርሻ አካላትን ያካተተ የህገ-ወጥ ንግድ ቁጥጥር ግብረ-ሃይል መኖሩንም ጠቁመዋል። ግብረ-ሃይሉ ባለፉት አምስት ቀናት በ304 የንግድ ድርጅቶች ላይ ባደረገው የክትትልና ቁጥጥር ሥራ በንግድ ልውውጥ ወቅት ሕገወጥ ተግባር ሲፈጽሙ በተገኙ 44 የንግድ ድርጅቶች ላይ ማሸግን ጨምሮ ሌሎች እርምጃዎች መወሰዱን አብራርተዋል። የንግዱ ማህበረሰብ አባላት ከህገ ወጥ ድርጊት በመቆጠብ በተጠያቂነት መንፈስ ሥራቸውን ማከናወን ይገባቸዋል ሲሉም አሳስበዋል።        
በክልሉ ምርታማነትን መጨመርና ገቢ የመሰብሰብ አቅምን ማሳደግ ይገባል - ርዕሰ መስተዳድር አቶ አረጋ ከበደ
Aug 5, 2024 118
ባህር ዳር ፤ ሐምሌ 29/2016 (ኢዜአ)፦በአማራ ክልል የኑሮ ውድነትን ለመከላከል ምርታማነትና ገቢን ማሳደግ ላይ አመራሩ ልዩ ትኩረት ሰጥቶ እንደሚሰራ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ አረጋ ከበደ ገለጹ። የክልሉ የከተማ ልማት ክላስተር በማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ፕሮግራም ፖሊሲ የትኩረት ጉዳዮች ላይ የውይይት መድረክ በባህር ዳር ከተማ አካሂዷል። በዚሁ ወቅት ርዕሰ መስተዳድር አቶ አረጋ ከበደ እንደገለጹት፤ በአዲሱ ዓመት አመራሩ የኑሮ ውድነትን ለመቀነስ በየዘርፉ ምርታማነትን የሚያሳድጉ ሥራዎች ላይ በትኩረት ይሰራል።   እንዲሁም የክልሉን የገቢ አቅም ማሳደግ ትኩረት የሚሻው ጉዳይ እንደሆነ ጠቅሰው፤ ገቢ የመሰብሰብ ሥራ ለገቢዎች ተቋም ብቻ የሚተው እንዳልሆነ ተናግረዋል። ለዚህም ከላይ እስከታች ያለው አመራር ገቢ የመሰብሰብ ስራውን የራሱ ተግባር አድርጎ መስራት እንደሚጠበቅበት ገልጸዋል። በተጨማሪም የኑሮ ውድነትን ለመቀነስ የሥራ እድል ፈጠራ ላይ ትኩረት ማድረግና ገበያውን መግራት እንደሚያስፈልግ ርዕሰ መስተዳድሩ ተናግረዋል። በክልሉ በከተማም ሆነ በገጠር የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ በየዘርፉ ቅንጅታዊ ሥራንና ትብብርን አጠናክሮ ለማስቀጠል እንደሚሰራም አስረድተዋል።   ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ዶክተር አብዱ ሁሴን በበኩላቸው እንደገለጹት፤ አሁን እየተወሰደ ያለው የፖሊሲ ማሻሻያ እርምጃ የማክሮ ኢኮኖሚ ስብራትን ለማሻሻል እንደሆነ መገንዘብ ያስፈልጋል። በተጨማሪም በኢንዱስትሪ የመልማት እምቅ አቅም ላለው የአማራ ክልል መልካም አጋጣሚ እንደሆነ ጠቅሰው፤ በየደረጃው ያለው አመራር በልዩ ክትትል ለተግባራዊነቱ መትጋት እንዳለበት አስገንዝበዋል።   በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የከተማ ዘርፍ አስተባባሪ እና የከተማና መሰረተ ልማት ቢሮ ሃላፊ ዶክተር አሕመዲን መሐመድ፤ ክልሉን ከችግር ለማውጣት ምርታማነትንና ገቢ የመሰብሰብ አቅምን ለማሳደግ ልዩ ትኩረት ሰጥቶ መሰራት ይገባል ብለዋል። በከተሞች ኢንዱስትሪዎችን በማስፋፋት በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ጠቅሰው፤ የተጀመሩ ሁለንተናዊ ተግባራት ተጠናክረው እንዲቀጥሉ ህገ ወጥነትን በመከላከል በኩል አመራር አባላት ግንባር ቀደም ሆነው ሊሰሩ እንደሚገባ አስገንዝበዋል። በመድረኩ የክልል፣ የዞንና የከተማ አስተዳደር አመራር አባላት ተሳታፊ ሆነዋል።      
በጌዴኦ ዞን የተጀመሩ የልማት ስራዎች መጠናከር  እንዳለባቸው ተገለጸ
Aug 5, 2024 107
ዲላ ፤ሐምሌ 29/2016 (ኢዜአ)፦ በጌዴኦ ዞን በተለያዩ ዘርፎች የተጀመሩ የልማት ስራዎች ተጠናክረው ሊቀጥሉ እንደሚገባ ተገለጸ። የዞኑን ህዝብ የወከሉ የምክር ቤት አባላት በጌዴኦ ዞን በዲላ ዙሪያ ወረዳና በዲላ ከተማ በየዘርፉ እየተከናወኑ ያሉ የልማት ሥራዎችን ጎብኝተዋል። ጉብኝቱም በዋናነት በግብርና ዘርፍ የቡና፣ የእንሰትና የፍራፍሬ ልማት፣ የመሰረተ ልማት ግንባታዎች እንዲሁም የኮሪደር ልማት ስራዎችን ያካተተ ነው። በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግስት የልማት ድርጅቶች ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ ዶክተር ኢንጅነር ስለሺ ኮሬ በወቅቱ ለኢዜአ እንዳሉት፤ የቡና፣ የእንሰትና የፍራፍሬ ክላስተር ልማት እየተከናወኑ ያሉ ስራዎች ተስፋ ሰጭና የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ናቸው። በተለይ በጥቂት አርሶ አደሮች ማሳ የተጀመረው ኩታ ገጠም የቡና ልማትን ማስፋት እንደሚገባ ጠቁመዋል።   ከአዲስ አበባ ከተማ ልምድ በመውሰድ በዲላ ከተማ የተጀመረው የኮሪደር ልማት ከህብረተሰቡ ጋር በመቀናጀት ወደ ስራ መገባቱ የሚበረታታ መሆኑን ጠቁመው፤ ይህ ተግባር መጠናከር እንዳለበት አሳስበዋል። የጌዴኦ ዞን ምክር ቤት አባል አቶ ንጉሴ አሰፋ በበኩላቸው እንደገለጹት፤ በዞኑ የተጀመሩ ዘርፈ ብዙና ተስፋ ሰጪ የልማት ስራዎች ተጠናክረው መቀጠል አለባቸው። በተለይ የዲላ ከተማ የንጹህ መጠጥ ውሃ ማስፋፊያ ግንባታ ለማጠናቀቅና ለአገልግሎት ለማብቃት የሚደረገው ጥረት የሚበረታታ መሆኑን ጠቅሰው፤ ጥረቱን እንደሚያግዙም አረጋግጠዋል። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክር ቤት አፈ ጉባኤ ወይዘሮ ፀሃይ ወራሳ በበኩላቸው፤ በዞኑ እየተከናወኑ ያሉ የልማት ስራዎች ተስፋ ሰጪና የህብረተሰቡን የልማትና መልካም አስተዳደር ጥያቄዎች የሚመልሱ መሆናቸውን ገልጸዋል።   የልማት ስራዎቹ ጅምራቸው መልካም መሆኑን አንስተው፤ የህዝቡን የልማት ፍላጎት እስኪመለስ ድረስ በተቀናጀና በተናበበ መልኩ ተጠናክረው መቀጠል እንዳለባቸው አስገንዝበዋል። የጌዴኦ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ዶክተር ዝናቡ ወልዴ በበኩላቸው፤ በዞኑ በተለይ በምግብ ሰብል እራስን በመቻል ከተረጅነት ለመላቀቅ የኩታ ገጠም የግብርና ልማት ስራዎች ላይ በማተኮር በውስን ስፍራ ከፍተኛ የምርት መጠን እየተገኘ ነው ብለዋል። በሞዴል አርሶ አደሮች ማሳ ቡና በሄክታር 19 ኩንታል ማግኘት መቻሉን ለአብነት ጠቅሰዋል። ዋና አስተዳዳሪው እንደተናገሩት፤ የዞኑ የለውጥ ሂደት ከግብ እንዲደርስ በየደረጃው ያሉ የምክር ቤት አባላት አስፈላጊውን ድጋፍ ማድረግ ይጠበቅባቸዋል።    
በአማራ ክልል የትምህርት ተደራሽነትን ለማስፋት በቅንጅት ይሰራል - ዶክተር አብዱ ሁሴን
Aug 5, 2024 96
ባህር ዳር፤ ሐምሌ 29/2016(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል በአዲሱ ዓመት የትምህርት ተደራሽነትን የበለጠ ለማስፋት በቅንጅት እንደሚሰራ የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ዶክተር አብዱ ሁሴን ገለፁ። በክልሉ የማህበራዊ ክላስተር አመራር አባላት የተሳተፉበት በትምህርት ጉዳዮች የሚመክር መድረክ በባህር ዳር እየተካሄደ ነው። ምክትል ርዕሰ መስተዳድሩ እንደገለፁት፤ የክልሉ መንግስት ባለፉት ዓመታት የመማሪያ መፃሀፍት፣ ወንበር፣ ጠረጴዛና ሌሎች ግብዓቶችን በማሟላት ለትምህርት ዘርፍ መጠናከር ትኩረት ሰጥቶ ሲሰራ ቆይቷል። በክልሉ የትምህርት ተደራሽነትን የበለጠ ለማስፋት ከተያዘው ክረምት ጀምሮ የሚፈፀም የትምህርት ንቅናቄ ዕቅድ ተዘጋጅቶ ወደ ስራ መግባቱን ገልጸዋል። የክረምት የዝግጅት ስራዎችን ጥንካሬና ድክመት በመገምገም በአዲሱ ዓመት ከምዝገባ ጀምሮ በቅንጅት በመረባረብ የዘርፉን ዕቅድ ማሳካት ላይ ትኩረት እንደሚደረግም ተናግረዋል።   የክልሉ ትምህርት ቢሮ ምክትል ሃላፊ አቶ መኳንንት አደመ በበኩላቸው፤ በአዲሱ የትምህርት ዘመን በቅድሚያ ነባርና አዲስ ተማሪዎችን በመለየት ከነሐሴ 20 ቀን 2016 ዓ.ም ጀምሮ በንቅናቄ ምዝገባ ይከናወናል ብለዋል። በተጨማሪም ትምህርት ቤቶችና የትምህርት ማህበረሰብ ያሉበት ሁኔታ በመለየት በግብዓት፣ ክህሎትና ሌሎች ስራዎች ለማጠናከር በየደረጃው ያለው ለትምህርት ዘርፉ አመራርና ባለድርሻ አካላት በልዩ ትኩረት ይሰራሉ። በመድረኩ የማህበራዊ ክላስተር የክልል፣ የዞን፣ የወረዳና የከተማ አስተዳደር አመራሮች እየተሳተፉ ይገኛል።
በአማራ ክልል በምርት ዘመኑ  ለማምረት የተያዘውን ዕቅድ ለማሳካት ርብርብ እየተደረገ ነው 
Aug 5, 2024 107
ባህር ዳር ፤ሐምሌ 29/2016(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል በ2016/2017 የምርት ዘመን ለማምረት በዕቅድ የተያዘውን ግብ ለማሳካት በተቀናጀ አግባብ ርብርብ እየተደረገ መሆኑን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። በገጠር ልማት ዘርፍ የተደራጁ ተቋማት የ2017 በጀት ዓመት ዕቅድ ትውውቅ መድረክ በባህር ዳር ከተማ ዛሬ ተካሂዷል። በምክትል ርዕሰ መስተዳደር ማዕረግ የገጠር ልማት ዘርፍ አስተባባሪና የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊ ድረስ ሳህሉ (ዶ/ር) እንደገለጹት፤በምርት ዘመኑ ካለፈው ዓመት የተሻለ ለማምረት ትኩረት ተሰጥቷል።   እስካሁን በተደረገው በዕቅድ ከተያዘው 5 ነጥብ 1 ሚሊዮን ሄክታር መሬት ውስጥ 4 ነጥብ 5 ሚሊዮን ሄክታሩ በተለያየ የሰብል ዘር መሸፈኑን አስታውቀዋል። በግብአት አቅርቦት በኩልም ካለፉት ዓመታት በተሻለ እስከሁን 6 ነጥብ 5 ሚሊዮን ኩንታል የአፈር ማዳበሪያ ለአርሶ አደሩ ማሰራጨት መቻሉን ተናግረዋል። በክልሉ በምርት ዘመኑ ዕቅድ መሰረት ከሚለማው መሬት 169 ሚሊዮን ኩንታል ምርት ለማሳካት የተቀናጀ ርብርብ እየተደረገ መሆኑን አስታውቀዋል። ''የተያዘውን ዕቅድ ለማሳካትም ቀሪውን መሬት በዘር ከመሸፈን ባሻገር የለማውን ሰብል ከፀረ አረምና ፀረ ሰብል ተባይ የመከላከል ስራ በትኩረት እየተሰራ ነው'' ብለዋል። የዝናቡ ስርጭት ለሰብል ልማቱ ተስማሚ መሆኑን ጠቅሰው፤ በዚህም ምርታማነትን በሄክታር ከ28 ነጥብ 2 ኩንታል ወደ 32 ነጥብ 7 ኩንታል ለማሳደግ የተሻሻሉ አሰራሮችን በመተግባር ርብርብ እየተደረገ እንደሚገኝ አስረድተዋል።   የክልሉ መንገድ ቢሮ ኃላፊ ጋሻው አወቀ(ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ለክልሉ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ልማት ምቹ ሁኔታ ለመፍጠርም ባለፈው በጀት ዓመት አንድ ሺህ 37 ኪሎ ሜትር መንገድ መገንባት መቻሉን ገልጸዋል። እንዲሁም 73 ድልድዮች መገንባታቸውንና 11ሺህ 902 ኪሎ ሜትር የነባር መንገዶች ጥገና ስራም መከናወኑንም አውስተዋል። በያዝነው በጀት ዓመትም ካለፈው ዓመት በተሻለ የመንገድ ግንባታና የነባር መንገዶች ጥገና ስራ ለማከናወን መታቀዱን አስረድተዋል።   የንፁህ መጠጥ ውሃ ተቋማትን ተደራሽ ለማድረግ ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ ነው ያሉት ደግሞ የክልሉ ውሃና ኢነርጂ ቢሮ ኃላፊ ማማሩ አያሌው(ዶ/ር) ናቸው። በተጠናቀቀው በጀት ዓመት 14 ከፍተኛ የውሃ ተቋማትን፣ 640 አነስተኛ የውሃ ተቋማትን በመገንባት ከ400 ሺህ በላይ ህዝብ ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልጸዋል። በዚህም የክልሉን የንፁህ መጠጥ ውሃ ሽፋን ከ73 ነጥብ 2 በመቶ ወደ 75 ነጥብ 1 በመቶ ማሳደግ መቻሉን አስታውቀዋል። በያዝነው የበጀት ዓመትም 14 ከፍተኛና መካከለኛ የውሃ ተቋማትን እንዲሁም አንድ ሺህ 600 አነስተኛ የንፁህ መጠጥ በመገንባት የመጠጥ ውሃ ሽፋኑን 77 ነጥብ 1 በመቶ ለማድረስ ታቅዶ ወደ ተግባር መገባቱን አስረድተዋል። በዕቅድ ትውውቅ መድረኩ የክላስተር ተቋማት ከፍተኛ የአመራር አባላት፣ የህዝብ ግንኙነት ሃላፊዎችና የዞን ምክትል አስተዳዳሪዎች ተሳትፈዋል።    
ከ550 ቢሊየን ብር በላይ ተጨማሪ በጀት ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሊቀርብ ነው 
Aug 5, 2024 155
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 29/2016(ኢዜአ)፦ለ2017 በጀት ዓመት ከ550 ቢሊየን ብር በላይ ተጨማሪ በጀት በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ለማፀደቅ ዝግጅት መደረጉን ገንዘብ ሚኒስቴር ገለጸ። የ2017 የፌዴራል መንግሥት በጀት 971 ነጥብ 2 ቢሊየን ብር ሆኖ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መጽደቁ ይታወሳል። በጀቱ ከባለፈው ዓመት ጋር ሲነጻጸር የ21 ነጥብ 1 በመቶ እድገት ያሳየ ነበር። ከዚህ ውስጥ ለመደበኛ በጀት 451 ነጥብ 3 ቢሊየን ብር ለካፒታል በጀት ደግሞ 283 ነጥብ 2 ቢሊየን ብር ተይዟል። የገንዘብ ሚኒስትር ዴኤታው እዮብ ተካልኝ (ዶ/ር) የማክሮ ኢኮኖሚ ፖሊሲ ትግበራውን አስመልክቶ በሰጡት ማብራሪያ የፖሊሲ ማሻሻያው ዘላቂና አስተማማኝ ኢኮኖሚ ለመገንባት መሠረት የሚጥል ነው ብለዋል። የፖሊሲ ማሻሻያው ተግባራዊ መደረጉን ተከትሎ የተለያዩ የፋይናንስ ምንጮች ድጋፍ እያደረጉ መሆኑንም ነው ያነሱት። ይህን ተከትሎ ገንዘብ ሚኒስቴር ለ2017 በጀት ዓመት ይፋ ካደረገው የፌዴራል መንግሥት በጀት ተጫማሪ በጀት እንደሚያፀድቅ ተናግረዋል። ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ለማፀደቅ የተዘጋጀው ከ550 ቢሊየን ብር በላይ ሲሆን፤ ከዚህ ወስጥ 240 ቢሊየን ብሩ ለማኅበራዊ ልማት የሚውል ነው ብለዋል። መንግሥት የማክሮ ኢኮኖሚ ፖሊሲውን በተሟላ መልኩ ገቢራዊ ሲያደርግ ዝቅተኛ ገቢ ያላቸውን ዜጎች ታሳቢ በማድረግ መሆኑንም አብራርተዋል። በዚህም ቋሚ ገቢ ያላቸውና በልማታዊ ሴፍትኔት ለሚታገዙ ዜጎች በቂ ድጎማ ለማድረግ ተጨማሪ በጀቱ ወሳኝ ሚና አለው ብለዋል። ተጨማሪ በጀቱ ለዘይት፣ ለነዳጅና ለመድኃኒት ድጎማ እንዲውል በማድረግ በፖሊሲው ትግበራ ጊዜ ሊደርሱ የሚችሉ ስጋቶችን አስቀድሞ ለመከላከል እንደሚያስችል አብራርተዋል። ከዚህ ባለፈ አገራዊ ወጪን በራስ ገቢ ለመሸፈን የሚደረገው ጥረት ተጠናክሮ እንደሚቀጥልና የፖሊሲ ትግበራው የገቢ አቅምን በማሳደግ በኩል ወሳኝ ሚና እንዳለው አንስተዋል። ኢኮኖሚው የሚያመነጨውን ገቢ በአግባቡ በመሰብሰብ ለተለያዩ የልማት ሥራዎች እንደሚውል ጠቁመዋል።  
በኦሮሚያ ክልል በአርብቶ አደር አካባቢዎች የተከናወኑ የኩታገጠም የግብርና ልማት ሥራዎች ውጤታማ ናቸው 
Aug 5, 2024 152
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 29/ 2016 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል በአርብቶ አደር አካባቢዎች የተከናወኑ የኩታገጠም የግብርና ልማት ሥራዎች ውጤታማ መሆኑን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ሽመልስ አብዲሳ ገለጹ። በኦሮሚያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ሽመልስ አብዲሳ የተመራው የክልሉና የፌዴራል ከፍተኛ አመራሮች በምዕራብ ጉጂ ዞኖች የተከናወኑ የግብርና ሥራዎችን ጎብኝቷል። የኦሮሚያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ሽመልስ አብዲሳ በዚሁ ጊዜ፤ ባለፉት ዓመታት በአርብቶ አደር አካባቢ ከፍጆታ ባለፈ ገበያ ተኮር የግብርና ልማት ተግባራት ውጤታማ መሆናቸውን ገልፀዋል።   ኩታገጠም እርሻን ማስፋትን ጨምሮ ግብርናን በቴክኖሎጂ በመደገፍ ረገድ ዘመናዊ የእርሻ መሣሪያዎች አቅርቦትና የአጠቃቀም ባህልን ለማሳደግ የተሰራው ሥራ ለውጥ አምጥቷል ነው ያሉት። በተለይም የሰብል ልማት በማይታወቅባቸው የክልሉ አካባቢዎች የተከናወኑ ተግባራት የምግብ ዋስትና ከማረጋገጥ ባለፈ ምርት ለአገር ውስጥ ኢንዱስትሪዎችና ለውጭ ገበያ እየቀረበ ይገኛል ብለዋል። በቀጣይም በዘርፉ የተከናወኑ መልካም ተግባራትን በማስፋት ከግብርና ዘርፍ በርካታ ባለሃብቶችን የማፍራት ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ተናግረዋል። ይህም በዋነኝነት በአካባቢው ያሉትን ፀጋዎች ጥቅም ላይ በማዋል የሚገኝን ገቢ በመቆጠብ ኢንቨስትመንት ላይ በማዋል ሊሆን ይገባል ብለዋል።      
 በምዕራብ ሸዋ ዞን የተለያዩ የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች ተመርቀው አገልግሎት መስጠት ጀመሩ
Aug 5, 2024 98
አምቦ ፤ ሐምሌ 29/2016(ኢዜአ)፦ በምዕራብ ሸዋ ዞን ጨሊያ ወረዳ ከ100 ሚሊዮን ብር በሚበልጥ ወጪ የተገነቡ 36 የልማት ፕሮጀክቶች ተመርቀው ለአገልግሎት ክፍት ሆኑ። የልማት ፕሮጀክቶቹ ዛሬ ሲመረቁ የኦሮሚያ ክልል የአመራር አባላት፣ የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ እና የወረዳ አመራሮች፣ አባ ገዳዎች፣ የሃይማኖት አባቶች፣ የአገር ሽማግሌዎች እና ነዋሪዎች ተገኝተዋል። ከተመረቁ የልማት ፕሮጀክቶች መካከል ለጨሊያ ወረዳ አስተዳደር ጽህፈት ቤት የሚያገለግል ህንጻ፣ መንገድ፣ የመጠጥ ውሃ ተቋማት፣ ድልድይ እና ሌሎች የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶች ይገኙበታል።   የምዕራብ ሸዋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ዲዳ ጉደታ በዚሁ ወቅት እንደተናገሩት ዛሬ ለምረቃ የበቁትን ጨምሮ በአጠቃላይ በዞኑ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ3 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር በላይ ወጪ የተደረገባቸው የልማት ስራዎች ለአገልግሎት በቅተዋል። አጠቃላይ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ግንባታቸው ተጠናቆ ለአገልግሎት የበቁት 762 የተለያዩ ፕሮጀክቶች መሆናቸውንም አስረድተዋል፡፡ የተጠናቀቁት የልማት ፕሮጀክቶች የዞኑ ህዝብ ለረጅም ጊዜ ሲጠይቃቸው የነበሩ የመሰረተ ልማት ጥያቄዎች መሆናቸውንም አስታውሰዋል።   ከለውጡ ወዲህ ፕሮጀክቶችን በተያዘላቸው ጊዜ አጠናቆ ለአግልግሎት ከማብቃት አንጻር አበረታች እንቅስቃሴዎች እንዳሉም ተናግረዋል። በፕሮጀክቶቹ ምረቃ ላይ የተገኙት የኦሮሚያ ቡሳ ጎኖፋ ሃላፊ አቶ ሞገስ ኢደኤ በበኩላቸው የዞኑ ነዋሪዎች ፕሮጀክቶቹ የራሳቸው መሆኑን ተገንዝበው እንክብካቤ እንዲያደርጉላቸው ጠይቀዋል፡፡ የጨሊያ ወረዳ ነዋሪዎች በበኩላቸው ለአገልግሎት የበቁ ፕሮጀክቶች ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ስላላቸው ረጅም ዓመት እንዲያገለግሉ እንከባከባቸዋለን ብለዋል።    
ለአቅመ ደካማ ወገኖች የሚከናወነው የቤት ግንባታ በፍጥነት እየተከወነ ነው
Aug 5, 2024 136
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 29/ 2016 (ኢዜአ)፦ በአዋሬ አካባቢ ለአቅመ ደካማ ወገኖች እየተከናወነ ያለው የቤት ግንባታ በታሰበው መሠረት እየሄደ መሆኑን የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት አስታወቀ፡፡ በየዓመቱ ለአረጋውያን እና በኢኮኖሚ ዝቅተኛ ለሆኑ ወገኖች የሚደረገው የቤት እድሳት እና ግንባታ ላይ የሚያተኩረው ማኅበራዊ በጎ ሥራ የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሥራዎች ቁልፍ ምሰሶ መሆኑን ገልጿል። በዚህም በአዋሬ አካባቢ ለሰው የተሻለ እና የተከበረ አኗኗር ለመፍጠር እየተደረገ ያለው የለውጥ እንቅስቃሴ በፌደራል እና ክልል የመንግሥት አካላት የሚተገበረው የዚሁ ትልም ዐቢይ አካል መሆኑን የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት በማህበራዊ ትስስር ገጹ አስታውቋል፡፡ የዘንድሮው ሥራም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በግንቦት ወር ማስጀመራቸውን ያስታወሰው ጽህፈት ቤቱ፤ ለአቅመ ደካማ ወገኖች የሚከናወነው የቤት ግንባታ በፍጥነት እየተከወነ እንደሚገኝ አመላክቷል፡፡
በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በድሬዳዋ የህዝብ ተሳትፎና ተጠቃሚነት ያረጋገጡ የልማት ውጤቶች ተመዝግበዋል - ከንቲባ ከድር ጁሃር
Aug 5, 2024 86
ድሬዳዋ ፤ሐምሌ 29/2016 (ኢዜአ)፦በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የህዝብ ተሳትፎና ተጠቃሚነት ያረጋገጡ የማህበራዊ እና የምጣኔ ሃብታዊ የልማት ውጤቶች መመዝገባቸውን የድሬዳዋ አስተዳደር ከንቲባ ከድር ጁሃር አስታወቁ። የድሬዳዋ አስተዳደር 3ኛ ዙር 3ኛ የሥራ ዘመን 8ኛ መደበኛ ጉባዔ እየተካሄደ ነው ። የአስተዳደሩ ከንቲባ ከድር ጁሃር ለጉባኤው የተጠናቀቀውን በጀት ዓመት የአስፈፃሚውን እና የማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎት ዘርፎች የዕቅድ አፈፃጸም ሪፖርት አቅርበዋል። ከንቲባው በሪፖርታቸው በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የገጠርና የከተማን ህዝብ ሁለንተናዊ ተሳትፎና ተጠቃሚነት ያረጋገጡ የማህበራዊ እና የምጣኔ ሃብታዊ የልማት ውጤቶች መመዝገባቸውን ገልጸዋል። የፍትህ እና የፀጥታ አካላትን በማቀናጀት እና አስተማማኝ ሰላምና ፀጥታን የማስፈን ተግባራት መከናወናቸውን ጠቅሰው፤ በጤና፣ በትምህርት፣ በስራ ዕድል ፈጠራ፣ የምግብ ዋስትናን ማረጋገጥ፣ በመንገድ ግንባታ እና በሌሎች ዘርፎችም የህዝብን የዓመታት የልማት እና የመልካም አስተዳደር ችግሮች ያቃለሉ ሥራዎች መሰራታቸውን ጠቁመዋል።   እንደ ከንቲባ ከድር ማብራሪያ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በአስተዳደሩ ገጠርና ከተማ የሚታየውን የስራ አጥነት ችግሮች ለማቃለል በተከናወኑ የተቀናጁ ስራዎች አበረታች ውጤቶች ተገኝተዋል። በገጠርና በከተማ ከተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎች የተመረቁ ባለሙያዎችን ጨምሮ ከ19ሺህ 660 በላይ ሰዎች ቋሚ የስራ ዕድል ለመፍጠር ታቅዶ ከ18ሺህ 80 በላይ ለሚሆኑ ሰዎች የስራ ዕድል በመፍጠር የዕቅዱን 91 ነጥብ 9 በመቶ ማሳካት መቻሉንም ተናግረዋል። ቋሚ የስራ ዕድል ከተፈጠረላቸው በተጨማሪ 3ሺህ 800 የሚሆኑ ወጣቶችና ሴቶች በተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶች ላይ ጊዜያዊ የስራ ዕድል ማግኘታቸውን ገልጸዋል። እንደ ከንቲባ ከድር ገለፃ፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የተገኙ የልማት ውጤቶችን በተሻለ መንገድ ለማስቀጠል የሚያስችል በድሬዳዋ ብሩህ እና የተረጋጋ የሥራ ምህዳር አለ። በጉባዔው ላይ የተሳተፉ የድሬዳዋ አስተዳደር የተለያዩ ቋሚ ኮሚቴዎች ሰብሳቢዎች በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በገጠርና በከተማ ያካሄዱትን የክትትልና የቁጥጥር ምልከታዎችን መነሻ በማድረግ በቀረበው ሪፖርት ላይ አስተያየታቸውን አቅርበዋል።    
በዞኑ ከ47 ሚሊዮን ብር በሚበልጥ ወጪ የተገነቡ ሁለት ድልድዮች ተመርቀው ለአገልግሎት ክፍት ተደረጉ
Aug 5, 2024 95
ሚዛን አማን ፤ ሐምሌ 29/2016(ኢዜአ)፦ በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ቤንች ሸኮ ዞን ከ47 ሚሊዮን ብር በሚበልጥ ወጪ የተገነቡ ሁለት ድልድዮች ተመርቀው ለአገልግሎት ክፍት መደረጋቸው ተገለፀ። በሚዛን አማን ከተማ የተገነባው የአጉ ወንዝ ድልድይና በግዲ ቤንች ወረዳ የተገነባውን የዳማ ወንዝ ድልድይን የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር) መርቀው ከፍተዋል።   ለሁለቱ ድልድዮች 47 ነጥብ 3 ሚሊዮን ብር ወጪ መደረጉን የክልሉ መንገዶች ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር አብድዩ መኮንን ገልጸዋል። የአጉ ወንዝ ድልድይ የሚዛን አማን ከተማ አስተዳደር እና የሸኮ ወረዳን የሚያገናኝ ሲሆን የድልድዩ መገንባት በአካባቢው የሚመረቱ የአትክልትና ፍራፍሬ እንዲሁም ሌሎች የግብርና ምርቶችን ወደ ገበያ ለማቅረብ ምቹ ሁኔታን የሚፈጥር ነው ብለዋል።   42 ሜትር የሚረዝመው የዳማ ወንዝ ድልድይ የጊድ ቤንች እና የሰሜን ቤንች ወረዳዎችን ከማገናኘትም በተጨማሪ የጊድ ቤንች ወረዳን ከዞን ማዕከል ጋር የሚያገናኝ ወሳኝ ድልድይ መሆኑንም ተናግረዋል። በምረቃ ሥነ ሥርዓቱ ላይ የክልሉ የመንግሥት ዋና ተጠሪ አቶ ፀጋዬ ማሞን ጨምሮ ሌሎች የክልሉ እና የዞን ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል።  
በሀዋሳ ከተማ ከ1 ሺህ በላይ ለሚሆኑ የመንግሥት ሠራተኞች የመኖሪያ ቤት መስሪያ ቦታ ተሰጠ
Aug 5, 2024 128
ሀዋሳ፤ሐምሌ 29/2016 (ኢዜአ)፡-በሀዋሳ ከተማ በማህበር ተደራጅተው የመኖሪያ ቤት መስሪያ ቦታ ለጠየቁ 1ሺህ 108 ለሚሆኑ የመንግሥት ሠራተኞች ቦታ ተሰጠ። የሀዋሳ ከተማ አስተዳደር ከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን መምሪያ ሃላፊ ኢንጂነር ምህረቱ ገብሬ ዛሬ በተዘጋጀው የቦታ ርክክብ መርኃ ግብር ላይ እንደገለፁት የቤት መስሪያ ቦታው የተሰጠው በመኖሪያ ቤቶች ህብረት ስራ ለተደራጁ 35 ማህበራት ነው።   ማህበራቱ ተደራጅተው 50 በመቶ የሆነውን ከ378 ሚሊዮን ብር በላይ ቆጥበው ያጠናቀቁ መሆናቸውንም አስታውቀዋል። የመኖሪያ ቤት መስሪያ ቦታ የተሰጣቸው የመንግስት ሠራተኞች፤የዩኒቨርሲቲ መምህራን፣ የጤና ባለሙያዎች እና የመከላከያ ሰራዊት አባላት ናቸው ብለዋል። ከቤት መስሪያ ቦታ ተጠቃሚዎች ውስጥ 334ቱ ደግሞ ሴቶች ናቸው ብለዋል። ለመንግስት ሰራተኞቹ የተሰጠው ቦታ 51 ሺህ 950 ካሬ ሜትር ስፋት ያለውና ባለ አራት ወለል ህንፃ መገንቢያ የሚሆን ነው ተብሏል። ቦታው መሰጠቱ በነዋሪው ዘንድ ይነሳ የነበረውን የቤት ቅሬታና የመልካም አስተዳደር ጥያቄ ለመመለስ የተወሰደ እርምጃ መሆኑን ያነሱት ደግሞ በመርሃ ግብሩ ላይ የተገኙት የሀዋሳ ከተማ ከንቲባ መኩሪያ መርሻዬ ናቸው። ከተማ አስተዳደሩ የነዋሪውን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ ዘርፈ ብዙ ልማቶችን በመሥራት ላይ መሆኑንም ከንቲባው ገልጸዋል። በመርኃ ግብሩ ላይ የከተማው አስተዳደር ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎችና የማህበራቱ አባላት ተገኝተዋል።  
ከተማዋን ውብና ለነዋሪዎች ምቹ የማድረግ ስራዎች በግልና በመንግስት ተቋማትም በመስፋፋት ላይ ይገኛሉ - ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Aug 5, 2024 166
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 28/2016(ኢዜአ):- አዲስ አበባን እንደ ስሟ ውብና ለኑሮ ምቹ ለማድረግ እንደ ከተማ አስተዳደር ከተጀመሩት የኮሪደር ልማት ስራዎች በተጨማሪ ስራው በሌሎች የግል እና የመንግስት ተቋማትም በመስፋፋት ላይ እንደሚገኝ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ:: ከንቲባ አዳነች አቤቤ በአቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ ለሕዝብ መዝናኛ አገልግሎት እንዲውል የተገነባውን ፋውንቴይን መርቀው አስጀምረዋል::   ከንቲባዋ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ከተማችን አዲስ አበባን እንደ ስሟ ውብ አበባ እንዲሁም ለኑሮ ምቹ ለማድረግ እንደ ከተማ አስተዳደር ከጀመርናቸው የኮሪደር ልማት ስራዎች በተጨማሪ ስራው በሌሎች የግል እና የመንግስት ተቋማት በመስፋፋት ላይ ይገኛል ሲሉ አስፍረዋል:: በዛሬው ምሽትም የኢትዮጵያ ኮንስትራክሽን ስራዎች ኮርፖሬሽን (ኢኮስኮ) በአቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ ለሕዝብ መዝናኛ አገልግሎት እንዲውል የገነባውን ፋውንቴይን መርቀን አገልግሎት አስጀምረናል ብለዋል ::   ፒያሳ ዶሮ ማነቂያ አካባቢ በብራዘርስ ኮንስትራክሽን እና ቦሌ ሩዋንዳ ድልድይ ስር በአሰር ኮንስትራክሽን በተመሳሳይ ለሕዝብ መዝናኛ እንዲውሉ በራሳቸው ወጪ የገነቧቸውን ፋውንቴኖች ለህዝብ አገልግሎት ክፍት ማድረጋቸውን አስታውሰዋል:: የኢትዮጵያ ኮንስትራክሽን ስራዎች ኮርፖሬሽን(ኢኮስኮ) ፣ብራዘርስ ኮንስትራክሽን እና አሰር ኮንስትራክሽን ከልብ እያመሰገንኩ ሌሎች የግል እና የመንግስት ተቋማትም ከዚህ ልምድ በመውሰድ አካባቢያቸውን ለነዋሪዎች ምቹ ማድረጋቸውን አጠናክረው እንዲቀጥሉ ጥሪ ላቀርብ እወዳለሁ ብለዋል::
የልማት ማህበሩ በድሬዳዋ ልማት ላይ የሚያደርገውን ተሳትፎ እንዲያሳድግ አስፈላጊው ድጋፍ ይደረጋል- ከንቲባ ከድር ጁሃር
Aug 4, 2024 139
ድሬዳዋ ፤ ሐምሌ 28/2016(ኢዜአ)፦ የስልጤ ልማት ማህበር በድሬዳዋ በተጀመሩ የልማት ተግባራት ላይ እያበረከተ የሚገኘውን አስተዋፅኦ እንዲያሳድግ አስፈላጊው ድጋፍ እንደሚደረግ የድሬዳዋ አስተዳደር ከንቲባ ገለፁ። በድሬዳዋና አካባቢው የሚገኘው የስልጤ ልማት ማህበር ቅርንጫፍ ፅህፈት ቤት "በአዲስ ተስፋ ሰላምን እናጠናክር" በሚል መሪ ሃሳብ ኮንፈረንስ ዛሬ በድሬዳዋ አካሄዷል።   ከንቲባ ከድር ጁሃር በኮንፈረንሱ ላይ በክብር እንግድነት ተገኝተው ባደረጉት ንግግር እንደገለፁት፤ ማህበረሰቡ በሚያከናውናቸው የልማት ተግባራት ከተረጂነት ለመውጣት ለተጀመረው ጥረት መሳካት በአብነት የሚጠቀስ ነው። በድሬዳዋ የሚኖሩ የማህበረሰቡ አባላት ከአስተዳደሩ ጎን በመቆም በማህበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎችና የበጎ ፍቃድ ልማት ስራዎች ላይ አስተዋጽኦ እያበረከቱ እንደሚገኙም ተናግረዋል። ማህበሩ በድሬዳዋ በተጀመሩ የልማት ተግባራት ላይ እያበረከተ የሚገኘውን አስተዋፅኦ እንዲያሳድግ አስፈላጊው ድጋፍ እንደሚደረግ አብራርተዋል።   የስልጤ ዞን ዋና አስተዳዳሪ እና የስልጤ ልማት ማህበር የቦርድ ሰብሳቢ አቶ አሊ ከድር በበኩላቸው፤ 22ተኛ ዓመቱን ያስቆጠረው ማህበሩ በአገር ዘላቂ ልማት ላይ የድርሻውን እያበረከተ ይገኛል። ማህበሩ ከአባላትና አጋሮች በሚያገኘው ሃብት፣ ዕውቀትና ጉልበት የዞኑን ህብረተሰብ ማህበራዊ ችግሮችን በማቃለል ረገድ አበረታች ስራዎች እያከናወነ መሆኑን ገልፀዋል ። የማህበረሰቡ ቋንቋ፣ ባህል እና ትውፊቶች ተጠብቀው ለትውልድ እንዲተላለፉ በማድረግም የራሱን ሚና እየተጫወተ መሆኑን አውስተዋል። የዛሬው ህዝባዊ ንቅናቄ መድረክ ዓላማም እነዚህን ስራዎች ይበልጥ ወደ ላቀ ደረጃ ለማድረስ እና ከድሬዳዋ ልማት ማህበር ጋር በመቀናጀት በአስተዳደሩ የልማት አጋርነትን ለማፅናት መሆኑንም ገልጸዋል።  
በክልሉ የተጀመሩ የልማት ስራዎችን ከመደገፍ ባሻገር የመጠበቅና የመንከባከብ ኃላፊነታችንን በትኩረት እንወጣለን- የሐረር ከተማ ነዋሪዎች
Aug 4, 2024 133
ሐረር፤ ሐምሌ 28/2016 (ኢዜአ)፡- በክልሉ የተጀመሩ የልማት ተግባራትን በተለያዩ አግባቦች ከመደገፍ ባሻገር እየተከናወኑ የሚገኙ የልማት ስራዎችን የመጠበቅና የመንከባከብ ኃላፊነታቸውን በትኩረት እንደሚወጡ የሐረር ከተማ ነዋሪዎች ገለፁ። በክልሉ በ2017 በጀት ዓመት በህዝብ ንቅናቄ የሚከናወኑ የልማት ተግባራት ዙሪያ ከሐረር ከተማ ነዋሪዎች ጋር የውይይት መድረክ ተካሄዷል። በመድረኩ የተገኙ ነዋሪዎች እንደገለጹት፤ በክልሉ የተጀመሩ የልማት ተግባራትን ከመደገፍ ባለፈ እየተከናወኑ ያሉ የልማት ስራዎችን የመጠበቅና የመንከባከብ ኃላፊነታችንን በትኩረት እንወጣለን። ከተሳታፊዎቹ መካከል አቶ አሰፋ ፍስሃ በክልሉ በተከናወነውና በተመለከትነው የኮሪደር የልማት ስራ ሁላችንም ደስ ብሎናል ኮርተናልም ብለዋል። በተለይ የክልሉ መንግስት በ2017 በጀት ዓመት በኮሪደር ልማትም ይሁን በማንኛውም ዘርፍ ለሚያከናውነው የልማት ስራ ያላቸውን ድጋፍ አጠናክረው እንደሚቀጥሉም አረጋግጠዋል። በከተማው እየተከናወኑ ያሉ የኮሪደር እና ሌሎች የልማት ስራዎች ከተማዋ ውብ ገጽታ እንድትላበስ እያደረጉ ይገኛሉ ያሉት ደግሞ ወይዘሮ ኢፍቱ ተስፋዬ ናቸው። ሐረርን ውብ ጽዱና ለጎብኚውና ለነዋሪዎቿ ማራኪ ለማድረግ እየተከናወኑ የሚገኙ ስራዎችን ህዝቡ በባለቤትነት ሊጠብቀውና ሊንከባከበው ይገባል ብለዋል። በክልሉ በአሁኑ ወቅት እየተከናወነ የሚገኘው የኮሪደር ልማት ስራ እጅግ ማራኪና አስደሳች ነው ያሉት ሌላው የከተማው ነዋሪ አቶ አብዲ ረሺድ ናቸው። ለስኬታማነቱም የክልሉ መንግስትና አመራሩ የወሰደው ቁርጠኝነት የሚደነቅ መሆኑን የተናገሩት አቶ አብዲ የልማት ስራዎቹን ልንደግፍና ልናግዝ ይገባል ብለዋል። መድረኩን የመሩት የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ ኦርዲን በድሪ በበኩላቸው በክልሉ አበረታች ስራዎች ቢከናወኑም በቂ አለመሆናቸውን ተናግረዋል።   በተለይ ሐረርን የሚመጥኑ፣ ነዋሪዎቿን ይበልጥ ተጠቃሚ የሚያደርጉና ፍትሃዊነት የተላበሱ ስራዎች በቀጣይ እንደሚከናወኑም አረጋግጠዋል። በውይይት መድረኩ ላይም በየደረጃው የሚገኙ የክልሉ አመራር አባላት፣ የማህበረሰብ ተወካዮች፣ ነዋሪዎችና ሌሎች ተገኝተዋል።
የኢትዮጵያ ቡና ከምርት እስከ ግብይት ባለው ሂደት ለቱሪዝም ዘርፉ መጎልበት ትልቅ ሚና ይኖረዋል- ዶክተር አዱኛ ደበላ
Aug 4, 2024 140
ጅማ ፤ ሐምሌ 28/2016(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ቡና ከምርት እስከ ግብይት ባለው ሂደት የአገርን ገፅታ በመገንባት ለቱሪዝም ዘርፉ መጎልበት ትልቅ ሚና እንደሚኖረው የቡናና ሻይ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር አዱኛ ደበላ (ዶ/ር ) ገለፁ። ቡናን ከቱሪዝሙ ዘርፍ ጋር በማስተሳሰር የቱሪስት መስህብ ለማድረግ ያለመ የመግባቢያ ስምምነት ሰነድን የቡናና ሻይ ባለስልጣን እና የኦሮሚያ ቱሪዝም ኮሚሽን ዛሬ ተፈራርመዋል። በኢትዮጵያ የተለያዩ የቡና ዝርያዎችን በምርምር በማግኘት ምርቱን በማሳደግ እና የውጭ ምንዛሬ ምንጭ ለማድረግ በትኩረት እየተሰራ መሆኑም ተገልጿል። ቡናን ከማስተዋወቅም ባለፈ ለቱሪዝም ዘርፉም ትልቅ ሚና እንዲኖረውና ትስስሩን እንዲጠናከር የማድረግ ስራ እየተሰራ መሆኑንም በስምምነቱ ወቅት ተነስቷል። የቡናና ሻይ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር አዱኛ ደበላ (ዶ/ር ) በወቅቱ እንደገለጹት፤ ቡናን በጥራት ተመርቶና እሴት ተጨምሮበት ለዓለም ገበያ በማቅረብ ከቱሪዝም ዘርፍ ጋር የማስተሳሰር ሥራ ይሰራል። ''የቡና ምርትን በምርምር ማዕከሎች፣ በቡና ተክል ልማት ውስጥ ሎጆችን እና መዝናኛ ስፍራዎችን በመገንባት የቱሪስት መስህብ ይደረጋል'' ብለዋል። ባለፈው ዓመት ከቡና ከአንድ ነጥብ አራት ቢሊዮን ዶላር በላይ ገቢ መገኘቱን የገለጹት ዳይሬክተሩ፤ ከዚህ በላይ ለማግኘት በትኩረት እየተሰራ መሆኑንም ገልጸዋል። የኦሮሚያ ቱሪዝም ኮሚሽነር ሌሊሴ ዱጋ እንደተናገሩት፤ ከቡናና ሻይ ባለስልጣን ጋር በመቀናጀት በክልሉ ያለውን የቡና ምርት ለዓለም በማስተዋወቅ፣ የቡናን ባህላዊ እሴት በማጉላት የቱሪስት መስህብ ይደረጋል። ቡናን ጥሬውን ከመላክ ይልቅ እሴት ታክሎበት ቢላክ የተሻለ ገቢ ከማምጣቱም በላይ በማሸጊያው ላይ የኢትዮጵያን ባህላዊና ታሪካዊ ሀብት ለማስተዋወቅም ያግዛል ብለዋል።  
የተለያዩ የጥቆማ ዜዴዎችን ጨምሮ ነፃ የስልክ መሥመሮችን በመጠቀም ያላግባብ የዋጋ ጭማሪ በሚያደርጉ ነጋዴዎች ላይ ዘላቂነት ያለው ህጋዊ እርምጃ እንወስዳለን- ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Aug 4, 2024 173
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 28/2016(ኢዜአ)፦ የተለያዩ የጥቆማ ዜዴዎችን ጨምሮ ነፃ የስልክ መሥመሮችን በመጠቀም ያላግባብ የዋጋ ጭማሪ በሚያደርጉ ነጋዴዎች ላይ ዘላቂነት ያለው ህጋዊ እርምጃ እንወስዳለን ሲሉ የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። ከንቲባ አዳነች አቤቤ እና የገንዘብ ሚኒስትር ዴኤታ እዮብ ተካልኝ(ዶ/ር) የአዲስ አበባ ከተማን የንግድ ማህበረሰብ እና ሌሎች ባለድርሻ አካላትን ያሳተፈ የማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርም ተግባራዊነት ዙሪያ ውይይት አድርገዋል።   በውይይቱ ላይ የገንዘብ ሚኒስትር ዴኤታ እዮብ ተካልኝ(ዶ/ር) መንግስት በተገበረው የማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርም ማሻሻያ አስፈላጊነት እና አተገባበር ዙሪያ ለንግዱ ማህበረሰብ እና ለከተማው አመራር ግንዛቤ አስጨብጠዋል:: በመድረኩ ላይ የተሳተፉት የንግዱ ማህበረሰብ አባላት በቀረበው ግንዛቤ ማስጨበጫ ላይ ያላቸውን ጥያቄ ያነሱ ሲሆን ህገወጥ ንግድ የኢኮኖሚ ጤንነትን በማቃወስ ሀገርን ለአደጋ የሚዳርግ መሆኑን በመጥቀስ መንግሥት በህገወጥ ነጋዴዎች እና ከእነሱ ጋር በመተባበር ሀገርን በሚጎዱ ስግብግብ አመራሮችና ባለሞያዎች ላይ ህጋዊ እርምጃዎችን ቀጣይነት ባለው አግባብ እንዲወስድ ጠይቀዋል።   ከንቲባ አዳነች አቤቤ ከተሳታፊዎቹ ለተነሱ ጥያቄዎች በሰጡት ምላሽ የሪፎርሙ ተግባራዊነት ሁሉንም ባለድርሻ አካላትን ባሳተፈ መልኩ እየተከናወነ መሆኑን ጠቅሰው አብዛኛው የንግዱ ማህበረሰብ በህጋዊነት ስራውን እየሰራ መሆኑን በማድነቅ ዶላር ጨመረ በሚል ሽፋን ያላአግባብ የዋጋ ጭማሪ እያደረጉ ያሉት ስግብግብ ነጋዴዎች ላይ የከተማ አስተዳደሩ ህጋዊ እርምጃ መውሰድ መጀመሩን ተናግረዋል። ለሀገራችን ኢኮኖሚ ፍቱን መፍትሄ ይዞ የመጣውን የማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርም ባልተገባ ሁኔታ በመተርጎም ያላግባብ የዋጋ ጭማሪ ያደረጉ 250 በላይ ነጋዴዎች ላይ ህጋዊ እርምጃ መወሰዱን ለታዳሚዎቹ ገልፀዋል። ከንቲባ አዳነች አቤቤ በውይይቱ ላይ ክትትሉና የእርምት እርምጃዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም አቅጣጫ አስቀምጠዋል። የገንዘብ ሚኒስትር ዴኤታ እዮብ ተካልኝ(ዶ/ር) በበኩላቸው የኢኮኖሚ ሪፎርሙ ተከታታይ የኢኮኖሚ እድገቱን የሚጨምር መሆኑን ጠቅሰው መንግስት ለዚህም ከፍተኛ ዝግጅት ማድረጉን ገልፀዋል። ከንቲባ አዳነች አቤቤ ህብረተሰቡ እስካሁን እያደረገ ላለው ውጤታማ ትብብር በማመስገን ሁሉም ባለድርሻ አካላት በዘላቂነት ከከተማ አስተዳደሩ ጋር በቅንጅት እንዲሰሩ ጥሪ ማቅረባቸውን የከንቲባ ጽህፈት ቤት መረጃ ያመለክታል።            
የኦሮሚያ ክልል ፕሬዝዳንት ሽመልስ አብዲሳ በጉጂ ዞን የግብርና እና የእንስሳት ሀብት ልማት ስራዎችን ጎበኙ
Aug 4, 2024 130
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 28/2016(ኢዜአ)፦ የኦሮሚያ ክልል ፕሬዝዳንት ሽመልስ አብዲሳ በጉጂ ዞን የተለያዩ ወረዳዎች የግብርና እና የእንስሳት ሀብት ልማት ስራዎችን ጎበኙ። የክልሉ ፕሬዝዳንትና ሌሎችም የክልልና የፌዴራል መንግስት ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች በጉጂ ዞን በቦሬ እና አኖ ቄረንሳ ወረዳዎች የተለያዩ የልማት ስራዎችን ተዘዋውረው ተመልክተዋል።   በክልሉ በግብርና ልማትና የእንስሳት እርባታ የላቀ ውጤት ለማስመዝገብ በልዩ ትኩረት እየተሰራ መሆኑን አቶ ሽመልስ ገልጸዋል። በዚህ ረገድ በጉጂ ዞን የተለያዩ ወረዳዎች የግብርና እና የእንስሳት ልማት ስራዎች ጥሩ ማሳያ መሆናቸውንም ጠቅሰዋል። በመሆኑም በእንስሳት ዝርያ ማሻሻያ፣ በመኖ ልማትና አቅርቦት እንዲሁም የእንስሳት ጤና አጠባበቅ ዙሪያ የተጀመሩ ስራዎች የሚበረታቱ በመሆናቸው ሊጠናከሩ ይገባል ብለዋል። በእንስሳት እርባታ በተገኘው ስኬት ልክ የተቀናጀ የግብርና ስራም በስፋት ሊከናወን እንደሚገባ ጠቅሰዋል። በሁሉም ዘርፎች መንግስት አስፈላጊውን ድጋፍና እገዛ የሚያደርግ መሆኑንም ፕሬዝዳንቱ አረጋግጠዋል።
ከንቲባ አዳነች አቤቤ መንግስት በቅርቡ ተግባራዊ ባደረገው የማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርም ማሻሻያ ዙሪያ ከንግድ ማህበረሰብ አባላት እና ከከተማ አስተዳደሩ አመራሮች ጋር ተወያዩ
Aug 4, 2024 163
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 28/2016(ኢዜአ)፦ መንግስት በቅርቡ ተግባራዊ ባደረገው የማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርም ማሻሻያ ዙሪያ ከንግድ ማህበረሰብ አባላት እና ከከተማ አስተዳደሩ አመራሮች ጋር ውይይት ማድረጋቸውን የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። ከንቲባዋ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት ዛሬ ከንግድ ማህበረሰብ አባላት እና ከከተማ አስተዳደሩ አመራሮች ጋር የፋይናንስ ሚኒስትር ዴኤታ እዮብ ተካልኝ (ዶ/ር) በተገኙበት መንግስት በቅርቡ ተግባራዊ ባደረገው የማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርም ማሻሻያ ዙሪያ ውይይት አድርገናል ብለዋል።   ሪፎርሙ ለሀገራችን በርካታ ጥቅም የሚያስገኝ መሆኑንም በመልዕክታቸው ጠቅሰዋል። በዋነኛነት ዘላቂ ልማትንና አካታችነትን ለማረጋገጥ፣ ሁሉንም የማህበረሰብ ክፍል ተጠቃሚ የሚያደርግ የኢኮኖሚ ስርዓት ለመገንባት፣ የመንግስትን የእዳ ጫና ለመቀነስ፣ የተረጋጋ ተወዳዳሪ እና የዋጋ ግሽበትን መቀነስ የሚያስችል የገበያ ሁኔታን ለመፍጠር፣ ተኪ ምርቶችን በማምረትና ለውጪ ገበያ የምንልከውን ምርት በማሳደግ እንዲሁም ምቹ የኢንቨስትመንት ሁኔታ በመፍጠር የውጪ ምንዛሬ ገቢን ለማሳደግ እድል የሚፈጥር መሆኑን ገልጸዋል። ወቅታዊ ተግዳሮቶችን ለመቆጣጠር ደሃው እና ዝቅተኛ ገቢ ያለው ማህበረሰብ እንዳይጎዳ የመንግስት ሰራተኞችን ደሞዝ መጨመር፣ ደሃውን መደጎም ፣ በተለይም በሴፍቲኔት የታቀፉ የማህበረሰብ ክፍሎችን ገቢ በሚያስገኝና ተረጂነትን በሚቀንስ መንገድ መደገፍ እንዲሁም የስራ እድልን በስፋት መፍጠርን ታሳቢ ባደረገ መልኩ የሚተገበር መሆኑንም ጠቅሰዋል። በቀጣይም ከአምራቾች እና አስመጪዎች ጋር በቅርበት በመስራትና ገበያውን የሚያዛቡ፣ በተለይም ምንም ከውጪ ምንዛሪ ጋር ግንኙነት የሌላቸው ምርቶች ላይ አላግባብ ዋጋ በሚጨምሩ እና ምርት በሚሰውሩ አካላት ላይ ጠንካራ የሆነ ቁጥጥር እና ህግ የማስከበር ስራ የምንሰራ ይሆናል ብለዋል።            
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም