ፖለቲካ
የድሬዳዋ አስተዳደር ምክር ቤት 8ኛ መደበኛ ጉባዔውን ዛሬ ማካሄድ ጀመረ
Aug 5, 2024 133
ድሬዳዋ፤ሐምሌ 29/2016 (ኢዜአ)፡-የድሬዳዋ አስተዳደር ምክር ቤት 3ኛ ዙር 3ኛ የሥራ ዘመን 8ኛ መደበኛ ጉባዔውን ዛሬ ማካሄድ ጀመረ። በጎፋ ዞን በደረሰው አደጋ የህሊና ፀሎት በማድረግ የተጀመረው እና ለሁለት ቀናት የሚቆየው 8ኛ መደበኛ ጉባዔው በተለያዩ አጀንዳዎች ላይ የሚመክር መሆኑን የምክር ቤቱ ምክትል አፈ ጉባኤ ወይዘሮ ከሪማ ዓሊ ተናግረዋል። ምክር ቤቱ በጉባዔው የአስፈፃሚውን እና የማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎት የስራ አፈፃፀም ሪፖርት እና በተያዘው በጀት ዓመት መሪ ዕቅድ ላይ ተወያይቶ ያፀድቃል ተብሏል። በተጨማሪም የምክር ቤት ፅህፈት ቤት እና ለምክር ቤቱ ተጠሪ የሆኑ የመገናኛ ብዙሃን ድርጅቶች፣ የዋናው ኦዲተር እና የድሬዳዋ አስተዳደር ፍርድ ቤቶች የስራ አፈፃፀሞች ላይ ተወያይቶ የሚያፀድቅ መሆኑን የጉባዔው አጀንዳ ያመለክታል። ከዚህ ባሻገር ምክር ቤቱ የድሬዳዋ አስተዳደር አስፈፃሚ እና የማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎት አካላትን እንደገና ለማቋቋም እና ተግባርና ኃላፊነታቸውን ለመወሰን በወጣ ረቂቅ አዋጅ ላይ ተወያይቶ ያፀድቃል ተብሎ ይጠበቃል። ጉባዔው የዘንድሮ በጀት ዓመት የበጀት ረቂቅ በማፅድቅ እና የተለያዩ ሹመቶችን እንደሚሰጥ ይጠበቃል። ጉባዔው የድሬዳዋ ከንቲባ ከድር ጁሃር፣ የአስፈፃሚውን እና የማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎት የስራ አፈፃፀም ሪፖርት ለጉባዔው እያቀረቡ ይገኛል። በ2000 ዓ.ም የተመሠረተው የድሬዳዋ አስተዳደር ምክር ቤት 189 አባላት እንዳሉት ይታወቃል።  
የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን በጋምቤላ ክልል ሲያካሂድ የቆየውን የአጀንዳ ማሰባሰብ ሂደት ዛሬ አጠናቀቀ
Aug 4, 2024 192
ጋምቤላ፤ ሐምሌ 28/2016(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን በጋምቤላ ክልል ሲያካሂድ የቆየውን የአጀንዳ ማሰባሰብ ሂደት ዛሬ አጠናቀቀ። ተሳታፊዎች በቆይታቸው ለሀገር ይበጃሉ ያሏቸውን አጀንዳዎች በማሰበሳብ በመረጧቸው ኮሚቴዎች አማካኝነት ለሀገራዊ ምክክር ኮሚሽኑ በአደራ አስረክበዋል ። የምክክር ኮሚሽን ኮሚሽነር መላኩ ወልደማሪያም በመድረኩ ማጠቃለያ ላይ እንዳሉት በክልሉ ካለፈው ሐምሌ 22 ቀን 2016 ዓ.ም ጀምሮ ሲካሄድ የቆየው የአጀንዳ ማሰበሳብ ሂደት ዛሬ በስኬት ተጠናቋል።   በአጀንዳ ማሰባሰብ ሂደቱ ሁሉም ባለድርሻ አካላት ለኢትዮጵያ ዘላቂ ሰላምና መፃኢ እድል ይበጃሉ ያሏቸውን ሃሳቦች በነፃነት በማዋጣት ረገድ መልካም ተሳትፎ የታየበት ነበር ብለዋል። ተሳታፊዎች ለህዝብና ለሀገር ይጠቅማሉ ያሏቸውን አጀንዳዎች በመለየትና በማሰባሰብ ረገድ ላሳዩት የነቃ ተሳትፎም ኮሚሽኑ ከፍተኛ ምስጋና እንዳለው ገልጸዋል። እንዲሁም በክልሉ ለአንድ ሳምንት ያህል ሲካሄድ የቆየው የአጀንዳ ማሰባሰብ ሂደት ያለምንም ችግር በስኬት እንዲጠናቀቅ ላደረጉ ተባባሪ አካላት ሁሉ ኮሚሽኑ የላቀ ምስጋና እንዳለው ኮሚሽነር መላኩ ተናግረዋል። በቀጣይም ኢትዮጵያ ያሉባትን ችግሮች በውይይት የምትፈታ ሀገር የሚለው ስም እንዲኖራት ለሀገር ዘላቂ ሰላም የጀመሩትን ፋና ወጊ ተግባር አጠናክረው እንዲቀጥሉ ኮሚሽነር መላኩ ጠይቀዋል።    
አዲስ የሚወጡና የሚሻሻሉ አዋጆች በልዩ ጥንቃቄ ታይተውና ሰፊ ውይይት ተደርጎባቸው የሚጸድቁ ናቸው- የምክር ቤቱ ቋሚ ኮሚቴ
Aug 4, 2024 254
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 28/2016(ኢዜአ)፦ አዲስ የሚወጡና የሚሻሻሉ አዋጆች በልዩ ጥንቃቄ ታይተውና ሰፊ ውይይት ተደርጎባቸው የሚጸድቁ መሆኑን በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የህግና ፍትህ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ገለጸ። በምክር ቤቱ የህግና ፍትህ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ እጸገነት መንግስቱ፤ በምክር ቤቱ የህግ ማርቀቅና ማጽደቅ ሂደት ሰፊና ጥልቅ የአሰራር ሂደቶችን የተከተለ መሆኑን ገልጸዋል። ለምክር ቤቱ በሚቀርቡ ረቂቅ ህጎች ዙሪያ የመንግስት ተጠሪ በኩል ለምክር ቤት አባላት ሰፊ ገለፃና ማብራሪያ የሚሰጥ ስለመሆኑ አንስተዋል። በዚህም መሰረት ምክር ቤቱ በቋሚ ኮሚቴው ረቂቅ ህጎች በዝርዝር እንዲፈትሹ የሚደረግ መሆኑን ገልጸዋል። ለዝርዝር እይታ የተመራላቸው ቋሚ ኮሚቴዎችም ባለድርሻ አካላትን በማሳተፍ በረቂቅ ህጉ ላይ ጥልቅ ውይይት የሚያደርጉበት አሰራር መሆኑን ሰብሳቢዋ ተናግረዋል። ከህገ-መንግስቱና ከዓለም አቀፍ ድንጋጌዎች ጋር እንዳይጣረሱ በልዩ ልዩ መንገዶች የማጣራት ስራ የሚከናወን መሆኑንም አስረድተዋል። በመሆኑም እነዚህን አሰራሮች በተከተለ መልኩ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ለምክር ቤቱ ከቀረቡ 52 አዋጆች መካከል 42ቱ መጽደቃቸውን ጠቁመዋል። ለዚህም የባለድርሻ አካላትና በረቂቅ አዋጁ ላይ ይመለከተኛል የሚሉ ግለሰቦች በነጻነት እንዲሳተፉ የህዝብ ተሳትፎ መድረኮች እንደሚመቻቹ ነው ያብራሩት። በምክር ቤቱ አዲስ የሚወጡም ሆኑ የሚሻሻሉ አዋጆች ሀገርና ህዝብን የሚጠቅሙና ለረጅም ዓመታት የሚያገለግሉ በመሆናቸው በልዩ ጥንቃቄ ታይቶ ሰፊ ውይይት ተደርጎባቸው የሚጸድቁ መሆኑን ገልጸዋል። ምክር ቤቱ በቀጣይም በሚያወጣቸው ህጎች ተፈጻሚነት ላይ ጥናትና ምርምር በማድረግ የመፈተሽ ስራ የሚሰራ ክፍል እንደሚያደራጅ ተናግረዋል። በምክር ቤቱ የሚወጡ ህጎች የታለመላቸውን ዓላማ እንዲመቱ የእያንዳንዱ ዜጋ ትብብርና ተሳትፎ ወሳኝ መሆኑን አስገንዝበዋል።
በምክክር መድረኩ የተፈጠረውን ምቹ አጋጣሚ ተጠቅመን በመግባባት ለዘላቂ ሠላም የድርሻችንን እንወጣለን 
Aug 3, 2024 214
ጋምቤላ፤ ሐምሌ 27/2016(ኢዜአ)፡- በምክክር መድረኩ የተፈጠረውን ምቹ አጋጣሚ በመጠቀም በመግባባት ለአገራዊ ዘላቂ ሠላም የድርሻቸውን እንደሚወጡ በጋምቤላ ክልል የሚንቀሳቀሱ የፖለቲካ ፓርቲ ተወካዮች ገለጹ። የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን በጋምቤላ ክልል እያካሄደ ያለው አጀንዳ ማሰባሰብ ሂደት እንደቀጠለ ነው። በምክክሩ በመሳተፍ ላይ የሚገኙ የፖለቲካ ፓርቲ ተወካዮች ለኢዜአ በሰጡት አስተያየት፤ ከምንም በላይ የህዝብና የአገርን ዘላቂ ሠላምና ጥቅም በሚያረጋገጡ ጉዳዮች ሃሳብ በማዋጣት ድርሻቸውን እንደሚወጡ አስታውቀዋል። ከተሳታፊዎች መካከል የኢዜማ ተወካይ ኮማንደር ጋድቤል ቦል እንዳሉት፤ በምክክሩ ህዝብና አገርን ይጠቅማሉ ያሏቸውን ሀሳብ አዋጥተዋል።   ''ከህዝብና ከአገር የሚበልጥ ነገር የለም'' ያሉት ኮማንደር ጋድቤል፣ ሁላችንም በመግባባት የአገሪቷን ሠላም በዘላቂነት ለማረጋገጥ የድርሻቸውን እንደሚወጡ ገልጸዋል። የህዝብና የአገርን ሠላም ለማረጋገጥ ሁሉም ባለድርሻ አካላት በጋራ ሊሰሩ ይገባል ያሉት ደግሞ የጋምቤላ ብሔራዊ ዴሞክራሲ ንቅናቄ/ ጋብዴን/ ተወካይ አቶ ኡቦንግ ኡሞድ ናቸው።   የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን እየተካሄደ ያለው አጀንዳ የማሰባሰብ ሂደት ኢትዮጵያ ከችግር የምትወጣበት መንገድ መሆኑን እንደሚያምኑ ተናግረዋል። እንደ ፖለቲካ ፓርቲም የህዝብና የአገር ሠላምና ብሔራዊ ጥቅም በሚነኩ ጉዳዮች አንድ ዓይነት አቋም መያዝ ይጠበቅብናል ብለዋል አቶ ኡቦንግ። በፖለቲካው ዓለም በምርጫ አሸንፎ መምራት የምትችለው ህዝብና አገር ሠላም ሲሆን ብቻ ነው ያሉት ተወካዩ፤ ሁላችንም ለአገር ዘላቂ ሠላም ቅድሚያ ሰጥተን መስራት ይጠበቅብናል ሲሉም አስተያየታቸውን ሰጥተዋል። ሌላው የመድረኩ ተሳታፊ የጋምቤላ ህዝቦች ነፃነት ንቅናቄ/ጋህነን/ተወካይ አቶ ኡኮች ኡሞድ፤ የአገርን ችግር ለመፍታት ሁሉም የፖለቲካ ፓርቲዎች በመግባባት ዘላቂ ሠላም እንዲሰፍን ልንሰራ ይገባናል ብለዋል።   ''የማያግባቡ ሃሳቦችን በኃይል አማራጭ ለመፍታት የሚደረግ እንቅስቃሴ ተቀባይነት የሌለው ተግባር ነው'' ያሉት ተወካዩ፣ በምክክር መድረኩ የተፈጠረውን ምቹ አጋጣሚ በመጠቀምና መግባባት ላይ መሥራት ይጠበቅብናል ሲሉ ሐሳባቸውን ሰጥተዋል።      
በምክክር ሀገራዊ አንድነትን እውን ለማድረግ የተጀመረው ጉዞ ስኬታማ እንዲሆን ዜጎች ንቁ ተሳትፏቸውን ሊያጠናክሩ ይገባል- ዶክተር ተገኘወርቅ ጌቱ
Aug 3, 2024 211
ድሬዳዋ ሐምሌ 27/2016 (ኢዜአ)፡- በአካታችና ነጻ ህዝባዊ ምክክር ሀገራዊ አንድነትን እውን ለማድረግ የተጀመረው ጉዞ ስኬታማ እንዲሆን ዜጎች ንቁ ተሳትፏቸውን እንዲያጠናክሩ የኢትዮጵያ አገራዊ የምክክር ኮሚሽነር ዶክተር ተገኘወርቅ ጌቱ ተናገሩ። ኮሚሽኑ በድሬዳዋ አስተዳደር እና በሐረሪ ክልል ከነሐሴ ስድስት ጀምሮ አጀንዳ ለማሰባሰብ ምክክር ያካሂዳል። በዛሬው ዕለት የኢትዮጵያ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ምክር ቤት በድሬዳዋ በሚካሄደው የአጀንዳ ማሰባሰብ ውይይት ላይ ለሚሳተፉትና ድሬዳዋ ከሚገኙት የሲቪል ማህበራት ጋር የግንዛቤ ማስጨበጫ ውይይት አካሂዷል። በውይይቱ ላይ የተሳተፉት የአገራዊ ምክክር ኮሚሽን ኮሚሽነር ተገኘወርቅ ጌቱ (ዶ/ር) እንደተናገሩት ፤ኮሚሽኑ በየክልሉና በከተማ አስተዳደሮች በህዝብ ከተመረጡ ወኪሎች ጋር ለአገራዊው ምክክር የሚጠቅሙ አጀንዳ የማሰባሰብ ሥራ እያካሄደ ነው። ባለፈው ሳምንት ከቤኒሻንጉል እና ከጋምቤላ ክልሎች ከተመረጡ የህዝብ ወኪሎች፣ ከፖለቲካ ፓርቲዎች፣ ከሲቪል ማህበራት እና ከሚመለከታቸው ወኪሎች ጋር በመምከር አጀንዳ አሰባስቦ አጠናቋል ብለዋል። ከነሐሴ ስድስት ጀምሮ በድሬዳዋ አስተዳደር እና በሐረሪ ክልል አጀንዳ ለማሰባሰብ የውይይት መድረኮች እንደሚያካሂድም አስረድተዋል። ነጻ፣ አካታች እና ገለልተኛ በሆነው መንገድ ከሚካሄደው ውይይት አገራዊ መግባባት የሚፈጥሩ አጀንዳዎች እንደሚሰበሰቡም ነው ዶክተር ተገኘወርቅ የገለፁት። ተቻችለን፣ ተረጋግተንና ተደማምጠን በመወያየት ብሎም ሰጥተን በመቀበል ነው ወደፊት መዝለቅ የምንችለው ያሉት ኮሚሽነሩ፣ በሰላም፣ በመመካከርና በመተባበር ከተሰራ አገርን የሚያፀኑ ውጤቶችን ማግኘት እንችላለን ብለዋል። እንደ ኮሚሽነር ተገኘወርቅ ጌቱ (ዶ/ር) ገለፃ ድህነትና በሰላም እጦት መድቀቅ እንዲያከትም ሁሉም በሀገራዊ ምክክሩ ኃላፊነቱን በአግባቡ መወጣት አለበት። የሲቪል ማህበራት ባላቸው ህዝባዊ ኃላፊነት እና ልምድ በአጀንዳ ማሰባሰቡ ላይ የነቃ ተሳትፏቸውን ማጠናከር እንዳለባቸውም ጠቁመዋል። የኮሚሽኑ የአጀንዳ እና የምክክር አስተባባሪ አቶ ተመስገን አብዲሳ ከነሐሴ ስድስት ጀምሮ ለ10 ተከታታይ ቀናት አስቀድመው ከድሬዳዋ አስተዳደር ከከተማ እና ገጠር ወረዳዎች በህዝብ ከተመረጡ ወኪሎች ጋር አጀንዳ የማሰባሰብ ውይይት ይካሄዳል ብለዋል። በውይይቱም የሁሉም ህብረተሰብ ወኪሎች፣ የፖለቲካ ፓርቲዎች፣ የሃይማኖት ተቋማት፣ የሲቪል ማህበራት፣ የመንግስት አካላት እና ተፅዕኖ ፈጣሪ ግለሰቦች እንደሚሳተፉ አስረድተዋል። በአጀንዳ ማሰባሰብ የውይይት መድረክ ላይ የሚሳተፉት አካላት በነፃነት፣ በገለልተኝነት እና በእኩልነት ለሀገራዊ ምክክሩ የሚጠቅሙ አጀንዳዎችን ያቀርባሉ ብለዋል።  
በክልሉ ሠላም  በዘላቂነት ተጠብቆ ልማቱ እንዲፋጠን ሚናቸውን እንደሚወጡ የምክር ቤት አባላት ገለጹ
Aug 3, 2024 214
ባህር ዳር ፤ሐምሌ 27/ 2016 (ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል ሠላምን በዘላቂነት በማስጠበቅ ልማቱ እንዲፋጠን የክትትልና የድጋፍ ተግባራቸውን እንደሚያጠናክሩ የክልሉ የምክር ቤት አባላት ገለጹ። ሠላም ለዘላቂ ልማትና እድገት ያለውን ፋይዳ በመገንዘብ ሁሉም የድርሻውን መወጣት እንዳለበትም የምክር ቤቱ አባላት አመልክተዋል። በምክር ቤቱ ከሰሜን ወሎ ዞን ግዳን ምርጫ ክልል የተወከሉት አቶ ጋሻው አስማሜ ለኢዜአ እንደተናገሩት፤ በክልሉ ሠላምን ለማስፈን ህዝቡ አካባቢውን በመጠበቅ የበኩሉን አስተዋጽኦ እንዲያበረክት ተከታታይ ውይይት እየተደረገ ነው። ችግር ውስጥ የገቡ ወገኖች ተመልሰው ከመንግስት ጋር ተቀራርበው በመወያየት ለችግሩ እልባት ሊሰጡ እንደሚገባ አመልክተዋል። ተመራጭ የምክር ቤት አባላትም ህዝብን በማወያየት የክልሉ ሰላም እንዲፀናና የታቀዱ የልማት ስራዎች እንዲሳኩ ለሠላም ዋጋ መክፈል አለብን ብለዋል። የክልሉ ሠላም በዘላቂነት ተጠብቆ ልማቱ እንዲፋጠን እኔም ለመረጠኝ ህዝብ የሰላምን ዋጋ አጥብቄ በማስረዳት የድርሻዬን ለመወጣት ዝግጁ ነኝ ብለዋል። ከሰሜን ሸዋ ዞን ግሼራቤል ምርጫ ክልል በምክር ቤቱ የተወከሉት አቶ አበራ ፈንታው በበኩላቸው፤ ያለሠላም መንቀሳቀስም ሆነ ልማትን ማፋጠን እንደማይቻል ተናግረዋል።   ሠላም ሰፍኖ ልማቱ ተጠናክሮ እንዲቀጥል የምክር ቤት አባላት ሚና ከፍ ያለ እንደሆነ ጠቅሰው፤ እሳቸውም በተመረጡበት አካባቢ ሰላም እንዲመጣ የክትትልና ድጋፍ ተግባራቸውን በማጠናከር ሚናቸውን እንደሚወጡ ገልጸዋል። ሠላም ለዘላቂ ልማትና እድገት ያለውን ፋይዳ በመገንዘብ ሁሉም ህብረተሰብ ለዘላቂ ሠላም እውን መሆን ሊሰራ እንደሚገባ አመለክተዋል። ማንኛውም አካል ችግሩን በውይይት ሊፈታ እንደሚገባ ጠቅሰው ፤ይህ እንዲሳካም ድጋፋቸውን ለማጠናከር ዝግጁ መሆናቸውን አስታውቀዋል። በክልሉ ዘላቂ ሠላም እንዲሰፍን " ሁላችንም የድርሻችንን መወጣት ይኖርብናል" ያሉት ደግሞ ከደቡብ ወሎ ዞን ተንታ ወረዳ ምርጫ ክልል የተወከሉት አቶ አሰፋ ይመር ናቸው።   ከመረጠን ህዝብ ጋር በጋራ ሃሳቦች ላይ የጋራ ግንዛቤ በመፍጠር ሁላችንም ለሠላም ትኩረት ሰጥተን በመስራት ልማቱን ልናፋጥን ይገባል ሲሉም ተናግረዋል። ሠላም ተጠብቆ ልማቱ እንዲፋጠን የክትትልና ድጋፍ ሥራቸውን አጠናክረው ሚናቸውን እንደሚወጡ ገልጸዋል።። በመጠፋፋት የምናገኘው ትርፍ አለመኖሩን በመገንዘብ በክልሉ ዘላቂ ሠላም እውን እንዲሆን ሁላችንም ተቀራርበን ችግሮችን በውይይት ልንፈታ ይገባል ሲሉም አስገንዝበዋል። ችግር ውስጥ የገቡ ወገኖች የሠላም ካውንስል ያቀረባውን የሠላም አማራጭ በመቀበል ለተግባራዊነቱ መዘጋጀት እንዳለባቸው የምክር ቤቱ አባላት አመልክተዋል። የአማራ ክልል ምክር ቤት ከሐምሌ 22 እስከ 25 ቀን 2016 ዓ.ም ሲያካሄድ የቆየው 8ኛ መደበኛ ጉባኤ በተለያዩ አጀንዳዎች ላይ በመምከርና ውሳኔዎችን በማሳለፍ ማጠናቀቁን በወቅቱ ተገልጿል።  
4ኛው ዓለም አቀፍ የፋይናንስ ለልማት ቅድመ ጉባኤ የኢትዮጵያን ገፅታ በመገንባት የጎላ ድርሻ እንደነበረው ተገለጸ
Aug 2, 2024 205
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 26/2016(ኢዜአ)፦በአዲስ አበባ የተካሄደው 4ኛው ዓለም አቀፍ የፋይናንስ ለልማት ቅድመ ጉባኤ የኢትዮጵያን ገፅታ በመገንባትና ቱሪዝምን በማስተዋወቅ የጎላ አስተዋጽኦ ማበርከቱን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ገለጸ። የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አምባሳደር ነብዩ ተድላ በወቅታዊ የኢትዮጵያ ዲፕሎማሲና የውጭ ግንኙነት ላይ ሳምንታዊ መግለጫ ሰጥተዋል። ቃል አቀባዩ፤ ዓለም አቀፍ የፋይናንስ ለልማት ቅድመ ጉባኤ የዘላቂ ልማት ግቦችን ለማሳካት የሚያስፈልገውን የፋይናንስ አቅርቦት ለማፈላለግ ያለመ ውይይት የተደረገበት እንደነበር አስታውሰዋል። በጉባኤው ከ40 በላይ የሚሆኑ ሚኒስትሮችን ጨምሮ ከአንድ ሺህ በላይ ተሳታፊዎች የተገኙበት ኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ ስብሰባዎችን የማስተናገድ የዳበረ አቅም እንዳላት ያረጋገጠ ነበር ብለዋል፡፡ ከጉባኤው ባሻገር 12 የጎንዮሽ ውይይቶች መደረጋቸውን ጠቅሰው፣ በሰላም፣ በጸጥታና በልማት ላይ የኢትዮጵያን ነባራዊ ሁኔታ ያስረዳንበት መድረክ ነው ብለዋል። ኢትዮጵያ በዲፕሎማሲ፣ ቱሪዝምና ገጽታ ግንባታ ዘርፍ ውጤት ያገኘችበት ጉባኤ እንደነበርም ገልጸዋል። ከዚህም በተጨማሪ ስምሪት የተሰጣቸው 24 አዳዲስ አምባሳደሮች የሀገራቸውን ብሄራዊ ጥቅም ለማስጠበቅ በኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ ፊት ቃል መግባታቸውን ተናግረዋል። አዳዲስ ተሿሚ አምባሳደሮች ያዳበሩትን ልምድና እውቀት ተጠቅመው ለሀገራቸውም ብሔራዊ ጥቅምና ሉዓላዊነት መከበር በትጋት እንዲሰሩ ሀላፊነት ተሰጥቷቸዋል ብለዋል፡፡ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አምባሳደር ታዬ አፅቀስላሴ አምባሳደሮች ልምዳቸውንና የወሰዱትን ስልጠና ተጠቅመው ዘመኑን የዋጀ ዲፕሎማሲያዊ እንቅስቃሴ እንዲያደርጉ ማሳሰባቸውንም አስታውሰዋል፡፡ ቃል አቀባዩ በሳምንታዊ መግለጫቸው ያነሱት ሌላው ጉዳይ፤ የኢትዮጵያ መንግስት የሥራ ስምምነት ባልፈጸመባቸው የኤዥያ ሀገራት በህገ- ወጥ መንገድ የሚሰደዱ ዜጎችን ከሀገራት ጋር በመነጋገር እየመለሰ መሆኑን ገልፀዋል፡፡ በተለይም ተታለው ወደ ታይላንድና ማይናማር የሄዱ ዜጎችን ጃፓንና ህንድ ባሉ የኢትዮጵያ ሚሲዮኖች አማካኝነት እንዲመለሱ ተደርጓል ብለዋል፡፡ ህብረተሰቡም የኢትዮጵያ መንግስት ከነዚህ ሀገራት ጋር ምንም አይነት የሥራ ስምሪት ውል አለመፈራረሙን ተረድቶ ከህገወጥ ደላሎችና አዘዋዋሪዎች ራሱን እንዲጠብቅ መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡ ከዚህም ባለፈ በቱርክ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር የተመራ የልዑካን ቡድን ነገ አዲስ አበባ ይገባል ብለዋል።        
የአማራ ክልልን ሰላም ለማረጋገጥና አሻጋሪ ልማቶችን በውጤት ለመፈጸም የአመራሩ ቁርጠኝነት ወሳኝ ነው
Aug 2, 2024 184
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 26/2016(ኢዜአ)፦ የአማራ ክልልን ሰላም ለማረጋገጥና አሻጋሪ ልማቶችን በውጤት ለመፈጸም የአመራሩ ቁርጠኝነትና ዲስፕሊን ወሳኝ መሆኑን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። የአማራ ክልል ከፍተኛና መካከለኛ አመራሮች የ2016 በጀት ዓመት አፈጻጸምና የ2017 ዕቅድ የውይይት መድረክ መካሄድ ጀምሯል። በውይይቱ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ፤ የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አረጋ ከበደ፣ የክልሉ ከፍተኛና መካከለኛ አመራሮች ተገኝተዋል። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ፤ የአማራ ክልልን ሰላም ለማረጋገጥና አሻጋሪ ልማቶችን በውጤት ለመፈጸም አመራሩ በቁርጠኝነትና በዲሲፕሊን ሊሰራ እንደሚገባ ተናግረዋል። የክልሉ መንግሥት በ2016 በጀት ዓመት በግጭት ውስጥም ሆኖ በርካታ የልማት ሥራዎችን ማከናወኑን ጠቅሰዋል። ለአብነትም በፌደራል መንግሥቱ የተገነቡ አዲሱ የዓባይ ድልድይ፣ የጎርጎራ ኢኮ ሪዞርትና ሌሎችንም ጠቅሰዋል። በግብርናው መስክም ትልቅ ውጤት መምጣቱን አንስተው፤ በገቢ አሰባሰብ በችግር ውስጥ ሆኖ ከባለፈው በጀት ዓመት የተሻለ ገቢ መሰብሰቡን ገልጸዋል። በ2017 በጀት ዓመትም ክልሉን ከነበረበት ነባራዊ ችግር ለማሻገርና የህዝቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የተዘጋጀውን ዕቅድ በአግባቡ መተግበር ከአመራሩ ይጠበቃል ነው ያሉት። ዕቅዱን በአግባቡ ለመፈጸም የክልሉ አመራር በዲሲፕሊን መምራት እና ቁርጠኛ መሆን እንዳለበት አንስተዋል። በዕቅዱ የተለዩ ፀጋዎችን በማልማት ወደ ሀብት ለመቀየር ውጤት ተኮር የሆነ አደረጃጀትንና የአመራር ስልትን መከተል ይገባል ብለዋል። በመሆኑም በአዲሱ በጀት ዓመት የተጀመረውን ሠላምና ልማት አጠናክሮ በመቀጠል የክልሉን ዕምቅ አቅምና ተስፋ ወደ ተጨባጭ ውጤት መቀየር እንደሚገባ አሳስበዋል።
ክልሉን ወደ ተሻለ ምዕራፍ ለማሻገር የቁጭት ዘመን ዕቅድ አዘጋጅተናል - ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ
Aug 2, 2024 181
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 26/2016(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል ያጋጠሙ ችግሮችን ወደ ዕድል በመቀየር ክልሉን ወደ ተሻለ ምዕራፍ ለማሻገር የቁጭት ዘመን ዕቅድ መዘጋጀቱን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ ገለጹ። የአማራ ክልል ከፍተኛና መካከለኛ አመራሮች የ2016 በጀት ዓመት አፈጻጸምና የ2017 ዕቅድ የውውይት መድረክ መካሄድ ጀምሯል። በውይይቱ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ፣ የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አረጋ ከበደ፣ የክልሉ ከፍተኛና መካከለኛ አመራሮች ተገኝተዋል። የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አረጋ ከበደ፥ የ2016 በጀት ዓመት ዋነኛ ትኩረት ሆኖ ያለፈው የፀጥታ ችግሮችን በመቅረፍ መረጋጋትን የማስፈን ስራ እንደሆነ ተናግረዋል። በዚህም ለልማት ምቹ ምህዳር የመፍጠር ስራ መከናወኑን ጠቅሰው፥ አንፃራዊ ሰላም ባለባቸው አካባቢዎች በግብርናና ሌሎች መስኮች ውጤት መመዝገቡን ገልጸዋል። ዘላቂ ሰላምን የመገንባት፣ የመልካም አስተዳደር ሥራን የማስፈን ተግባራትም መከናወናቸውን ጠቅሰዋል። በአዲሱ 2017 በጀት ዓመትም ከዚህ ቀደም በተለያዩ ችግሮች ያልተሳኩ ዕቅዶችን ለማካካስና የበጀት ዓመቱን ዕቅድ በአግባቡ ለመፈጸም ዝግጅት መደረጉን ገልጸዋል። የ2017 በጀት ዓመት ትኩረት ሰላምን በየአካባቢው በማረጋገጥ ለቀጣይ ዓመታት የልማት ሥራዎች አስተማማኝ መሠረት መጣል እንደሆነም ጠቅሰዋል። ለዚህም በርካታ ጠመዝማዛ መንገድን ማለፍ እንደሚጠይቅ አመራሩ መገንዘብ አለበት ብለዋል። በተለይም አመራሩ ችግሮችን በልዩ ትኩረት፣ በቅንጅትና በትብብር መሻገር እንዳለበት አሳስበዋል። ሥራችን የህዝብን ጥያቄ የመመለስና የህልውና ጉዳይ ነው ያሉት ርዕሰ መስተዳድሩ፥ ህዝቡን ለሰላምና ለልማት ማስተባበር እንደሚገባ አንስተዋል። ክልሉ ያለውን የወደፊት የልማት ርዕይ በዝርዝር ያካተተ ስትራቴጂክ ፎኖተ ካርታና ዕቅድ ማዘጋጀቱንም ገልጸዋል። ዕቅዱ በማክሮ ደረጃ ያሉ ጥንካሬና ድክመቶችን በመለየት የተዘጋጀና ከ2018-2022 ዓ.ም የሚተገበር የቁጭት ዘመን ዕቅድ ነው ብለዋል። የአማራ ክልልን ከግጭት ማግስት ወደ ስኬት ለማሻገር ዕቅዱ ወሳኝ በመሆኑ፥ በ2017 በጀት ዓመት ምቹ መሠረት መጣል እንደሚገባ ጠቁመዋል። ለዚህም አመራሩ የጋራ መግባባት በመፍጠር ለተግባራዊነቱ በቁርጠኝነት መነሳትና ህብረተሰቡን ማስገንዘብ የዚህ በጀት ዓመት ትልቅ ስራ ነው ብለዋል። ያጋጠመንን ችግር ወደ ዕድል በመለወጥ ክልሉን ለማሻገር ህዝብን ያሳተፈ ሰፊ ርብርብ ወሳኝ ነው ብለዋል።  
ዕዙ የአካባቢውን ሰላም የማስከበር ተግባርና የአባላቱን አቅም በስልጠና ማጎልበት በተቀናጀ መልኩ እያከናወነ መሆኑን ገለጸ
Aug 2, 2024 195
ጅማ፤ ሐምሌ 26/2016(ኢዜአ)፦ የዳሎል ማዕከላዊ ዕዝ የአካባቢውን ሰላም የማስከበር ተግባሩን እየፈጸመ በተጓዳኝ የአባላቱን አቅም በስልጠና በማጎልበት የተቀናጀ ስራ እየሰራ መሆኑን ገለጸ። የሀገር መከላከያ ሰራዊት የዳሎል ማዕከላዊ ዕዝ ለሁለት ወራት ያሰለጠናቸውን የሰራዊቱ ስልታዊ አመራር አባላትን አስመረቀ። የዳሎል ማዕከላዊ ዕዝ ምክትል አዛዥ ለኦፕሬሽናል ሜጀር ጄኔራል አብዱሮ ከድር በምረቃው ላይ እንደገለጹት፤ ዕዙ ከሌሎች ዕዞች ጋር በመቀናጀት የአካባቢውን ሰላም እያስከበረ ነው። በአንድ በኩል የአካባቢውን ሰላም የማስከበር ተግባሩን እየፈጸመ በተጓዳኝ የአባላቱን አቅም በስልጠና በማጎልበት የተቀናጀ ስራ እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል። ግዳጅ የመፈጸም አቅማችንን የማሳደግ ስራ የአባላትና አመራሩን አቅም ግንባታ የሚፈልግ በመሆኑ ለአቅም ግንባታ ትኩረት ተሰጥቷል ነው ያሉት። ሲሰጥ የቆየው ስልጠናም ሰራዊቱ በአካል ብቃት እና በስነ-ልቦና ዳብሮ ለሀገሩ ክብር እና ሰላም አስተማማኝ መከታ መሆን የሚችል ስራዊት ለመገንባት እድል እንደሚፈጥር ተናግረዋል። ዕዙ በሚንቀሳቀስበት አካባቢ አሸባሪው የሸኔ ቡድን ላይ ውጤታማ የህግ ማስከበር ስራ እያከናወነ መሆኑንም ጠቅሰዋል። ባለፋት ሁለት ወራት ሰልጥነው የተመረቁ አመራር አባላት በበኩላቸው በስልጠናው የደፈጣ እና መደበኛ ውጊያ ታክቲክና ስልትን ያጠቃለለ እውቀት ማግኘታቸውን ገልጸዋል። ሻለቃ ባያሌው ጥሩነህ፣ ስልጠናው ችግሮችን ቀድሞ በመረዳት የመቆጣጠር ስልት ላይ ተጨማሪ እውቀት ያገኙበት መሆኑን ተናግረዋል። በስልጠናው በመደበኛና በደፈጣ ውጊያ የሚያስፈልጉ መሰረታዊ ታክቲኮችን ሰልጥነን የምንመራቸውን አባላት በዚሁ መሰረት ለማሰማራት ዝግጁ ነን ብለዋል። መቶ አለቃ ዮናስ ብርቁ በበኩላቸው ስልጠናው አጠቃላይ ወታደራዊ ዝግጁነትን ያቀፈ ሲሆን፤ የመሪነት ሚናን የሚያጎለብት እውቀት የቀሰሙበት እንደሆነም አመልክተዋል። በየትኛውም ዓይነት የውጊያ ስልት የአመራር ሚናና ሀላፊነት እስከምን ድረስ እንደሆነ የተማርንበት ብሎም የውጊያ ስልቶችን የተረዳንበት ነው ሲሉ ተናግረዋል።          
የኃይማኖት ተቋማት የአብሮነት እሴትን በማጠናከር በጋራ አገራዊ ጉዳዮች ላይ በስፋት መረባረብ ይጠበቅባቸዋል- ፕሬዝዳንት ሣህለወርቅ ዘውዴ
Aug 1, 2024 316
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 25/2016(ኢዜአ)፦ የኃይማኖት ተቋማት መከባበርና የአብሮነት እሴቱን ሊሸረሽሩ የሚችሉ ጉዳዮችን በመከላከል በጋራ አገራዊ ጉዳዮች ላይ መረባረብ እንዳለባቸው ፕሬዝዳንት ሣህለወርቅ ዘውዴ ተናገሩ። የኢትዮጵያ የኃይማኖት ተቋማት ጉባዔ 16ኛ መደበኛ ጠቅላላ ጉባዔና የዕውቅና መድረክ "በጎ ለዋሉልን እናመስግን፤ ሰላማችንን እንጠብቅ" በሚል መሪ ኃሳብ ተካሂዷል።   በመርኃ-ግብሩ ፕሬዝዳንት ሣህለወርቅ ዘውዴ፣ የሰላም ሚኒስትር ዴኤታ ከይረዲን ተዘራ (ዶ/ር)፣ የኃይማኖት ተቋማት መሪዎችና የተለያዩ እንግዶች ተገኝተዋል። ፕሬዝዳንት ሣህለወርቅ ዘውዴ በዚሁ ጊዜ እንደገለጹት፤ የኃይማኖት መሪዎች በምዕመናን ባላቸው ተሰሚነት ምዕመናን በማስተማር በኩል የሚጫወቱት ሚና ቀላል አይደለም። በጋራ አገራዊ ጉዳዮች ርብርብ እንደሚያስፈልግ ገልጸው፤ በኃይማኖት መካከል የመከባበርና የአብሮነት እሴትን ሊሸረሽሩ የሚችሉ ተግባራትን መከላከል እንደሚገባ ገልፀዋል። ሰላም ከሌለ ልማትና እድገት ማምጣት እንደማይቻል ጠቅሰው፤ ሰላምን ለማፅናት የተባበረ ክንድ እንዲሁም የኃይማኖት አስተምህሮና መንፈሳዊ ድጋፍ ወሳኝ መሆኑን ተናግረዋል። ይህንን ከግምት በማስገባት የኃይማኖት ተቋማት በአገሪቱ ሰላምን ለማረጋገጥ እያከናወኑ ያለውን አዎንታዊ ተግባር አጠናክረው እንዲቀጥሉም ነው ፕሬዝዳንቷ የጠየቁት። የሰላም ሚኒስትር ዴኤታ ከይረዲን ተዘራ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የኃይማኖት ተቋማት አገርን በዘመናት ለማስቀጠል ሚናቸውን ሲወጡ መቆየታቸውን ተናግረዋል።   ኢትዮጵያውያን የአብሮነትና አንድነት እሴቶችን እንዲያዳብሩ የኃይማኖት ተቋማት ሚና ጉልህ እንደሆነም አንስተዋል። ሚኒስቴሩ የኃይማኖት ተቋማት ያላቸውን አቅም ለአገር ግንባታና ለዘላቂ ሰላም ለመጠቀም ከጉባዔው ጋር እያከናወነ ያለውን ሥራ አጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። የጉባዔው የሥራ አስፈጻሚ ቦርድ ሰብሳቢ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ፤ ጉባዔው በሰላምና መከባበር እሴት ግንባታ ላይ በትብብር ለመሥራት የተመሠረተ መንፈሳዊ ተቋም ነው ብለዋል።   ይህንንም ተከትሎ በአገሪቱ ሕዝቦችና የኃይማኖት ተቋማት መካከል ለዘመናት የዘለቀውን የመከባበር፣ የመደጋገፍ ባህልን ለማጠናከርና ለትውልድ ለማስተላለፍ ሲሰራ መቆየቱን ተናግረዋል። የኢትዮጵያ የኃይማኖት ተቋማት ጉባዔ ለሰላም፣ መከባበርና አብሮነት እሴቶችን ማጎልበት የጀመረውን ጥረት ይበልጥ አጠናክሮ እንደሚቀጥል ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ አረጋግጠዋል። በመድረኩ የጉባዔው የ2016 በጀት ዓመት ሪፖርት የቀረበ ሲሆን፤ ለጉባዔው አስተዋጽዖ ያደረጉ ግለሰቦችና ተቋማት ዕውቅና ተሰጥቷቸዋል።
በአማራ ክልል ዘላቂ ሠላምን በማስፈን የታቀዱ የልማት ተግባራትን ለማሳካት ክትትልና ድጋፉ ይጠናከራል- አፈጉባኤ ፋንቱ ተስፋዬ
Aug 1, 2024 233
ባህር ዳር፤ ሐምሌ 25/2016(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል ዘላቂ ሠላምን በማስፈን የታቀዱ የልማትና የመልካም አስተዳደር ተግባራት ለማሳካት ክትትልና ድጋፉ እንደሚጠናከር የክልሉ ምክር ቤት አፈ ጉባኤ ፋንቱ ተስፋዬ ተናገሩ። አፈጉባኤዋ ምክር ቤቱ ያካሄደውን 8ኛ መደበኛ ጉባኤ መጠናቀቁን አስመልክቶ በሰጡት መግለጫ እንዳመለከቱት፤ የክልሉን የልማት ዕቅዶች በተያዘላቸው ጊዜ እንዲፈፀሙ ልዩ ትኩረት ተሰጥቷል። ለዚህም በዋናነት የሰብል ምርታማነትን በማሳደግ ለኢንዱስትሪዎች ግብዓት የሚሆኑና ለኤክስፖርት የሚውሉ ምርቶችን በብዛትና በጥራት ለማምረት ምክር ቤቱ አስፈፃሚውን አካል በመከታተል ድጋፉን እንደሚያጠናክር ገልጸዋል። እንዲሁም የስራ ዕድል ፈጠራን ከግብርናና ኢንዱስትሪ ጋር በማስተሳሰር የሚስተዋለውን የስራ አጥነት ችግር ለመፍታትም እንዲሁ። ለህዝብ የገባነውን ቃል የምንፈፅመው ሠላምን በማስፈንና ልማቱን በማፋጠን የሞት የሽረት ጉዳይ ተደርጎ በመስራት መሆን እንዳለበት ተናግረዋል። የ2017 በጀት ዓመት ዕቅድ በተገቢው መንገድ እንዲፈፀምም ህግ አውጪው፣ ህግ ተርጓሚውና ህግ አስፈፃሚው በተሰጣቸው ኃላፊነት ልክ ተቀናጅተውና ተናበው ሊሰሩ እንደሚገባም አሳስበዋል። በተለይ ሠላሙን አፅንቶ የህዝብ ተሳትፎን በማጠናከር የልማትና የመልካም አስተዳደር ተግባራት በስፋት መከናወን እንዳለባቸው አፈጉባኤዋ አመልክተዋል። የምክር ቤት አባላትም መንግስት ለህዝቡ የገባቸውን ቃሎች ለመፈፀማቸው በልዩ ትኩረት የክትትልና ቁጥጥር ስራቸውን ማከናወን እንዳለባቸው አስገንዝበዋል። ለአሰራር ከፍተት ያለባቸውን ህጎችና ደንቦችን ከማሻሻል ባለፈ የወጡ ህጎች ተፈፃሚ እንዲሆኑም የመከታተልና የመቆጣጠር ሥራቸውን እንደሚያጠናክሩ ገልጸዋል። እንዲሁም ኢኮኖሚው የሚያመነጨውን ገቢ አሟጦ በመሰብሰብ ለልማት ስራው እንዲውል ከማስገንዘብ ባለፈ የፀደቀው በጀት በቁጠባ የልማት ሥራዎች ላይ እንዲውሉ የምክር ቤት አባላት ተገቢውን ሚናቸውን መወጣት እንዳለባቸው ተናግረዋል። ሠላሙን ለማፅናት በየደረጃው ያለው ህብረተሰብ ከፀጥታ ኃይሉ ጋር በመቀናጀት የድርሻውን እንዲወጣም አፈ ጉባኤዋ መልዕክት አስተላልፈዋል። የክልሉ ምክር ቤት 8ኛው መደበኛ ጉባኤ የተለያዩ ሹመቶችን በመስጠት ዛሬ መጠናቀቁን ቀደም ሲል ተገልጿል።
ኢትዮጵያ በባለብዙ ወገን የዲፕሎማሲ መስክ ያላትን ተሳትፎ አጠናክራ ቀጥላለች
Aug 1, 2024 213
አዲስ አበባ ፤ሐምሌ 25 /2016(ኢዜአ)፡- ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ መድረክ በባለብዙ ወገን የዲፕሎማሲ መስክ ያላትን ተሳትፎ አጠናክራ መቀጠሏን በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የኢትዮጵያ ቋሚ መልዕክተኛ አምባሳደር ተስፋዬ ይልማ ገለጹ። አምባሳደር ተስፋዬ ይልማ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ ኢትዮጵያ ከጥንት ጀምሮ በዓለም አቀፍ መድረክ በባለብዙ ወገን የዲፕሎማሲ ዘርፍ ውስጥ የላቀ አስተዋጽዖ ስታበረክት የቆየች አገር መሆኗን አንስተዋል። ኢትዮጵያ ከአፍሪካ በግንባር ቀደም የመንግሥታቱ ማኅበር አባልና ቀጥሎም እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር በ1945 የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ሲመሠረት መሥራች አገራት መካከል አንዷ መሆኗንም ነው የገለጹት። ኢትዮጵያ በተለይም በአፍሪካ በቅኝ አገዛዝ ሥር ወድቀው ለቆዩት የአፍሪካ አገራት ጭምር ድምፅ በመሆን የረዥም ዘመን የባለብዙ ወገን የዲፕሎማሲ መስክ ውስጥ ያላሰለሰ ጥረት ስታደርግ የቆየች አገር መሆኗንም ጠቅሰዋል። በዓለም አቀፍ መድረክ በተለያዩ ጉዳዮች ላይ ንቁ ተሳትፎ ስታደርግ የቆየች አገር መሆኗን አንስተው፤ በዚህም ኢትዮጵያ ከተለያዩ አገራት ጋር ያላትን የባለብዙ ወገን ዲፕሎማሲዋን እያጠናከረች መምጣቷን አስረድተዋል። በሰላምና ጸጥታው ዘርፍ ኢትዮጵያ በመንግሥታቱ ድርጅት እንዲሁም በአፍሪካ ኅብረት ጥላ ሥር በሚመሩ የሰላም ማስከበር ተልዕኮ በመሰማራት ያላት አስተዋጽዖ እጅግ ሰፊ መሆኑን አብራርተዋል። በዚህም በጎረቤት አገራት ዘላቂ ሰላምና መረጋጋት እንዲረጋገጥ ከፍተኛ አበርክቶ ማድረጓን ጠቅሰው፤ በቀጣናውም ሆነ በአፍሪካ ሰላም እንዲሰፍንና ልማትና እድገት እዲሳለጥ የምታበረክተውን አስተዋጽዖ አጠናክራ ትቀጥላለች ብለዋል። በሌላ በኩል ኢትዮጵያ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሳሽነት እያከናወነች ያለው የአረንጓዴ አሻራ መርኃ-ግብር በዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ዘንድ እውቅና እየተሰጠው መምጣቱን ገልፀዋል። ኢትዮጵያ የምታከናውነው የችግኝ ተከላ መርኃ-ግብር የማስተዋወቅ ሥራ በስፋት እየተሰራ መሆኑን ጠቅሰው፤ ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ በኢትዮጵያ የሚተከለውን ችግኝ በቴክኖሎጂ በመታገዝ ግንዛቤ እንዳለው ተናግረዋል።    
ለናይል ትብብር ማዕቀፍ ስምምነት ተፈጻሚነት ኢትዮጵያ የተቀናጀ የዲፕሎማሲ ጥረት በተጠናከረ መልኩ ሊቀጥል ይገባል
Aug 1, 2024 221
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 25/2016(ኢዜአ)፦ለናይል ትብብር ማዕቀፍ ስምምነት ተፈጻሚነት የኢትዮጵያ የተቀናጀ የዲፕሎማሲ ጥረት በተጠናከረ መልኩ ሊቀጥል እንደሚገባ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የውጭ ግንኙነትና ሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አባል ሣዲቅ አደም ገለጹ። የናይል ትብብር ማዕቀፍ ስምምነት እ.አ.አ በ2010 ለፊርማ ክፍት ሆኗል። እ.አ.አ ከ2013 እስከ 2023 ባለው ጊዜ ኢትዮጵያ፣ ሩዋንዳ፣ ታንዛንያ፣ ዩጋንዳና ብሩንዲ ስምምነቱን አጽድቀዋል። ደቡብ ሱዳን እ.አ.አ ሐምሌ 8 ቀን 2024 ማዕቀፉን ያፀደቀች ስድስተኛ ሀገር መሆኗን ተከትሎ ሥምምነቱ ወደ ተፈጻሚነት እንዲገባ የሚያስችል ይሆናል። የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የውጭ ግንኙነትና ሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አባልና የሕግ ባለሙያው አቶ ሣዲቅ አደም የሁለተኛ ዲግሪ የመመረቂያ ጽሁፋቸው በናይል ትብብር ማዕቀፍ ስምምነት አማካኝነት የናይል ተፋሰስ ኮሚሽን መቋቋም ስላለው አንድምታና ጠቀሜታ ላይ ትኩረቱን ያደረገ ነው። የናይል ትብብር ማዕቀፍ ስምምነትና ተፈጻሚነትን አስመልክቶም ከኢዜአ ጋር ቆይታ ያደረጉት አቶ ሣዲቅ፤ የናይል ትብብር ማዕቀፍ ስምምነት እ.አ.አ ከ2010 ጀምሮ ለፊርማ ክፍት ቢሆንም ፀድቆ ወደ ትግበራ ምዕራፍ ለመግባት የ14 ዓመት ጊዜ መውሰዱን ይናገራሉ። እ.አ.አ በ1929 እና በ1959 የተፈጸሙ የቅኝ ግዛት የውሃ ውሎችን ለማስጠበቅ የተፋሰሱን ሀገራት ጫና ውስጥ በመክተት ሲደረጉ የነበሩ ጥረቶች የስምምነቱን ተፈጻሚነት እንደጎተተው አመልክተዋል። ይሁንና ሀገራቱ ጊዜ ያለፈባቸውንና የጋራ ተጠቃሚነትን የማያሰፍኑትን ውሎችን በመተው በውሃ ሀብት አጠቃቀም የጋራ ትብብር የሚፈጥረውን ስምምነት መተግበር አለብን በሚል ባደረጉት ጥረትና ባሳዩት ቁርጠኝነት ማዕቀፉ ወደ ወሳኝ ምዕራፍ ተሸጋግሯል ብለዋል። የናይል ትብብር ማዕቀፍ ስምምነት ወደ ትግበራ ደረጃ መሸጋገር የቅኝ ዘመን ውሎችን ዋጋ የሚያሳጣና በውሃ ሀብት አጠቃቀም ላይ ከዚህ በፊት የነበሩ ጊዜያዊ ማዕቀፎች ወደ ቋሚ አሰራር እንደሚያሸጋግር ነው የምክር ቤቱ አባሉ የገለጹት። በስምምነቱ ተፈጻሚነት ወቅት የናይል ተፋሰስ ኮሚሽን እንደሚቋቋምና ኮሚሽኑ የውሃ ሀብትን በፍትሐዊነትና በሚዛናዊነት የመጠቀም ጉዳይ ላይ እንደሚሰራ አስረድተዋል። በተጨማሪም ስምምነቱ “እኔ ብቻ ልጠቀም” በሚል ለረጅም ጊዜ የቆየውን የተሳሳተ እሳቤ በመቀየር በውሃ ሀብት ትብብር ላይ አዲስ የትርክት ለውጥ እንዲመጣ ትልቅ አስተዋጽኦ እንዳለው አንስተዋል። የትብብር ስምምነቱ ገቢራዊ መሆን ስምምነቱን ያልፈረሙና ያላጸደቁ ሀገራት ወደ ማዕቀፉ እንዲመጡ ከማድረግ አንጻር በጎ ተጽእኖ እንደሚኖረው አመልክተዋል። በተጨማሪም ስምምነቱ ዓለም አቀፍ ተቀባይነት በማምጣት የቴክኒክ፣ የገንዘብና የዲፕሎማሲ ድጋፎችን ለማግኘት እድል እንደሚፈጥር ተናግረዋል። ኢትዮጵያ የናይል ትብብር ማዕቀፍ ስምምነትን የፈረመችና ያጸደቀች የመጀመሪያ ሀገር መሆኗን ጠቅሰው ስምምነቱ አሁን ወዳለበት ምዕራፍ እንዲሸጋገር በዲፕሎማሲና በሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነት መስክ የተከናወኑ ስራዎች ወሳኝ እንደነበሩም አመልክተዋል። ኢትዮጵያ የማዕቀፉ ተግባራዊነት ረጅም ጊዜ እንዳይወስድና በፍጥነት ተፈጻሚ እንዲሆን የተቀናጀ የዲፕሎማሲ ስራ ማከናወን እንዳለባት ጠቅሰው ለዚህም ከተፋሰሱ ሀገራት ጋር በትብብር መስራት ይኖርባታል ብለዋል። ኢትዮጵያ የተለያዩ የዲፕሎማሲ አማራጮችን በመከተል ስምምነቱ ያለውን ፋይዳ ለዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ማስረዳት እንደሚጠበቅባትም ነው የተናገሩት። የተፋሰሱ ሀገራት የጋራ ጥረት በማድረግ ስምምነቱን ወደ ትግበራ እንዲገባ አበክረው መስራት እንደሚጠበቅባቸውና የስምምነቱ ዝርዝር ተፈጻሚት ላይ ያሉ ጉዳዮች ላይ ውይይቶችን ማካሄድ እንዳለባቸው ገልጸዋል። ስምምነቱን ያልፈረሙና ያላፀደቁ ሀገራትም ፍትሐዊና የጋራ ተጠቃሚነትን የሚያሰፍነውን ስምምነት ተቀብለው ለማዕቀፉ ውጤታማነት አስተዋጽኦ ማድረግ እንደሚጠበቅባቸው አመልክተዋል። የሲቪክ ማህበረሰብ ተቋማት፣ ምሁራንና የተለያዩ ባለድርሻ አካላትም ለማዕቀፉ ገቢራዊነት የበኩላቸውን አስተዋጽኦ ማድረግ እንደሚኖርባቸውም አክለዋል።  
የአማራ ክልል ምክር ቤት  መደበኛ ጉባኤ ሹመቶችን በማፅደቅ ተጠናቀቀ
Aug 1, 2024 288
ባህር ዳር፤ ሐምሌ 25/2016(ኢዜአ)፡- የአማራ ክልል ምክር ቤት በርዕሰ መስተዳድር አቶ አረጋ ከበደ የቀረቡ የተለያዩ ሹመቶችን ተቀብሎ በማፅደቅ መደበኛ ጉባኤውን አጠናቀቀ። የክልሉ ምክር ቤት 6ኛ ዙር፣ 3ኛ ዓመት የስራ ዘመን፣ 8ኛ መደበኛ ጉባኤውን ከሐምሌ 22ቀን 2016 ዓ.ም ጀምሮ በተለያዩ ጉዳዮች ሲመክር ቆይቷል። ምክር ቤቱ በቆይታው የክልሉን የ2016 በጀት ዓመት እቅድ ከመገምገም ባሻገር የተያዘው በጀት ዓመት የማስፈፀሚያ በጀት መርምሮ በሙሉ ድምፅ አፅድቋል። እንዲሁም የስነ ምግባር ጉድለት የተገኘባቸውን አራት ዳኞች ከስራ ማሰናበትን ጨምሮ በሌሎች አጀንዳዎች ዙሪያ በመምከር ውሳኔ ማሳለፉ ይታወቃል።   ዛሬ ደግሞ በክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ አረጋ ከበደ የቀረቡ የተለያዩ ሹመቶችን ተቀብሎ አፅድቋል። በዚህም መሰረት፡- 1ኛ- አቶ ዓለምአንተ አግደው- የክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዚደንት፣ 2ኛ- አቶ ሙሉዓለም ቢያዝን - የክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ምክትል ፕሬዚደንት እና 3ኛ- አቶ መልካሙ ፀጋዬ -የክልሉ ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ኃላፊ ሆነው እንዲያገለግሉ የተሾሙ ናቸው።   ተሿሚዎቹ በትምህርት ዝግጅትም ሆነ በስራ የካበተ የስራ ልምድ ያላቸው እንደሆኑ ርዕሰ መስተዳድሩ ለምክር ቤቱ አስረድተዋል። እንዲሁም ምክር ቤቱ ለክልሉ ምክር ቤት ለሰው ሃብት አስተዳደርና ቱሪዝም ልማት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ አበራ ፈንታው፤ ለመንግስት ወጪ ቁጥጥር አስተዳደር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ደግሞ ወይዘሮ እመቤት ከበደ አድርጎ ሹመታቸውን በማፅደቅ ጉባኤው መረሃ ግብሩን አጠናቋል።    
ሰሜን ምዕራብ ዕዝ ግዳጅና ተልዕኮውን በጀግንነት እየተወጣ የሚገኝ ጠንካራ ዕዝ ነው -ጄኔራል አበባው ታደሰ 
Jul 31, 2024 227
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 24/2016(ኢዜአ)፦ የጦር ኃይሎች ምክትል ጠቅላይ ኤታማዦር ሹም ጄኔራል አበባው ታደሰ ሰሜን ምዕራብ ዕዝ በየትኛውም ጊዜና ቦታ የሚሠጠውን ግዳጅና ተልዕኮውን በጀግንነት እየተወጣ የሚገኝ ጠንካራ ዕዝ ነው ሲሉ ተናገሩ። ይህንን ጥንካሬ ማስቀጠልና በቀጣይ ለሚሰጠው ግዳጅና ተልዕኮ በሁሉም መስክ የበለጠ መዘጋጀት ይጠበቅበታል ሲሉም አሳስበዋል። ጄኔራል አበባው ታደሠ ከዕዙ ከፍተኛ አመራሮች ጋር በመሆን በሰሜን ምዕራብ ዕዝ ጠቅላይ መምሪያ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር አካል በሆነው የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር ላይ ተሳትፈዋል። የመከላከያ ዘመቻ ዋና መምሪያ ኃላፊ ሌተናል ጄኔራል በላይ ስዩም፣ የሰሜን ምዕራብ ዕዝ አዛዥ ሌተናል ጄኔራል ብርሃኑ በቀለ፣የምስራቅ ዕዝ ምክትል አዛዥ ሜጄር ጄኔራል ግዛው ኡማን ጨምሮ ጄኔራል መኮንኖችና የጠቅላይ መምሪያው ስታፍ አባላት በችግኝ ተከላው ላይ ተሳትፈዋል።   በዕለቱም ለምግብነት የሚውሉ የፓፓዬ፣ የአቡካዶና ሌሎች የሀገር በቀል ችግኞች በክብር እንግዶቹና በጠቅላይ መምሪያው ስታፍ አባላት መተከላቸውን የኢፌዴሪ መከላከያ ሰራዊት መረጃ ያመለክታል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም