አካባቢ ጥበቃ
በቀሪዎቹ የክረምት ወራት ከመደበኛ በላይ ዝናብ ይጠበቃል 
Aug 5, 2024 107
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 29/2016(ኢዜአ)፦ በቀሪዎቹ የክረምት ወራት የሚጠበቀው ከመደበኛ በላይ የዝናብ መጠን ለግብርናና ለሌሎች ማኅበራዊ ሥራዎች ማዋል እንደሚገባ የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት ገለጸ። የኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ፈጠነ ተሾመ የክረምት ወራት የዝናብ ሁኔታን በተመለከተ ዛሬ መግለጫ ሰጥተዋል። በመግለጫቸውም፤ በነሐሴና በመስከረም ወራት የክረምት ዝናብ ተጠናክሮ የሚቀጥል ሲሆን በአንዳንድ አካባቢዎች ላይ ቅጽበታዊ ጎርፍ ሊከሰት ይችላል ብለዋል። የክረምት ወቅት ዝናብ አወጣጥም በደቡብ ምዕራብ፣ ምዕራብ፣ ሰሜን ምዕራብና በመካከለኛ የሀገሪቱ አካባቢዎች የመዘግየት አዝማሚያ እንደሚኖርም ተናግረዋል። የክረምት ዝናብ ተጠቃሚ አካባቢዎች የትግራይ፣ አማራ፣ አፋር፣ ቤንሻንጉል ጉሙዝ፣ ጋምቤላ፣ ኦሮሚያ፣ ደቡብ ምዕራብ፣ ደቡብና ማዕከላዊ ኢትዮጵያ፣ አዲስ አበባ፣ ሀረሪ ክልልና ድሬዳዋ አስተዳደር፣ ሰሜን ሶማሌ ክልል አካባቢ ላይ ከመደበኛ በላይ ዝናብ እንደሚያገኙ ትንበያዎች ያሳያሉ ብለዋል። ይህንን ከግንዛቤ በማስገባት ከመደበኛ በላይ የሆነውን ዝናብ ለግብርናና ለሌሎች ማኅበራዊ ሥራዎች ማዋል እንደሚገባ ተናግረዋል። የሚኖረው ዝናብ ለመኽር ሰብሎች በቂ እርጥበት እንዲኖር የሚያስችል ሲሆን በእርጥበት አጠር አካባቢዎች የዝናብ ውኃን ለማሰባሰብ አመቺ ሁኔታ እንደሚፈጥር ተናግረዋል። በተጨማሪም የግድቦች የውኃ መጠንና የገጸ ምድርና ከርሰ ምድር ውኃ እንደሚጨምሩ እና ለአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር ምቹ ሁኔታን እንደሚፈጥርም ጠቁመዋል። በሌላ መልኩ የአፈር ውስጥ እርጥበት መብዛት የአፈር መሸርሸርና የመሬት መንሸራተት፣ የሰብል በሽታዎች ሊኖር ስለሚችል ጥንቃቄ ማድረግ እንደሚገባም ተናግረዋል። ጎን ለጎንም በማሳዎች ላይ የውኃ መተኛት በረባዳማ አካባቢዎች በሚዘሩ ሰብሎች ላይ ጉዳት ሊያስከትል ስለሚችል ጥንቃቄ ማድረግ እንደሚገባም አስገንዝበዋል። የጎርፍ ተጋላጭ አካባቢዎች ቅጽበታዊ ጎርፍ ሊከሰት እንደሚችልና የወንዝ ሙላት ሊከስት ስለሚችል ከፍተኛ ጥንቃቄ ሊደረግ ይገባል ሲሉም አሳስበዋል።  
ከ157 ቶን በላይ የኤሌክትሮኒክስና ኤሌክትሪክ ቆሻሻ ተወግዷል
Aug 4, 2024 164
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 28/2016(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ባለፈው በጀት ዓመት ከ157 ቶን በላይ የኤሌክትሮኒክስና ኤሌክትሪክ ቆሻሻ መወገዱን የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን አስታወቀ። የአገልግሎት ጊዜያቸው የተጠናቀቀ የኤሌክትሮኒክስና ኤሌክትሪክ ዕቃዎች በአግባቡ ካልተወገዱ ለአካባቢ ብክለትና ለጤና ጠንቅ እንደሚሆኑ ይነገራል። በዚህም መሰረት የኤሌክትሮኒክስና የኤሌክትሪክ ቆሻሻን የማስወገድ ስራ እየተከናወነ መሆኑን የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን አስታውቋል። በባለስልጣኑ የአካባቢ ህግ ተከባሪነት መሪ ሥራ አስፈጻሚ ተወካይ አዲሱ ጥበቡ፤ የአካባቢ ጥበቃ የሁሉም በመሆኑ የብክለትና የንጽህና መጓደል ምክንያት የሚሆኑ ነገሮችን በጥንቃቄ ማስወገድ እንደሚገባ ገልጸዋል። በዚህ ረገድ በተለይም የኤሌክትሮኒክስና ኤሌክትሪክ ቆሻሻ አካባቢን ከማቆሸሽ አልፎ ለጤና አደገኛ በመሆኑ የክትትልና ቁጥጥር እንዲሁም የማስወገድ ስራ እየተከናወነ መሆኑን ተናግረዋል። የኤሌክትሮኒክስና ኤሌክትሪክ ቆሻሻ ለማስወገድ የሚፈልግ ግለሰብም ሆነ ድርጅት ከአካባቢ ጥበቃ ፈቃድ መውሰድ ግዴታ መሆኑን ጠቅሰው በዚሁ መሰረት በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ157 ቶን በላይ የኤሌክትሮኒክስና ኤሌክትሪክ ቆሻሻ መወገዱን ገልጸዋል። አሁን ላይ የኤሌክትሮኒክስና ኤሌክትሪክ ቆሻሻ ክምችት እየተበራከተ መምጣቱን የጠቆሙት ተወካዩ ሁሉም የመንግሥትና የግል ተቋማት በጥንቃቄና በአግባቡ ማስወገድ እንዲችሉ አሠራር ይዘረጋልም ብለዋል። የኤሌክትሪክና ኤሌክትሮኒክስ እቃዎችን ማደስንና መልሶ ጥቅም ላይ ማዋልን መልመድ ይገባል ሲሉም መክረዋል። የኤሌክትሪክና ኤሌክትሮኒክ ቆሻሻ፣ ከጨረር አመንጪ መሳሪያዎች ውጭ ሁሉም ዓይነት የተጣለ የኤሌክትሪክና የኤሌክትሮኒክ መሳሪያ እና የመሳሪያ ክፍል የሚያጠቃልል ነው። በዚህም መሰረት ከሦስት ዓመታት በፊት በተካሄደ ጥናት በኢትዮጵያ 43 ሺህ ቶን የኤሌክትሪክና ኤሌክትሮኒክስ ቆሻሻ ክምችት መኖሩ ተመላክቷል።
የኢትዮጵያ የአረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብር በምግብ እራስን የመቻል ዓላማን የሚያሳካ ነው
Aug 3, 2024 187
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 27/2016(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ የአረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብር በምግብ እራስን የመቻል ዓላማን የሚያሳካ መሆኑን የፌደሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባኤ አገኘሁ ተሻገር ገለጹ። የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ-ጉባዔ አገኘሁ ተሻገር በማእከላዊ ኢትዮጵያ ምስራቅ ጉራጌ ዞን የክረምት የበጎ ፈቃድ ተግባራት ሥራዎችን አስጀምረዋል። አፈ-ጉባዔው ከተለያዩ የፌዴራልና የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ከፍተኛ አመራሮች ጋር በመሆን በቡታጅራ ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ የአረንጓዴ አሻራቸውን አሳርፈዋል። የፌደሬሽን ምክር ቤት አፈ-ጉባዔ አገኘሁ ተሻገር በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ በፌዴሬሽን ምክር ቤትና በተጠሪ ተቋማት የሚሰሩ የአቅመ ደካሞች ቤት ዕድሳት ስራዎች በአጭር ጊዜ እንደሚጠናቀቁ ገልጸዋል። በተጨማሪም 300 ለሚጠጉ ተማሪዎች ለ2017 ዓ.ም የሚሆኑ የትምህርት ቁሳቁሶች መበርከቱን ገልጸዋል። በቡታጅራ ከተማ የበጎ ፈቃድ ተግባራት ሥራዎችን በማከናወናቸው የተሰማቸውን ደስታ ገለጸዋል። ማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ትልቅ አቅም ያለው መሆኑን ገልጸው፤ የተጀመሩ የልማት እንዲሁም ሰላምን የማጽናት ሥራዎች ተጠናክረው መቀጠል እንዳለባቸው ተናግረዋል። የአረንጓዴ አሻራ አካባቢን ከመጠበቅ ባሻገር የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ የሚደረገው ትግል አካል መሆኑን አስረድተዋል። አገራት እራሳቸውን በምግብ እስካልቻሉ ድረስ ከጥገኝነት ሊወጡ አይችሉም ያሉት አፈ ጉባኤው ኢትዮጵያ የጀመረችው የአረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብር በምግብ እራስን የመቻል አላማን የሚያሳካ መሆኑን ተናግረዋል። የምግብ ዋስትናን የማረጋገጥ ጉዳይ የሞት ሽረት መሆኑን ገልጸው ለዚህም የአረንጓዴ አሻራ ጉልህ አስተዋጽኦ አለው ብለዋል። መንግሥት የገባውን ቃል በሙሉ ይተገብራል ያሉት አፈ-ጉባዔው፤ ለዚህም በቁርጠኝነት እየሰራ መሆኑን አመላክተዋል።   የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው በበኩላቸው፤ የፌዴሬሽን ምክር ቤት በክልሉ ለሚያከናውናቸው የተለያዩ የበጎ ፈቃድ ሥራዎችን ምስጋና አቅርበዋል። የኅብረተሰቡን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ሥራዎች በስፋት እየተከናወኑ መሆኑን አንስተዋል። በቀጣይም ምርታማነት፣ የሥራ ዕድል ፈጠራ፣ ሰላምን የማጽናት እና የኅብረተሰቡን ተጠቃሚነት ማጎልበት የትኩረት አቅጣጫዎች መሆናቸውን ጠቁመዋል። ነሐሴ 13 ቀን 2016 ክልሉ የተመሰረተበትን አንደኛ ዓመት ምክንያት በማድረግ በአንድ ጀምበር 2 ነጥብ 5 ሚልዮን ሰው የሚሳተፍበት የችግኝ ተከላ እንደሚካሄድ ጠቁመዋል። ለዚህም የመትከያ ቦታዎችን የመለየትና ጉድጓዶችን የማዘጋጀት ስራ መጠናቀቁን ገልጸዋል። አፈ-ጉባዔ አገኘው ተሻገር ከተለያዩ የፌዴራልና የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ከፍተኛ አመራሮች ጋር በመሆን የቡታጅራ ከተማ የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴ ተዘዋውረው ተመልክተዋል።  
ፖሊስ የዜጎችን ሰላምና ደህንነት ከመጠበቅ ባለፈ በበጎ ፍቃድ ተግባራት በመሰማራት ህዝባዊነቱን እያስመሰከረ ነው
Aug 3, 2024 184
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 27/2016(ኢዜአ)፦ፖሊስ የዜጎችን ሰላምና ደህንነት ከመጠበቅ ባለፈ በበጎ ፍቃድ ተግባራት በመሳተፍ ህዝባዊነቱን እያስመሰከረ መሆኑን የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ኮሚሽነር ጀነራል ደመላሽ ገብረሚካኤል ገለጹ፡፡ የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ኮሚሽነሮችና አባላት በዛሬው ዕለት በኮልፌ የፖሊስ ማሰልጠኛ ማዕከል በመገኘት አረንጓዴ አሻራቸውን አሳርፈዋል፡፡ የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ኮሚሽነር ጀነራል ደመላሽ ገብረሚካኤል በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ ሁሉም የፖሊስ ሰራዊት በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ (ዶ/ር ) አነሳሽነት የተጀመረውን የአረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብር ገቢራዊ በማድረግ ላይ ይገኛል፡፡   ፖሊስ መንግስት የጀመረውን ኢትዮጵያን አረንጓዴ የማልበስ መርሀ ግብር በመደገፍ ችግኝ ይተክላል፤ ጽድቀታቸውንም ይከታተላል ብለዋል፡፡ የአየር ንብረት ለውጥ ኢትዮጵያን ጨምሮ ዓለም ላይ ያስከተለውን ጎርፍ ድርቅና መሰል የተፈጥሮ አደጋ ለመከላከል የአረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብር ድርሻው የጎላ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ መርሀ ግብሩ ምግብ ነክ የሆኑ ችግኞችን በመትከል የምግብ ዋስትናን ማረጋገጥ የሚያስችል ፕሮጀክት በመሆኑ ፖሊስ በትኩረት የሚሰራበት ማህበራዊ ሃላፊነት መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በአረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብር የኢትዮጵያ የደን ሽፋን እየተሻሻለ መምጣቱን የገለጹት ኮሚሽነር ጀነራል ደመላሽ፤ ከልማት ተግባራት ባሻገር ፖሊስ በመደበኛ ሥራው የዜጎችን ሰላምና ደህንነት በመጠበቅ አለኝታነቱን አረጋግጧል ብለዋል፡፡ የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ሰራዊት ሰፊ ቁጥር ያለውና በሁሉም የሀገሪቱ አካባቢ የሚገኝ በመሆኑ ከመደበኛ ሥራው ባሻገር በማህበራዊ አገልግሎቱ ህዝባዊነቱን ማረጋገጥ አስችሎታል ብለዋል፡፡ በመሆኑም በመንግስት ከተሰጠው የዜጎችን ደህንነት የማስጠበቅ ተልዕኮ ባሻገር በሌሎች ሀገራዊ በጎ አድራጎት ሥራዎች የሚኖረው ተሳትፎ ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል፡፡ በኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ የአድማ ብተና ፖሊስ መምሪያ ሬጅመንት 1 ምክትል አዛዥ ዋና ኢንስፔክተር አባተ ፈለቀ ፖሊስ እንደ ዜጋ በችግኝ ተከላ አሻራውን በማሳረፍ የቀጣዩ ትውልድ አርአያ መሆኑን በተግባር ያሳያል ብለዋል፡፡ ረዳት ሳጅን አረብ ሁሴን በበኩላቸው በአረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብር ተሳትፎ ከማድረግ ባለፈ እንደ ፖሊስ ማንኛውንም መስዋዕትነት በመክፈል ለቀጣዩ ትውልድ የተሻለች አገር ለማስከበር እንሰራለን ብለዋል፡፡ አረንጓዴ አሻራ ህይወትን ማስቀጠል ነው የሚሉት የፖሊስ አባላቱ፤ የዜጎችን ደህንነተ ከመጠበቅ ባለፈ ሰው ተኮር በሆኑ ጉዳዮች ላይ በንቃት እንደሚሳተፉ አረጋግጠዋል፡፡ የፖሊስ ሰራዊቱ ችግኝ ከመትከል ባለፈ የተተከሉትን በመንከባከብ ለውጤት ማብቃት የሚያስችል መርሀ ግብር ማዘጋጀቱንም ገልጸዋል፡፡              
በድሬዳዋ አስተዳደር ምቹ የሥራና የመኖሪያ አካባቢዎች ለመፍጠር ተቋማት በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ድርሻቸውን መወጣት አለባቸው - ከንቲባ ከድር
Aug 3, 2024 171
ድሬዳዋ፤ ሐምሌ 27/2016(ኢዜአ)፦በድሬዳዋ አስተዳደር ምቹ የሥራና የመኖሪያ አካባቢዎች ለመፍጠር ተቋማት በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ድርሻቸውን መወጣት አለባቸው ሲሉ ከንቲባ ከድር ጁሃር አሳሰቡ። ከንቲባ ከድር ጁሃርን ጨምሮ ከፍተኛ የአመራር አባላት የተሳተፉበት የዘንድሮ የአረንጓዴ አሻራ ችግኝ ተከላ መርሐ ግብር ዛሬ በአስተዳደሩ ስር በሚገኙ ተቋማት ተካሄዷል። በዚህም ድሬዳዋ ዩኒቨርሲቲ ሪፈራል ሆስፒታል፣ አዲሱ ምድር ባቡርና በሌሎች ተቋማት የጥላ፣ የውበት፣ የፍራፍሬና የደን ችግኞች ተተክለዋል። ከንቲባ ከድር በዚሁ ወቅት እንደተናገሩት አረንጓዴ አሻራ ችግኝ ተከላ መርሐ ግብር ውብና ተስማሚ ከተማ እና የሥራ ተቋማት ለመፍጠር መሠረታዊ አስተዋጽኦ እያበረከተ ነው። ምቹ የስራ አካባቢን በመፍጠር ፈጣንና ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት መርሐ ግብሩ አጋዥ መሆኑንም አስረድተዋል። በመሆኑም ድሬዳዋን ምቹና ተስማሚ የመኖሪያና የኢንቨስትመንት ማዕከል ለማድረግና ተቋማት የስራ አካባቢያቸውን ምቹ ለማድረግ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ላይ መሳተፍ አለባቸው ብለዋል። በችግኝ ተከላው የተሳተፉ ተቋማት ለተከሏቸው ችግኞች እንክብካቤ እንዲያደርጉ አሳስበዋል። በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የድሬዳዋ አስተዳደር ምክር ቤት የመንግሥት ተጠሪ አቶ ኢብራሂም ዩሱፍ በበኩላቸው የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር በአስተዳደሩ የሚከሰተውን የጎርፍ አደጋ በመከላከል ረገድ ውጤት እየተገኘበት መሆኑን ገልጸዋል። የመንግሥት ተቋማትና የህክምና ማዕከላት ለተገልጋዮች ምቹ ሆነው አገልግሎት ለመስጠት እያገዙ መሆኑንም በመጠቆም መርሐ ግብሩ በልዩ ትኩረት በመተግበር ላይ እንደሆነ ተናግረዋል። በችግኝ ተከላው የተሳተፉ አካላትም በድሬዳዋ የሚታየውን አበረታች ውጤት ለማጠናከር፣ የልማትና የጋራ ትስስርን ለማፅናት በተከላው ላይ መሳተፋቸውን ገልጸዋል። ለትውልድ የተሻለ አገርና አካባቢ ለማውረስ በአረንጓዴ አሻራ ችግኝ ተከላ መርሐ ግብር መሳተፍ ይገባል ሲሉም መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል። በከተማዋ በተከናወነው የችግኝ ተከላ መርሐ ግብር ከችግኝ መትከል ባሻገር፤ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት አካል የሆኑ የደም ልገሳና ነፃ የጤና ምርመራ በተጓዳኝ ተካሄዷል።  
ኢዜአ ትክክለኛ መረጃዎችን ለህዝብ ተደራሽ ከማድረግ በተጨማሪ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የበኩሉን ድርሻ እየተወጣ ነው
Aug 3, 2024 149
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 27/2016(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ትክክለኛ መረጃዎችን ለህዝብ ተደራሽ ከማድረግ በተጨማሪ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር በመሳተፍ የበኩሉን ድርሻ እየተወጣ መሆኑ ተገለፀ። የዘንድሮ ዓመት የአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ (ዶ/ር) በአማራ ክልል ሐይቅ ከተማ ተገኝተው በይፋ ማስጀመራቸው ይታወሳል። የኢዜአ አመራሮችና ሰራተኞች ዛሬ በእንጦጦ ፓርክ አረንጓዴ አሻራቸውን አኑረዋል። የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ምክትል ስራ አስፈጻሚ አቶ ነጋሲ አምባዬ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ኢዜአ ለተከታታይ ዓመታት ችግኞችን በመትከል የራሱን አሻራ እያኖረ መጥቷል። የተተከሉት ችግኞች አገር በቀል ከመሆናቸው ባሻገር የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል፣ የአፈር ለምነትን ለመጠበቅና ለምግብነት የሚውሉ መሆናቸውን አመላክተዋል፡፡ ተቋሙ በቀጣይም የተተከሉ ችግኞችን የጽድቀት ምጣኔ ከፍ ለማድረግ ፕሮግራም አውጥቶ እንክብካቤ እንደሚያደርግ አስታውቀዋል።   በችግኝ ተከላው ከተሳተፉ የተቋሙ ሰራተኞች መካከል ዮሐንስ ወንድይራድ እና የንጉስ ውቤ ፤ ባለፉት ተከታታይ አመታት ኢዜአ ባዘጋጃቸው የችግኝ ተከላ መርሃ ግብሮች መሳተፋቸውን አመላከተዋል፡፡   ችግኞችን ከመትከል ባሻገር እንዲጸድቁ እንክብካቤ ማድረጋቸውን ጠቁመው፤ በቀጣይም ይህንኑ ተግባር አጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል፡፡ በዘንድሮው አረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር "የምትተክል ሀገር፤ የሚያፀና ትውልድ" በሚል መሪ ቃል 7 ነጥብ 5 ቢሊዮን ችግኝ ለመትከል ዕቅድ መያዙ ይታወቃል።  
የኢትዮጵያ አየር መንገድ አመራሮችና ሠራተኞች የአረንጓዴ አሻራቸውን አኖሩ
Aug 3, 2024 107
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 27/2016(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ አየር መንገድ አመራሮችና ሠራተኞች በአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብርን ችግኝ በመትከል አሻራቸውን አኑረዋል። አመራሮቹና ሰራተኞቹ ዛሬ በአዲስ አበባ ቦሌ ክፍለ ከተማ በተለምዶ አየር መንገድ ጀርባ ተብሎ በሚጠራው አካባቢ አረንጓዴ አሻራቸውን አኑረዋል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ መስፍን ጣሰው አየር መንገዱ የአካባቢ ጥበቃን እንደ አንድ ማህበራዊ ሀላፊነት ይዞ እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በዚህም ከችግኝ ተከላው በተጨማሪ ለአካባቢ ምቹ እና ተስማሚ የሆኑ የአቪዬሽን ቴክኖሎጂዎችን ጥቅም ላይ በማዋል የራሱን አስተዋፅዖ እያደረገ መሆኑን አስታውቀዋል።   አዳዲስ እና ዘመናዊ አውሮፕላኖችን የበረራ አገልግሎት ላይ በማዋል፣ በዓለም አቀፍ ደረጃ የአካባቢ ብክለትን ለመቀነስ በአየር መንገዶች በሚደረገው ርብርብ አካል በመሆን የካርበን ልቀትን በከፍተኛ ደረጃ የሚቀንሰውን ዘላቂ የአቪዬሽን ነዳጅ በመጠቀም እንዲሁም ቁሳቁሶችን መልሶ በመጠቀም ለአካባቢ ደህንነት መጠበቅ የራሱን ጉልህ ድርሻ እየተወጣ መሆኑን ጠቁመዋል። 40 ሄክታር በሚሆን ስፍራ ላይ 16 አይነት ሀገር በቀል የሆኑ 50 ሺህ ችግኞች ለመትከል ዕቅድ መያዙንና እስካሁን 27 ሺህ ያህል ችግኞች መተከላቸውን ገልጸዋል። የተቋሙ ሰራተኞች የተተከሉትን ችግኞች በመንከባከብ ኃላፊነታቸውን እንደሚወጡና በቀጣይም የአረንጓዴ አሻራ ተሳትፏቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ መናገራቸውን ከአየር መንገዱ የተገኘው መረጃ ያመላክታል።
የአረንጓዴ አሻራ አካባቢን ከመጠበቅ ባለፈ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ ከምናደርገው ትግል አንዱ ነው - አፈ-ጉባዔ አገኘሁ ተሻገር
Aug 3, 2024 104
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 27/2016(ኢዜአ)፦የአረንጓዴ አሻራ አካባቢን ከመጠበቅ ባለፈ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ ከምናደርገው ትግል አንዱ ነው ሲሉ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ-ጉባዔ አገኘሁ ተሻገር ተናገሩ። የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ-ጉባዔ አገኘሁ ተሻገር፤ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በምስራቅ ጉራጌ ዞን፣ በቡታጅራ ከተማ የፌዴሬሽን ምክር ቤትና በተጠሪ ተቋማት የሚሰሩ የአቅመ ደካሞች ቤት ዕድሳት አስጀምረዋል። በተጨማሪም 300 ለሚጠጉ ተማሪዎች ለ 2017 ዓ. ም የሚሆኑ የትምህርት ቁሳቁሶችን አበርክተዋል። አፈ-ጉባዔውና ሌሎች አመራሮች ከማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ከፍተኛ አመራሮች ጋር በመሆን በቡታጅራ ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ የአረንጓዴ አሻራቸውን አሳርፈዋል።   የፌደሬሽን ምክር ቤት አፈ-ጉባዔ አገኘሁ ተሻገር በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ የአረንጓዴ አሻራ አካባቢን ከመጠበቅ ባሻገር የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ የሚደረገው ትግል አካል መሆኑን አስረድተዋል። የተጀመሩ የአረንጓዴ አሻራን የማኖርና የመንከባከብ ሥራ ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት ጠቁመዋል። የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ትልቅ አቅም ያለው መሆኑን ገልጸው፤ የተጀመሩ የልማት እንዲሁም ሰላምን የማጽናት ሥራዎች ተጠናክረው መቀጠል እንዳለባቸው ተናግረዋል። መንግሥት የገባውን ቃል በሙሉ ይተገብራል ያሉት አፈ-ጉባዔው፤ ለዚህም በቁርጠኝነት እየሰራ መሆኑን አመላክተዋል። የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው በበኩላቸው፤ የፌዴሬሽን ምክር ቤት በክልሉ የተለያዩ የበጎ ፈቃድ ሥራዎችን ለማከናወን በመምጣቱ ምስጋና አቅርበዋል።   ክልሉ በየጊዜው የሚያጋጥሙ ችግሮችን በመፍታት በትክክለኛው አቅጣጫ ላይ እንደሚገኝም ገልፀዋል። እንዲሁም የኅብረተሰቡን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ሥራዎች በስፋት እየተከናወኑ መሆኑን አንስተዋል። በቀጣይም ምርታማነት፣ የሥራ ዕድል ፈጠራ፣ ሰላምን የማጽናት እና የኅብረተሰቡን ተጠቃሚነት ማጎልበት የትኩረት አቅጣጫዎች መሆናቸውን ጠቁመዋል። "የምትተክል ሀገር የሚያፀና ትውልድ" በሚል መሪ ሀሳብ እየተካሄደ በሚገኘው 6ኛው አገር አቀፍ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር 7 ነጥብ 5 ቢሊየን ችግኝ ለመትከል ግብ ተጥሎ እየተሰራ ነው።
በአረንጓዴ አሻራ መርሀግብር  የተተከሉ ችግኞችን ለውጤት ለማብቃት ተግተን እንሰራለን- በደቡብ ወሎ ዞን አርሶ አደሮች
Aug 3, 2024 100
ደሴ፤ ሐምሌ 27/2016(ኢዜአ)፡- በደቡብ ወሎ ዞን እየተከናወነ ባለው የአረንጓዴ አሻራ መርሀግብር የተተከሉ ችግኞችን በመንከባከብ ለውጤት ለማብቃት ተግተው እንደሚሰሩ በዞኑ አስተያየታቸውን የሰጡ አርሶ አደሮች ገለጹ፡፡ በዞኑ በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሀግብር 33 ሺህ ሄክታር መሬት የተለያዩ ችግኞችን ለመትከል ርብርብ እየተደረገ መሆኑ የግብርና መምሪያው አስታውቋል። በዞኑ ደሴ ዙሪያ ወረዳ የ037 ቀበሌ አርሶ አደር ሰይድ ይመር እንዳሉት፤ መንግስት ለአረንጓዴ አሻራ መረሃ ግብር የሰጠው ትኩረት ተጠቃሚ እንዲሆኑ አስችሏል። ይህም ባለፉት ዓመታት በተተከሉ ችግኞች የደን ልማትን ከማጠናከር ባለፈ የመሬታቸው የአፈር ለምነት ተጠብቆ የሰብል ምርታማነትን ለማሳደግ ምቹ ሁኔታ መፍጠራቸውን ተናግረዋል። እርሳቸውም ቀደም ሲል ከተከሉት ችግኞች በየሦስት ዓመቱ በመሸጥ እስከ 300 ሺህ ብር ተጨማሪ ገቢ እያገኙ መሆኑን ጠቅሰው፤ በዚህ የክረምት ወቅትም ችግኝ ተከላ እያከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የተከልኩትን ችግኝም በአግባቡ በመንከባከብ ለውጤት ለማብቃት እሰራለሁ ብለዋል።   ሌላው በዚሁ ወረዳ የ038 ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ሰይድ በሽር ፤ ቀደም ሲል ከተከሉት ችግኝ ለአጠና የደረሰውን በመሸጥ በየዓመቱ በአማካይ 25 ሺህ ብር እንደሚያገኙ አውስተዋል፡፡ ዘንድሮም ከ2 ሺህ በላይ አፕልና ሌሎችንም ችግኞችን ለመትከል ወደ ተግባር መግባታቸውን ተናግረዋል፡፡ በአረንጓዴ አሻራ ያለሙ አካባቢዎችን በበጋው ወራት በተፋሰስ በማልማት፣ በክረምት ደግሞ ችግኝ በመትከል ተጠቃሚ እየሆንን ነው ያሉት ደግሞ በአርጎባ ብሔረሰብ ልዩ ወረዳ የ01 ቀበሌ አርሶ አደር አደም መሐመድ ናቸው፡፡ ባለፉት ዓመታት የተከሉት የማንጎ፣ ብርቱካንና የፓፓያ ችግኞች እየሰጧቸው ካሉት ምርት ሽያጭ በሚያገኙት ገቢ በመበረታታት ተጨማሪ ችግኝ እንዲተክሉ ያነሳሳቸው መሆኑን ገልጸዋል። ባለፈው ዓመት ከፍራፍሬ ሽያጭ ከ20 ሺህ ብር በላይ ማግኘታቸውን አስታውሰው፤በዘንድሮው ክረምትም የፍራፍሬ ችግኝ በብዛት እየተከሉ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ የደቡብ ወሎ ዞን ግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ አህመድ ጋሎ በበኩላቸው፤ የአረንጓዴ አሻራ መረሀግብር ህብረተሰቡን ተጠቃሚ እያደረገ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ አርሶ አደሩ ጭምር በማሳውና በሌሎችም የወል መሬቶች ችግኝ በመትከልና በመንከባከብ ለውጤት እያበቃ እንደሚገኝ አስረድተዋል፡፡ በዞኑ ባለፉት ዓመታት የተተከሉ ችግኞች ምርታማነት እንዲጨምር፣ የደን ልማት እንዲጠናከርና ለእንሰሳት መኖ በቀላሉ ማገኘት እንዲቻል ምቹ ሁኔታ መፍጠራቸውን ገልጸዋል፡፡ በዘንድሮው ክረምትም 33 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ ችግኝ ለመትከል ርብርብ እየተደረገ መሆኑን አስታወቀዋል፡፡ በደቡብ ወሎ ዞን ባለፈው ዓመት ክረምት 30 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ የተለያዩ ችግኞች መተከላቸውም ከግብርና መምሪያው የተገኘው መረጃ ያመለክታል።  
ፌዴራል ፖሊስ በአረንጓዴ አሻራ መርሀ-ግብር ላይ የሚያደርገውን ተሳትፎ አጠናክሮ ይቀጥላል - ኮሚሽነር ጀነራል ደመላሽ ገብረሚካኤል
Aug 3, 2024 99
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 27/2016(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ ባለፉት ዓመታት በተሰማራባቸው የሀገራችን አካባቢዎች ሁሉ ከኅብረተሰቡ ጋር በመሆን ሲያደርገው የቆየውን የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ተሳትፎ አጠናክሮ እንደሚቀጥል የኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽነር ጀነራል ደመላሽ ገብረሚካኤል ገለጹ። የፌዴራል ፖሊስ አመራርና አባላት በሀገራችን እየተተገበረ ያለውን የአረንጓዴ ልማት ስትራቴጂን በመከተል ኮልፌ በሚገኘው የልዩ ፀረ ሽብር መምሪያ ግቢ ችግኝ በመትከል አረንጓዴ አሻራቸውን አኑረዋል።   በመርሃ-ግብሩ ላይ ኮሚሽነር ጀነራል ደመላሽ ገብረሚካኤል እንደገለጹት የኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ ባለፉት ዓመታት በተሰማራበት የሀገራችን አካባቢዎች ሁሉ ከኅብረተሰቡ ጋር በመሆን ችግኝ ተከላ ሲያካሂድ ቆይቷል። አሁን ላይም ይሄንን ተግባሩን ይበልጥ በተጠናከረ መልኩ እንደሚያስቀጥል ተናግረዋል። ፖሊስ ከህዝብ የወጣ የህዝብ ልጅ ስለሆነ በተለያዩ ጊዜያት ከህብረተሰቡ ጎን በመሆን በልማት ስራዎች ላይ በመሳተፍ እንዲሁም አቅመ-ደካሞችን በመደገፍ ማህበራዊ ኃላፊነቱን እየተወጣ እንደሚገኝ ገልፀዋል።   የዛሬው የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር ዋና ዓላማም ሀገራችን የምትከተለው የአረንጓዴ ልማት ስትራቴጂ ላይ አሻራችንን ማሳረፍ ነው ብለዋል። የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ በተሰማራበት በሀገራችን በአራቱ ማዕዘናት ሰላምና ፀጥታን በማስከበርና ሀገራዊ ተልዕኮውን በመወጣት እያስመዘገበ ካለው አመርቂ ውጤት ባሻገር ሀገራችን የምትከተለውን የአረንጓዴ ልማት ስትራቴጂ ላይም በስፋት በመሳተፍ የድርሻውን እያበረከተ እንደሚገኝ ገልፀዋል። ችግኞችን መትከል ብቻ ሳይሆን ተንከባክቦ በማሳደግ ለፍሬ እንዲበቁ ማድረግ ይጠበቅብናል ሲሉ መግለጻቸውን ከፌዴራል ፖሊስ የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ፅዳት ኤጀንሲ አና በስሩ ያሉ ተቋማት ሰራተኞችና አመራሮች አረንጓዴ አሻራቸውን አኖሩ
Aug 3, 2024 110
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 27/2016(ኢዜአ)፦የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ፅዳት ኤጀንሲ አና በስሩ ያሉ ተቋማት ሰራተኞችና አመራሮች አረንጓዴ አሻራቸውን አኖሩ። "የምትተክል ሀገር፤ የሚያፀና ትውልድ" በሚል መሪ ሃሳብ እየተካሔደ ባለው ስድስተኛው ዙር የአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር የተለያዩ ተቋማት አሻራቸውን እያሳረፉ ነው። በዛሬው ዕለት የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ፅዳት ኤጀንሲ እና በስሩ ያሉ ተቋማት አመራርና ሰራተኞች በረጲ ደረቅ ቆሻሻ ማስወገጃ ስፍራ አረንጓዴ አሻራቸውን አኑረዋል። በችግኝ ተከላው ላይ በቢሮ ኃላፊ ማዕረግ የአዲስ አበባ ከተማ ምክትል ዋና ስራ አስኪያጅ ወይዘሮ ቆንጅት ደበላ ፣ የአዲስ አበባ ከተማ የፅዳት አስተዳደር ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር እሸቱ ለማ (ዶ/ር) እና ሌሎችም አመራሮች ተገኝተዋል። በዚሁ ወቅት ምክትል ስራ አስኪያጇ ወይዘሮ ቆንጂት ደበላ የአረንጓዴ አሻራ መዲናዋን ውበት በማላበስ የላቀ አስተዋጽኦ እያበረከተ ነው ብለዋል። ከተማ አስተዳደሩ መዲናዋን ውብና ፅዱ ለማድረግ በርካታ ተግባራትን እያከናወነ እንደሚገኝም ተናግረዋል ። በመዲናዋ በአረንጓዴ አሻራና በኮሪደር ልማት የሚሰሩ ፕሮጀክቶችን ለመንከባከብ እና ለመጠበቅ የሚያስችል የህግ ማእቀፍ ተግባራዊ መደረጉን በማንሳት ይህም አጥፊዎችን ተጠያቂ ለማድረግ እንደሚረዳ ጠቁመዋል፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ፅዳት ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር እሸቱ ለማ (ዶ/ር) በበኩላቸው የአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር ችግኞችን በመትከል ለቀጣዩ ትውልድ ምቹ ከባቢን ለመፍጠር የሚያስችል ነው ብለዋል ። የሚተከሉት ችግኞች ከውበት ባሻገር ለምግብነትም የሚውሉ በመሆናቸው ዘርፈ ብዙ ጥቅም እንዳላቸውም ነው የገለጹት።   በመርኃ ግብሩ ላይ የተገኙት የልደታ ክፍለ ከተማ ፅዳት አስተዳደር ኃላፊ አቶ በፍቃዱ ኃይሌ የመዲናዋ ነዋሪ በአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር በመሳተፍ እያበረከተ ያለው አስተዋጽኦ ከፍተኛ ነው ብለዋል። ችግኝ መትከል ምቹና ጽዱ መኖሪያ አካባቢ ለመፍጠር ከፍተኛ አበርክቶ እንዳለው የአራዳ ክፍለ ከተማ ወረዳ ሁለት መንገድ ፅዳት ባለሙያ ወይዘሮ እልፍነሽ ታደሰ ተናግረዋል ። የተከሉትን ችግኞች ለመንከባከብም ዝግጁ መሆናቸውን ተሳታፊዎቹ አብራርተዋል ። በዘንድሮ ክረምት እንደ ሀገር 7 ነጥብ 5 ቢሊየን ችግኝ ለመትከል ግብ ተጥሎ እየተሰራ መሆኑ ይታወቃል ።  
የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ አመራርና ሠራተኞች የአረንጓዴ አሻራቸውን አኖሩ
Aug 3, 2024 93
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 27/2016 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ አመራርና ሠራተኞች ቦሌ ለሚ ኢንዱስትሪ ፓርክ የአረንጓዴ አሻራቸውን አኑረዋል። የዘንድሮው ሀገር አቀፍ የአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር "የምትተክል ሀገር፤ የሚያፀና ትውልድ" በሚል መሪ ሃሳብ በመካሄድ ላይ ነው። በዚሁ መርኃ ግብር የተለያዩ ተቋማት አሻራቸውን እያኖሩ ሲሆን፤ በዛሬው ዕለትም የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ አመራርና ሠራተኞች ችግኝ በመትከል አሻራቸውን አኑረዋል። አመራርና ሠራተኞቹ የአረንጓዴ አሻራቸውን ያኖሩት ቦሌ ለሚ ኢንዱስትሪ ፓርክ ውስጥ ነው።   ባንኩ በዘንድሮው መርኃ ግብር በአዲስ አበባ ማዕከል ብቻ ከ50 ሺህ በላይ ለምግብነት የሚውሉ ፣ ሀገር በቀልና ዘርፈ-ብዙ ጠቀሜታ ያላቸውን ዛፎችና ችግኞች ለመትከል አቅዶ እየሰራ መሆኑ ተገልጿል። ከአዲስ አበባ ማዕከል በተጨማሪ በሌሎች የሀገሪቱ አካባቢዎች በሚገኙ 23 ዲስትሪክቶች የችግኝ ተከላው እንደሚካሄድ ነው የተገለፀው። የ2016 ዓ.ም ሀገር አቀፍ የአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር 7 ነጥብ 5 ቢሊየን ችግኝ ለመትከል ዕቅድ ተይዞ እየተሰራ ነው።  
ኢዜአ ትክክለኛ መረጃዎችን ለህዝብ ተደራሽ ከማድረግ በተጨማሪ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የበኩሉን ድርሻ እየተወጣ ነው
Aug 3, 2024 115
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 27/2016(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት /ኢዜአ/ ትክክለኛ መረጃዎችን ለህዝብ ተደራሽ ከማድረግ በተጨማሪ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር የበኩሉን ድርሻ እየተወጣ መሆኑን የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ምክትል ስራ አስፈጻሚ አቶ ነጋሲ አምባዬ ገለጹ። የዘንድሮ የአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በሀይቅ ከተማ ተገኝተው በይፋ ማስጀመራቸው ይታወሳል። የኢዜአ አመራሮችና ባለሙያዎችም በእንጦጦ ፓርክ ችግኝ በመትከል አረንጓዴ አሻራቸውን አስቀምጠዋል። የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ምክትል ስራ አስፈጻሚ አቶ ነጋሲ አምባዬ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ ተቋሙ ለተከታታይ አመታት ችግኞችን በመትከል የራሱን አሻራ እያኖረ መጥቷል። በተቋሙ የሚተከሉ ችግኞች ሙሉ በሙሉ የአፈር ለምነትን በአጭር ጊዜ የሚመልሱ እና አገር በቀል እንደሆኑም ገልጸዋል። ችግኞችን ከመትከል ባሻገር በተገቢው መንገድ እንዲጸድቁ ለመንከባከብ እንደሚሰራም ተናግረዋል። በቀጣይም ተቋሙ የችግኞችን የጽድቀት ምጣኔ ከፍ ለማድረግ ፕሮግራም አውጥቶ እንክብካቤ እንደሚያደርግ አስታውቀዋል። በችግኝ ተከላው የተሳተፉ አመራሮችና ባለሙያዎች በበኩላቸው ፤ የተተከሉ ችግኞች እንዲጸድቁ እንክብካቤ ለማድረግ ዝግጁ መሆናቸውን ተናግረዋል። በዘንድሮው አረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር "የምትተክል ሀገር፤ የሚያፀና ትውልድ" በሚል መሪ ሀሳብ 7 ነጥብ 5 ቢሊዮን ችግኝ ለመትከል ዕቅድ ተይዞ ተግባራዊ እንቅስቃሴ መጀመሩ ይታወቃል።
በምዕራብ ወለጋ ዞን በተያዘው ክረምት በአጭር ጊዜ ምርት የሚሰጡ የቡና ችግኞች ተተክለዋል
Aug 3, 2024 109
ጊምቢ፤ ሀምሌ 27/2016 (ኢዜአ)፦በምዕራብ ወለጋ ዞን በተያዘው ክረምት በአጭር ጊዜ ውስጥ ምርት የሚሰጡና በሽታን የሚቋቋሙ የቡና ችግኞች በስፋት መተከላቸውን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት አስታወቀ። በጽፈት ቤቱ የቡናና ሻይ ልማት ቡድን መሪ አቶ ኤፍሬም መስፍን፣ የተተከሉ የቡና ችግኞች ከጅማ ግብርና ምርምር ማዕከል የተገኙና በአጠረ ጊዜ ምርት የሚሰጡ ናቸው ብለዋል። በዞኑ የቡና ችግኝ የሚተከለው ከግንቦት አጋማሽ እስከ ሀምሌ መጨረሻ መሆኑን ጠቅሰው በተያዘው ክረምትም የዞኑን ህዝብ በስፋት በማሳተፍ በርካታ የቡና ችግኞች መተከላቸውን ተናግረዋል። በአጠቃላይ የቡና ችግኞቹ በ65 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ የተተከሉ ሲሆን በቡና ችግኝ ተከላው ላይ ከ200 ሺህ በላይ አርሶ አደሮች መሳታፋቸውን ገልጸዋል። የቡና ችግኞቹም በ3 ሺህ 426 የግልና መንግስት ችግኝ ማፊያ ጣቢያዎች መዘጋጀታቸውን አስታውሰዋል።   ዘንድሮ የተተከሉ የቡና ችግኞች የዞኑን የቡና ተክል ሽፋን ወደ 620 ሺህ ሄክታር መሬት ከፍ የሚያደርገው መሆኑንም ጠቅሰዋል። የላሎ አሳቢ ወረዳ አርሶ አደር ሀብቴ ጋሩማ፣ ዘንድሮ ከ2 ሺህ በላይ የተሻሻለ ዝርያ ያላቸው የቡና ችግኞች መትከላቸውን ተናግረዋል። የቡና ችግኞቹ በምርምር የተረጋገጡና በአጭር ጊዜ ውስጥ ምርት የሚሰጡ እንዲሁም በሽታን የሚቋቋሙ መሆኑን ከግብርና ባለሙያ ግንዛቤ ማግኘታቸውንም ገልጸዋል። የጊምቢ ወረዳ አርሶ አደር ታከለ ፍቅሩ በበኩላቸው ባላቸው ሩብ ሔክታር መሬት ላይ በባለሙያ ምክር በመታገዝ የቡና ችግኝ መትከላቸውን ተናግረዋል። አርሶ አደሩ በየዓመቱ አዳዲስ የቡና ችግኞችን የመትከል ልምድ እንዳላቸውም ነው የተናገሩት።    
አቶ አገኘሁ ተሻገር የክረምት የበጎ ፈቃድ ተግባራት ሥራዎችን ለማስጀመር ቡታጅራ ገብተዋል
Aug 3, 2024 111
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 27/2016 (ኢዜአ)፦ የኢፌዲሪ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ-ጉባዔ አቶ አገኘሁ ተሻገር የክረምት የበጎ ፈቃድ ተግባራት ሥራዎችን ለማስጀመር ቡታጅራ ከተማ ገብተዋል። አፈ-ጉባኤው በፌዴሬሽን ምክር ቤትና በተጠሪ ተቋማት የሚሰሩ የአቅመ ደካሞችን ቤት ዕድሳትና ለተማሪዎች የትምህርት ቁሳቁስ ድጋፍ ለማድረግ እንዲሁም የችግኝ ተከላ መርሐ-ግብር ያስጀምራሉ። አፈ-ጉባኤው ቡታጅራ ከተማ ሲደርሱ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ-መስተዳድር አቶ እንዳሻው ጣሰውን ጨምሮ የክልሉ ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች አቀባበል አድርገውላቸዋል። በመርሃ ግብሩ ላይ ለመሳተፍ አፈ-ጉባኤውን ጨምሮ የፌዴሬሽን ምክር ቤትና የተጠሪ ተቋማት ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል።   መርሐ-ግብሩን የምክር ቤቱና የክልሉ ከፍተኛ አመራሮች፣ የምክር ቤቱ ተጠሪ ተቋማት ኃላፊዎችና ሠራተኞች እንዲሁም የክብር እንግዶች በተገኙበት በይፋ እንደሚያስጀምሩም ተመላክቷል። የምስራቅ ጉራጌ ዞን በክረምቱ ለመትከል የያዘው 24 ሚልዮን የችግኝ ተከላ እቅድ አካል የሆነው የችግኝ ተከላ መርሐ ግብርም ይካሔዳል። ምክር ቤቱ የክረምት ወራት የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር፣ የአቅመ ደካማ ወገኖችን ቤቶች አድሶ የማስረከብ እና ሌሎች ሀገራዊ የበጎ አድራጎት መርሃ-ግብሮችን ላለፉት ዓመታት በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች ማከናወኑን ከፌዴሬሽን ምክር ቤት የተገኘው መረጃ ያመለክታል። የዘንድሮውን የአረንጓዴ አሻራ መርሐ-ግብር ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) "የምትተክል ሀገር የሚያፀና ትውልድ" በሚል መሪ ሀሳብ ሰኔ 22 ቀን 2016 ዓ.ም በደቡብ ወሎ ዞን ሐይቅ ከተማ በይፋ ማስጀመራቸው ይታወሳል፡፡
በምስራቅ ጎጃም ዞን አንድ ነጥብ አንድ ሚሊየን የቡና ችግኞች ይተከላሉ
Aug 2, 2024 113
ደብረ ማርቆስ ፤ሐምሌ 26/2016 (ኢዜአ)፡- በምስራቅ ጎጃም ዞን በተያዘው የክረምት ወቅት አንድ ነጥብ አንድ ሚሊየን የቡና ችግኞች ለመትከል ተ እየተሰራ መሆኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። የመምሪያው የአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ባለሙያ አቶ ተሾመ በላይ ለኢዜአ እንደተናገሩት በዞኑ የቡና ልማትን ለማስፋፋት ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ ነው ። ለዘንድሮ ክረምት አንድ ነጥብ አንድ ሚሊዮን የቡና ችግኞች ተዘጋጅተው እስካሁን 472 ሺህ መተከላቸውን ተናግረዋል ። ዘንድሮ አጠቃላይ በሚተከሉት ችግኞች ከ400 ሄክታር በላይ ተጨማሪ መሬት እንደሚለማ ጠቁመው ተከላው እስከ ሐምሌ 30 ቀን 2016 ዓ.ም እንደሚጠናቀቅ አመላክተዋል ። አርሶ አደሩ ከሰብል ልማት ጎን ለጎን በቡና ልማት በመሳተፍ ተጨማሪ ገቢ በማግኘት የኢኮኖሚ አቅሙን እያሳደገ መሆኑን ተናግረዋል። እንደ ባለሙያው ገለጻ በዞኑ እስካሁን 43 ሺህ ሄክታር መሬት በቡና ተክል ተሸፍኗል። በዞኑ የጎዛምን ወረዳ የጥጃን ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር አንተናኔ አበበ እንዳሉት "በዚህ ክረምት በሩብ ሄክታር መሬት ላይ የቡና ችግኝ ተከላ ማከናወናቸውን ገልጸዋል። ልማቱን በማስፋፋት ተጠቃሚ ለመሆን እንደሚተጉ አመላክተዋል። "ከሰብል ልማት ስራቸው ጎን ለጎን በቡና ልማት በመሳተፍ ተጠቃሚ መሆናቸውን የገለጹት ደግሞ በወረዳው የገራሞ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ቢሻው ጌታቸው ናቸው። ከዚህ በፊት በተከሉት ቡና በሚያገኙት ምርት ከቤት ውስጥ ፍጆታ አልፎ ለገበያ ማቅረብ መጀመራቸውን ጠቅሰው በዚህ የክረምት ወቅትም ተከላ ለማከናወን የጉድጓድ ቁፋሮ ዝግጅት ማድረጋቸውን ገልፀዋል።        
የፌዴራል ቤቶች ኮርፖሬሽን አመራሮችና ሠራተኞች የአረንጓዴ አሻራቸውን አኖሩ
Aug 2, 2024 140
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 26/2016(ኢዜአ)፦ፌዴራል ቤቶች ኮርፖሬሽን አመራሮችና ሠራተኞች በጉለሌ ዕጽዋት ማዕከል አረንጓዴ አሻራቸውን አኑረዋል። "የምትተክል ሀገር የሚያፀና ትውልድ" በሚል መሪ ሀሳብ እየተካሄደ የሚገኘው 6ተኛው ዙር የአረንጓዴ አሻራ መርሐግብር የተለያዩ ተቋማት የበኩላቸውን አሻራ እያሳረፉ ይገኛሉ። ዛሬም የኮርፖሬሽኑ አመራሮችና ሠራተኞች በተከታታይ አምስት ዓመታት አገር በቀል ችግኞችን ሲተክሉበት በነበረው በጉለሌ ዕጽዋት ማዕከል አረንጓዴ አሻራቸውን አሳርፈዋል። የፌዴራል ቤቶች ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈፃሚ ረሻድ ከማል በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ ኮርፖሬሽኑ ከቤት ልማት በተጨማሪ በአረንጓዴ አሻራ መርሀግብር የበኩሉን እያበረከተ ይገኛል። ተቋሙ የቤት ልማት ሥራን ከአረንጓዴ ልማት ጋር አስተሳስሮ እየሰራ መሆኑን ገልጸው፤ በቀጣይ በሌሎች ዓለማት በህንጻ ላይ ችግኝ የመትከል ተሞክሮን በኮርፖሬሽኑ እንደሚተገበር ጠቁመዋል። በኮርፖሬሽኑ ባለው ይዞታዎች የችግኝ ተከላ እያካሄደ መሆኑን ገልጸው፤ የቤት ልማቱን ከአረንጓዴ አሻራ ጋር አስተሳስሮ እየሰራ ይገኛል ብለዋል። በአረንጓዴ ልማት ሥራው የአካባቢ ሚዛንን ከመጠበቅ ባለፈ ለመጪው ትውልድ የተሻለ አገር ለማስረከብ እንደሚያስችል ተናግረዋል። የኮርፖሬሽኑ ሠራተኞች የሆኑት ወይዘሮ አጸዱ ረጋሳ እና አቶ አማኑኤል አያሌው እንዳሉት ችግኝ በመትከል ለመጪው ትውልድ እንዲተላለፍ የበኩላችን እየተወጣን ነው ብለዋል። ችግኝ መትከል ብቻ ሳይሆን እንዲጸድቅ ስንከባከብ ቆይተናል ይህንን ስራ አጠናክረን እንቀጥላለን ብለዋል።    
የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቋቋም በሚደረገው ጥረት የሚጠበቅብንን ድርሻ እየተወጣን ነው
Aug 2, 2024 136
አዳማ፤ ሐምሌ 26/2016(ኢዜአ)፡- የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቋቋም በሚደረገው ጥረት የሚጠበቅብንን ድርሻ እየተወጣን ነው ሲሉ የኢትዮጵያ የንግድ ስራዎች ኮርፖሬሽን አመራር አባላትና ሰራተኞች ገለጹ። በኮርፖሬሽኑ ዋና መስሪያ ቤትና በ28 የግብይት ማዕከላት የሚገኙ ከ2 ሺህ በላይ የሚሆኑ የኮርፖሬሽኑ ሰራተኞች ዛሬ የአረንጓዴ አሻራቸውን አኑረዋል። የኮርፖሬሽኑ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ አቻ ደምሴ በተለይ ለኢዜአ እንደገለፁት፤ የተሻለች ሀገር ለቀጣይ ትውልድ ለማስረከብና የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር እንዲሳካ ኮርፖሬሽኑ የሚጠበቅበትን ድርሻ እየተወጣ ነው። በተለይ የአፈር ለምነትን ለመጠበቅ፣ የአፈር መከላትንና የአየር ብክለትን ለመከላከል፣ የአካባቢውን ስነ-ምህዳር ለመጠበቅ የሚቻለው በአረንጓዴ አሻራ ንቁ ተሳታፊ መሆን ሲቻል ነው ብለዋል። ኮርፖሬሽኑ የዘንድሮውን የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ለማሳካት 1 ነጥብ 2 ሚሊዮን ብር ወጪ በማድረግ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸውን ችግኞች ገዝቶ ወደ ተከላ መግባቱን ገልጸዋል። በዚህም በዛሬው ዕለት በሁሉም የኮርፖሬሽኑ ማዕከላት ተከላ እየተከናወነ መሆኑን ገልጸዋል።   የኮርፖሬሽኑ ምክትል ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ ገመቺስ መላኩ በበኩላቸው ኮርፖሬሽኑ ባለፉት ዓመታት ከ49 ሺህ በላይ ችግኞችን መትከሉን ጠቅሰው ከተተከሉት ችግኞች ውስጥ ከ31 ሺህ በላይ የሚሆኑት መፅደቃቸው ተረጋግጧል ብለዋል። ከፀደቁት ችግኞች መካከልም ቡና፣ ፓፓያ፣ ማንጎ፣ አቮካዶና ዘይቱንን ጨምሮ ለምግብነት የሚውሉ ችግኞች እንደሚገኙበትም ገልፀዋል። በዛሬው ዕለት በ28ቱ የኮርፖሬሽኑ ማዕከላት ከ11 ሺህ 500 በላይ የተለያየ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች ተከላ እየተከናወነ መሆኑን ጠቅሰው በአዳማ ማዕከል ብቻ 5ሺህ ችግኞች ተተክለዋል ብለዋል። በችግኝ ተከላው ላይ የተሳተፉ የኮርፖሬሽኑ ሰራተኞች የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር እንዲሳካ ባለፉት ተከታታይ ዓመታት ችግኝ እየተከሉ መሆኑን ጠቅሰው በቀጣይም በተከላው ረገድ የሚያደርጉትን ተሳትፎ እንደሚያጠናክሩም ገልጸዋል።  
 የመዲናዋን ፅዳት ደረጃውን በጠበቀ መልኩ ለማከናወን በተሰራው ስራ ህብረተሰቡን የፅዳቱ ባለቤት ማድረግ መቻሉ ተገለጸ
Aug 1, 2024 170
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 25/2016(ኢዜአ)፦ የመዲናዋን ፅዳት ደረጃውን በጠበቀ መልኩ ለማከናወን በተሰራው ግንዛቤ የማሳደግ ተግባር ህብረተሰቡን የፅዳቱ ባለቤት ማድረግ መቻሉን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ፅዳት ኤጀንሲ አስታወቀ፡፡ ኤጀንሲው በ2016 ዓ.ም ዕቅድ አፈጻጸምና በ 2017 ዓ.ም ዕቅድ ዙሪያ ከባለድርሻ አካላት ጋር ውይይት አድርጓል። በዚሁ ወቅት የኤጀንሲው ዋና ዳይሬክተር እሸቱ ለማ (ዶ/ር) በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ኤጀንሲው የከተማዋን ደረጃ የሚመጥን የፅዳት አጠባበቅ ተግባራት ማከናወኑን ተናግረዋል፡፡ በዚህም ከተማዋን ስማርት ሲቲ ለማድረግ የተጀመረውን ተግባር የሚያሳልጡ የፅዳት ንቅናቄዎችን በማከናወን ውጤታማ ለውጥ ማስመዝገብ ተችሏል ብለዋል፡፡ ኤጀንሲው የመዲናዋን የፅዳት አጠባበቅ ደረጃውን በጠበቀ መልኩ ዘመናዊ ለማድረግ እየሰራ መሆኑን አብራርተዋል ፡፡ የኤጀንሲው ምክትል ዳይሬክተር አቶ ሳዲቅ ሽኩር በ2016 በጀት ዓመት ኤጂንሲው ያከናወናቸውን ዝርዝር ተግባራት የተመለከተ ሪፖርት አቅርበዋል፡፡   በዋናነት የመዲናዋን ፅዳት ደረጃውን በጠበቀ መልኩ ለማከናወን በተሰራው ግንዛቤ የማሳደግ ተግባር ህብረተሰቡን የፅዳቱ ባለቤት ማድረግ መቻሉን በሪፖርታቸው ገልጸዋል ፡፡ ህብረተሰቡ የደረቅ ቆሻሻ አያያዝና አወጋገድ ግንዛቤ እንዲኖረው 2 ሺህ ባለሙያዎች ተመድበው ብሎክን ማዕከል በማድረግ ቤት ለቤት የግንዛቤ ማስጨበጫ ስራ መስራታቸውን ገልጸዋል፡፡ በኮሪደር ልማት የተገነቡ መንገዶችና ሌሎችም ዋና ዋና መንገዶች ፅዳት ለማስጠበቅ በየመንገዶቹ ዳር 988 ቆሻሻ መጣያዎች መገንባታቸውንም ገልጸዋል ፡፡ ደረቅ ቆሻሻ መሰብሰብና ጥቅም ላይ ማዋል አንዱ ስራ ዘርፍ ሲሆን ባለፈው በጀት ዓመት ለ3 ሺህ ዜጎች የሥራ ዕድል መፈጠሩን አስታውቀዋል፡፡   የአቃቂ ቃሊቲ ወረዳ ስድስት ጽዳት ኃላፊ ወይዘሮ ምስጋና በለጠ አዲስ አበባን ውብና ጽዱ ለማድረግ ኤጀንሲው የያዘውን ግብ ለማሳካት አበክረው እየሰሩ እንደሚገኙ ተናግረዋል ፡፡ የህብረተሰቡ ቆሻሻ አያያዝና አወጋገድ ሥርዓት እየተቀየረ መምጣቱን ተከትሎ መዲናዋን ጽዱ የማድረግ ስራው ውጤት ማምጣቱን የገለጹት ደግሞ ከለሚ ኩራ ወረዳ የመጡት አቶ መገርሳ ጆቴ ናቸው ፡፡ በበጀት ዓመቱ 950 ሺህ 166 ቶን ደረቅ ቆሻሻ መሰብሰብ መቻሉና ከዚህም ውስጥ 90 ሺህ ቶን ቆሻሻ መልሶ ጥቅም ላይ መዋሉ በሪፖርቱ ተመላክቷል ፡፡ ቆሻሻን መልሶ ጥቅም ላይ በማዋል ስራ ላይ የተሰማሩ ማህበራት በበጀት ዓመቱ 1 ነጥብ 4 ቢሊዮን ገቢ ማግኘታቸውም ተገልጿል ፡፡  
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም