ስፖርት
ተጠባቂው የ5 ሺህ ሜትር ሴቶች ፍጻሜ ዛሬ ማምሻውን ይካሄዳል 
Aug 5, 2024 179
አዲስ አበባ፤ሐምሌ 29/2016(ኢዜአ)፦በፈረንሳይ ፓሪስ እየተካሄደ በሚገኘው 33ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች በ5 ሺህ ሜትር ሴቶች የሚደረገውን የፍጻሜ ውድድር ኢትዮጵያውያን በጉጉት ይጠብቁታል። ውድድሩ ከምሽቱ 4 ሰዓት ከ15 ደቂቃ 80 ሺህ ተመልካች በሚያስተናግደው ስታድ ደ ፍራንስ ብሔራዊ ስታዲየም ይከናወናል። በፍጻሜው አትሌት ጉዳፍ ፀጋይ፣ አትሌት እጅጋየሁ ታዬና አትሌት መዲና ኢሳ ኢትዮጵያን ወክለው ይወዳደራሉ። አትሌቶቹ ሐምሌ 26 ቀን 2016 ዓ.ም የተደረገውን ማጣሪያ አልፈው ለፍጻሜው ደርሰዋል። ውድድሩን ያሸንፋሉ ተብሎ የቅድሚያ ግምት ከተሰጣቸው አትሌቶች መካከል አንዷ የርቀቱ የዓለም ክብረ ወሰን ባለቤት የሆነችው ጉዳፍ ፀጋይ ናት። ጉዳፍ እ.አ.አ በ2023 በአሜሪካ ኢውጅን በተካሄደ ውድድር 14 ደቂቃ ከ00 ሴኮንድ ከ21 ማይክሮ ሴኮንድ ክብረ ወሰኑን የጨበጠችበት ሰዓት ነው። አትሌቷ በቶኪዮ በተካሄደው 32ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች በ5 ሺህ ሜትር የነሐስ ሜዳሊያ አግኝታ ነበር፤ በሁለተኛ የኦሊምፒክ ተሳትፎዋ ወርቅ ለማምጣት ትሮጣለች። ሌላኛዋ ተወዳዳሪ አትሌት እጅጋየሁ ታዬ በኦሊምፒክ ጨዋታዎች ይሄ ሁለተኛ ተሳትፎዋ ነው። እጅጋየሁ በ32ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች በ5 ሺህ ሜትር ፍጻሜ 5ኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃ ነበር። አትሌቷ እ.አ.አ በ2022 በአሜሪካ ኢውጅን በተደረገ ውድድር 14 ደቂቃ ከ12 ሴኮንድ ከ98 ማይክሮ ሴኮንድ የርቀቱን የግል ምርጥ ሰዓቷን አስመዝግባለች። በፍጻሜው ኢትዮጵያን የምትወክለው ሶስተኛ አትሌት ታዳጊዋ መዲና ኢሳ ናት፤ መዲና በኦሊምፒክ ስትሳተፍ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው። አትሌት መዲና ከሁለት ዓመት በፊት በለንደን በተካሄደ የዳይመንድ ሊግ ውድድር 14 ደቂቃ ከ16 ሴኮንድ ከ54 ማይክሮ ሴኮንድ በርቀቱ የግል ምርጥ ሰዓቷን አስመዝግባለች። በጋና አክራ በመጋቢት ወር 2016 ዓ.ም በተከናወነው 13ኛው የአፍሪካ ጨዋታዎች እና ከሁለት ዓመት በፊት በኮሎምቢያ በተካሄደው 19ኛው የዓለም አትሌቲክስ ከ20 ዓመት በታች ሻምፒዮና በ5 ሺህ ሜትር የወርቅ ሜዳሊያዎችን አግኝታለች። በፍጻሜው የኢትዮጵያ አትሌቶች ከኬንያውያኑ ፌዝ ኪፕዬጎንና ቢትሪስ ቺቤት እንዲሁም በትውልድ ኢትዮጵያዊ በዜግነት ኔዘርላንዳዊ ከሆነችው ሲፋን ሀሰን ጋር የሚያደርጉት ፍልሚያ በስፖርት ቤተሰቡ በጉጉት ይጠበቃል። በተያያዘም ከምሽቱ 4 ሰዓት ከ47 ደቂቃ ላይ የ8 መቶ ሜትር ሴቶች ፍጻሜ ይደረጋል፤ በውድድሩ ላይ አትሌት ፅጌ ዱጉማና አትሌት ወርቅነሽ መለሰ ይሳተፋሉ። ትናንት በተደረገው የርቀቱ የግማሽ ፍጻሜ ውድድር አትሌት ፅጌ ከምድብ 2 1ኛ እንዲሁም ወርቅነሽ መለሰ በምድብ 1 2ኛ በመውጣት ለፍጻሜ አልፈዋል። አትሌት ፅጌ 1 ደቂቃ ከ57 ሴኮንድ ከ47 ማይክሮ ሴኮንድ፣ አትሌት ወርቅነሽ 1 ደቂቃ ከ58 ሴኮንድ ከ6 ማይክሮ ሴኮንድ የርቀቱ የግል ምርጥ ሰዓታቸው ነው። አትሌቶቹ ትናንት በተደረገው ማጣሪያ በርቀቱ ያላቸውን የግል ምርጥ ሰዓታቸውን አሻሽለዋል፤ ወርቅነሽ በ33ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች የግል ምርጥ ሰዓቷን ስታሻሽል ለሁለተኛ ጊዜ ነው። በተጨማሪም ከምሽቱ 2 ሰዓት ከ4 ደቂቃ ላይ የ3 ሺህ ሜትር ወንዶች መሰናክል ማጣሪያ ውድድር ይካሄዳል፤ ለሜቻ ግርማ፣ ጌትነት ዋለና ሳሙኤል ፍሬው ይሳተፋሉ። በ7 ደቂቃ ከ52 ሴኮንድ ከ11 ማይክሮ ሴኮንድ የርቀቱ የዓለም ክብረ ወሰን ባለቤት የሆነው ለሜቻ ግርማ በማጣሪያው በምድብ 3 ይወዳደራል፤ በቶኪዮ በተካሄደው 32ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች በርቀቱ የብር ሜዳሊያ ማግኘቱ የሚታወስ ነው። በምድብ 1 የሚገኘው አትሌት ጌትነት ዋለ 8 ደቂቃ ከ5 ሴኮንድ ከ15 ማይክሮ ሴኮንድ እንዲሁም በምድብ 2 የሚወዳደረው አትሌት ሳሙኤል ፍሬው 8 ደቂቃ ከ5 ሴኮንድ ከ78 ማይክሮ ሴኮንድ የርቀቱ የግል ምርጥ ሰዓታቸው ነው። በሶስት ምድብ በሚደረገው ማጣሪያ ከየምድቡ ከአንድ እስከ አምስት የሚወጡ አትሌቶች ለፍጻሜው ያልፋሉ። የፍጻሜው ውድድር ረቡዕ ነሐሴ 1 ቀን 2016 ዓ.ም ከምሽቱ 4 ሰዓት ከ43 ደቂቃ ላይ ይካሄዳል። ኢትዮጵያ በ33ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች እስካሁን ያገኘችው 1 የብር ሜዳሊያ ብቻ ነው፤ ሜዳሊያውን ያስገኘው አትሌት በሪሁ አረጋዊ በ10 ሺህ ሜትር ወንዶች የፍጻሜ ውድድር ነው።    
ኢትዮጵያውያን አትሌቶች በመካከለኛ ርቀት ለፍጻሜ ለማለፍ የሚያደርጓቸው የማጣሪያ ውድድሮች ይጠበቃሉ
Aug 4, 2024 182
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 28/2016(ኢዜአ)፦ በ33ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች የኢትዮጵያ አትሌቶች በመካከለኛ ርቀት ለፍጻሜ ለማለፍ የማጣሪያ ውድድራቸውን ዛሬ ያደርጋሉ። ከረፋዱ 5 ሰዓት ከ5 ደቂቃ ላይ በሚካሄደው የ3000 ሜትር መሰናክል ሴቶች የማጣሪያ ውድድር ሎሚ ሙለታና ሲምቦ አለማየሁ ኢትዮጵያን ወክለው ይሳተፋሉ። በኦሊምፒክ ጨዋታዎች ሁለተኛ ተሳትፎዋን የምታደርገው አትሌት ሎሚ በማጣሪያው በምድብ 1 ትወዳደራለች። በቶኪዮ በተካሄደው 32ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች በተመሳሳይ ርቀት ባደረገችው ማጣሪያ 10ኛ ወጥታ ለፍጻሜ አላለፈችም። ሎሚ እ.አ.አ በ2021 በኔዘርላንድ ሄንግሎ በተካሄደ ውድድር 9 ደቂቃ ከ14 ሴኮንድ ከ04 ማይክሮ ሴኮንድ በመግባት የርቀቱን የግል ምርጥ ሰዓቷን አስመዘግባለች። በመጋቢት ወር 2016 ዓ.ም በጋና በተካሄደው 13ኛው የአፍሪካ ጨዋታዎች በ3000 ሜትር መሰናክል ሴቶች ፍጻሜ የነሐስ ሜዳሊያ አግኝታለች። ሌላኛዋ ኢትዮጵያዊ አትሌት ሲምቦ አለማየሁ የማጣሪያ ውድድሯን በምድብ 2 ታደርጋለች። ሲምቦ በኦሊምፒክ ጨዋታዎች ስትሳተፍ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው። አትሌቷ እ.አ.አ በ2023 በጣልያን ፍሎረንስ በተካሄደው የዳይመንድ ሊግ ውድድር 9 ደቂቃ ከ00 ሴኮንድ ከ71 ማይክሮ ሴኮንድ የርቀቱ የግል ምርጥ ሰዓቷን አስመዝግባለች። ሲምቦ እ.አ.አ በ2022 በኮሎምቢያ ካሊ በተካሄደው 19ኛው የዓለም አትሌቲክስ ከ20 ዓመት በታች የአትሌቲክስ ሻምፒዮና በ3000 ሜትር መሰናክል የብር ሜዳሊያ አግኝታለች። በሶስት ምድብ በሚካሄደው የማጣሪያ ውድድር ከየምድቡ ከአንድ እስከ አምስት የሚወጡ አትሌቶች ሐምሌ 30 ቀን 2016 ዓ.ም ለሚካሄደው የፍጻሜ ፍልሚያ ያልፋሉ። ከምሽቱ 3 ሰዓት ከ35 ደቂቃ የ800 ሜትር ሴቶች የግማሽ ፍጻሜ ውድድር ይደረጋል። በማጣሪያው አትሌት ፅጌ ዱጉማና አትሌት ወርቅነሽ መለሰ ይሳተፋሉ። ሁለቱም አትሌቶች ከትናንት በስቲያ በተደረገው የመጀመሪያ ዙር ማጣሪያ ከየምድባቸው አንደኛ በመውጣት ለግማሽ ፍጻሜው ማለፋቸው ይታወቃል። የመጀመሪያ የኦሊምፒክ ተሳትፎዋን እያደረገች የምትገኘው አትሌት ወርቅነሽ መለሰ በምድብ 1 ውድድሯን ታደርጋለች። አርብ በነበረው የመጀመሪያ ዙር ማጣሪያ 1 ደቂቃ ከ58 ሴኮንድ ከ7 ማይክሮ ሴኮንድ በመግባት የግል ምርጥ ሰዓቷን በ68 ማይክሮ ሴኮንድ አሻሽላለች። በምድብ 2 የምትገኘው አትሌት ፅጌ ዱጉማ እ.አ.አ ግንቦት 18 2024 በአሜሪካ ሎስ አንጀለስ በተካሄደ ወድድር 1 ደቂቃ ከ57 ሴኮንድ ከ56 ማይክሮ ሴኮንድ የርቀቱን የግል ምርጥ ሰዓት አስመዘግባለች። ወጣቷ ተስፈኛ አትሌት በመጋቢት ወር 2016 ዓ.ም በስኮትላንድ ግላስኮው በተካሄደው 19ኛው የወርልድ አትሌቲክስ የዓለም የቤት ውስጥ ሻምፒዮና እንዲሁም በጋና አክራ በተደረገው 13ኛው የአፍሪካ ጨዋታዎች በ800 ሜትር የወርቅ ሜዳሊያዎችን አግኝታለች። በሶስት ምድብ በሚደረገው የማጣሪያ ውድድር ከየምድቡ አንደኛና ሁለተኛ የሚወጡ አትሌቶች ለፍጻሜ ያልፋሉ። በተጨማሪም ከእያንዳንዱ ምድብ በተመሳሳይ ፈጣን ሰዓት ያስመዘገቡ ሁለት አትሌቶች ፍጻሜውን ይቀላቀላሉ። ከምሽቱ 4 ሰዓት ከ10 ደቂቃ በሚካሄደው የ1 ሺህ 500 ሜትር ግማሽ ፍጻሜ አትሌት ኤርሚያስ ግርማና አትሌት ሳሙኤል ተፈራ ይወዳደራሉ። ኤርሚያስ ከትናንት በስቲያ በተደረገው ማጣሪያ 1ኛ እንዲሁም ሳሙኤል 6ኛ በመውጣት ለግማሽ ፍጻሜው ደርሰዋል። አትሌት ኤርሚያስ በሰኔ ወር 2016 ዓ.ም በፊንላንድ በተካሄደ ውድድር 3 ደቂቃ ከ34 ሴኮንድ ከ73 ማይክሮ ሴኮንድ በርቀቱ የግል ምርጥ ሰዓቱን አስመዝግቧል። በመጋቢት ወር 2016 ዓ.ም በጋና አክራ በተካሄደው 13ኛው የአፍሪካ ጨዋታዎች በርቀቱ የብር ሜዳሊያ ማግኘቱ ይታወሳል። ሌላኛው ተወዳዳሪ አትሌት ሳሙኤል ተፈራ ከሶስት ዓመት በፊት በፈረንሳይ ሞናኮ በተካሄደ ውድድር 3 ደቂቃ ከ30 ሴኮንድ ከ71 ማይክሮ ሴኮንድ የርቀቱን የግል ምርጥ ሰዓቱን አስመዝግቧል። አትሌት ሳሙኤል በ17ኛው እና 18ኛው የዓለም አትሌቲክስ የቤት ውስጥ ሻምፒዮናዎች በ1500 ሜትር የወርቅ ሜዳሊያ አግኝቷል። በሁለት ምድብ ተከፍሎ በሚካሄደው የማጣሪያ ውድድር ከየምድቡ ከአንድ እስከ ስድስት የሚወጡ አትሌቶች ለፍጻሜው ያልፋሉ።ከረፋዱ 5 ሰዓት ከ5 ደቂቃ ላይ በሚካሄደው የ3000 ሜትር መሰናክል ሴቶች የማጣሪያ ውድድር ሎሚ ሙለታና ሲምቦ አለማየሁ ኢትዮጵያ ወክለው ይሳተፋሉ። በኦሊምፒክ ጨዋታዎች ሁለተኛ ተሳትፎዋን የምታደርገው አትሌት ሎሚ በማጣሪያው በምድብ 1 ትወዳደራለች። በቶኪዮ በተካሄደው 32ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች በተመሳሳይ ርቀት ባደረገችው ማጣሪያ 10ኛ ወጥታ ለፍጻሜ አላለፈችም። ሎሚ እ.አ.አ በ2021 በኔዘርላንድ ሄንግሎ በተካሄደ ውድድር 9 ደቂቃ ከ14 ሴኮንድ ከ04 ማይክሮ ሴኮንድ በመግባት የርቀቱን የግል ምርጥ ሰዓቷን አስመዘግባለች። በመጋቢት ወር 2016 ዓ.ም በጋና በተካሄደው 13ኛው የአፍሪካ ጨዋታዎች በ3000 ሜትር መሰናክል ሴቶች ፍጻሜ የነሐስ ሜዳሊያ አግኝታለች። ሌላኛዋ ኢትዮጵያዊ አትሌት ሲምቦ አለማየሁ የማጣሪያ ውድድሯን በምድብ 2 ታደርጋለች። ሲምቦ በኦሊምፒክ ጨዋታዎች ስትሳተፍ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው። አትሌቷ እ.አ.አ በ2023 በጣልያን ፍሎረንስ በተካሄደው የዳይመንድ ሊግ ውድድር 9 ደቂቃ ከ00 ሴኮንድ ከ71 ማይክሮ ሴኮንድ የርቀቱ የግል ምርጥ ሰዓቷን አስመዝግባለች። ሲምቦ እ.አ.አ በ2022 በኮሎምቢያ ካሊ በተካሄደው 19ኛው የዓለም አትሌቲክስ ከ20 ዓመት በታች የአትሌቲክስ ሻምፒዮና በ3000 ሜትር መሰናክል የብር ሜዳሊያ አግኝታለች። በሶስት ምድብ በሚካሄደው የማጣሪያ ውድድር ከየምድቡ ከአንድ እስከ አምስት የሚወጡ አትሌቶች ማክሰኞ ሐምሌ 30 ቀን 2016 ዓ.ም ለሚካሄደው የፍጻሜ ፍልሚያ ያልፋሉ። ከምሽቱ 3 ሰዓት ከ35 ደቂቃ የ800 ሜትር ሴቶች የግማሽ ፍጻሜ ውድድር ይደረጋል። በማጣሪያው አትሌት ፅጌ ዱጉማና አትሌት ወርቅነሽ መለሰ ይሳተፋሉ። ሁለቱም አትሌቶች ከትናንት በስቲያ በተደረገው የመጀመሪያ ዙር ማጣሪያ ከየምድባቸው አንደኛ በመውጣት ለግማሽ ፍጻሜው ማለፋቸው ይታወቃል። የመጀመሪያ የኦሊምፒክ ተሳትፎዋን እያደረገች የምትገኘው አትሌት ወርቅነሽ መለሰ በምድብ 1 ውድድሯን ታደርጋለች። አርብ በነበረው የመጀመሪያ ዙር ማጣሪያ 1 ደቂቃ ከ58 ሴኮንድ ከ7 ማይክሮ ሴኮንድ በመግባት የግል ምርጥ ሰዓቷን በ68 ማይክሮ ሴኮንድ አሻሽላለች። በምድብ 2 የምትገኘው አትሌት ፅጌ ዱጉማ እ.አ.አ ግንቦት 18 2024 በአሜሪካ ሎስ አንጀለስ በተካሄደ ወድድር 1 ደቂቃ ከ57 ሴኮንድ ከ56 ማይክሮ ሴኮንድ የርቀቱን የግል ምርጥ ሰዓት አስመዘግባለች። ወጣቷ ተስፈኛ አትሌት በመጋቢት ወር 2016 ዓ.ም በስኮትላንድ ግላስኮው በተካሄደው 19ኛው የወርልድ አትሌቲክስ የዓለም የቤት ውስጥ ሻምፒዮና እንዲሁም በጋና አክራ በተደረገው 13ኛው የአፍሪካ ጨዋታዎች በ800 ሜትር የወርቅ ሜዳሊያዎችን አግኝታለች። በሶስት ምድብ በሚደረገው የማጣሪያ ውድድር ከየምድቡ አንደኛና ሁለተኛ የሚወጡ አትሌቶች ለፍጻሜ ያልፋሉ። ከእያንዳንዱ ምድብ በተመሳሳይ ፈጣን ሰዓት ያስመዘገቡ ሁለት አትሌቶች ፍጻሜውን ይቀላቀላሉ። ከምሽቱ 4 ሰዓት ከ10 ደቂቃ በሚካሄደው የ1 ሺህ 500 ሜትር ግማሽ ፍጻሜ አትሌት ኤርሚያስ ግርማና አትሌት ሳሙኤል ተፈራ ይወዳደራሉ። ኤርሚያስ ከትናንት በስቲያ በተደረገው ማጣሪያ 1ኛ እንዲሁም ሳሙኤል 6ኛ በመውጣት ለግማሽ ፍጻሜው ደርሰዋል። አትሌት ኤርሚያስ በሰኔ ወር 2016 ዓ.ም በፊንላንድ በተካሄደ ውድድር 3 ደቂቃ ከ34 ሴኮንድ ከ73 ማይክሮ ሴኮንድ በርቀቱ የግል ምርጥ ሰዓቱን አስመዝግቧል። በመጋቢት ወር 2016 ዓ.ም በጋና አክራ በተካሄደው 13ኛው የአፍሪካ ጨዋታዎች በርቀቱ የብር ሜዳሊያ ማግኘቱ ይታወሳል። ሌላኛው ተወዳዳሪ አትሌት ሳሙኤል ተፈራ ከሶስት ዓመት በፊት በፈረንሳይ ሞናኮ በተካሄደ ውድድር 3 ደቂቃ ከ30 ሴኮንድ ከ71 ማይክሮ ሴኮንድ የርቀቱን የግል ምርጥ ሰዓቱን አስመዝግቧል። አትሌት ሳሙኤል በ17ኛው እና 18ኛው የዓለም አትሌቲክስ የቤት ውስጥ ሻምፒዮናዎች በ1500 ሜትር የወርቅ ሜዳሊያ አግኝቷል። በሁለት ምድብ ተከፍሎ በሚካሄደው የማጣሪያ ውድድር ከየምድቡ ከአንድ እስከ ስድስት የሚወጡ አትሌቶች ለፍጻሜው ያልፋሉ።
ኢትዮጵያን በውሃ ዋና ስፖርት የምትወክለው ሊና አለማየሁ በኦሊምፒክ ጨዋታዎች የማጣሪያ ውድድሯን ዛሬ ታደርጋለች
Aug 3, 2024 206
አዲስ አበባ ፤ ሐምሌ 27/2016 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያን በውሃ ዋና ስፖርት የምትወክለው ሊና አለማየሁ በ50 ሜትር ሴቶች የነጻ ቀዘፋ ውድድር ወደ ግማሽ ፍጻሜ ለማለፍ የማጣሪያ ውድድሯን ዛሬ ታከናውናለች። ኢትዮጵያ በኦሊምፒክ ጨዋታዎች በውሃ ዋና ስፖርት ስትሳተፍ የዘንድሮው ለአራተኛ ጊዜ ነው። ዛሬ 9ኛ ቀኑን ባስቆጠረው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች ኢትዮጵያ ከአትሌቲክስ ውጪ በምትሳተፍበት የውሃ ዋና የስፖርት ዓይነት የማጣሪያ ውድድር ይደረጋል። ዋናተኛዋ ሊና አለማየሁ በ50 ሜትር ሴቶች የነጻ ቀዘፋ ውድድር ትሳተፋለች። ውድድሩ ከቀኑ 6 ሰዓት ላይ 30 ሺህ 680 ተመልካች በሚያስተናግደው ‘París La Défense Arena’ ሁለገብ የቤት ውስጥ የስፖርት ውድድር ማዕከል ይከናወናል። ለመጀመሪያ ጊዜ በኦሊምፒክ ጨዋታዎች የምትሳተፈው ሊና በማጣሪያው በምድብ 2 የምትገኝ ሲሆን በአጠቃላይ በምድቡ 8 ተወዳዳሪዎች ለግማሽ ፍጻሜው ለማለፍ ይፋለማሉ። የ50 ሜትር ሴቶች የነጻ ቀዘፋ ውድድር ማጣሪያ በ10 ምድቦች ተከፍሎ የሚካሄድ ሲሆን ከየምድቡ አንደኛ የሚወጡ ዋናተኞች ወደ ግማሽ ፍጻሜው ያልፋሉ። በተጨማሪም ከምድቦቹ ፈጣን ሰዓት ያስመዘገቡ ተጨማሪ 6 አትሌቶች ወደ ቀጣዩ ዙር ይሸጋገራሉ።   ዋናተኛዋ ሊና ወደ ቀጣዩ ዙር ለማለፍ ከሚያስችሏት ሁለት እድሎች አንዱን ካሳካች በዕለቱ ከምሽቱ 3 ሰዓት ከ39 ደቂቃ ለሚካሄደው የግማሽ ፍጻሜ ውድድር ማለፏን ታረጋግጣለች። ሊና ለግማሽ ፍጻሜው አልፋ ማምሻውን በሚደረገው ውድድር ከምድቧ 1ኛ ወይም ፈጣን ሰዓት ከሚያስመዘግቡ 8 ዋናተኞች አንዷ መሆን ከቻለች ነገ ከምሽቱ 1 ሰዓት ከ30 ላይ ለሚካሄደው የፍጻሜ ውድድር አላፊ ትሆናለች። 31 ሴኮንድ ከ87 ማይክሮ ሴኮንድ የርቀቱ የግል ምርጥ ሰዓቷ ነው። ምርጥ ሰዓቷን ያስመዘገበችው በመጋቢት ወር 2016 ዓ.ም በጋና በተካሄደው 13ኛው የአፍሪካ ጨዋታዎች በ50 ሜትር ሴቶች ነጻ ቀዘፋ ውድድር ነው። ዋናተኛዋ ሊና በ50 ሜትር ሴቶች ነጻ ቀዘፋ መወዳደር የጀመረችው እ.አ.አ በ2018 ነው። ዋናተኛዋ ከዚህ ቀደም የ100 ሜትር ሴቶች ነጻ ቀዘፋ፣ የ4 በ100 (4x100) ነጻ ቀዘፋ የዱላ ቅብብልና 50 ሜትር ቢራቢሮ በዓለም አቀፍና አህጉራዊ መድረክ ላይ ተሳትፋለች። ሊና በ33ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች የመክፈቻ ስነ ስርዓት ከ20 ኪሎ ሜትር ወንዶች የእርምጃ ተወዳዳሪ ምስጋና ዋቁማ ጋር የኢትዮጵያን ባንዲራ መያዟ የሚታወስ ነው። እ.አ.አ በ2016 በሪዮ ዴጄኔሮ በተካሄደው 31ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች ራሔል ገብረስላሴ እና እ.አ.አ በ2012 በለንደን በተከናወነው 30ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች ያኔት ስዩም በ50 ሜትር ሴቶች የነጻ ቀዘፋ ውድድር ቢሳተፉም ከመጀመሪያው ዙር ማለፍ አልቻሉም። ኢትዮጵያ በውሃ ዋና ስፖርት በኦሊምፒክ ጨዋታዎች ስትሳተፍ የአሁኑ ለአራተኛ ጊዜ ነው። የመጀመሪያ ተሳትፎዋ እ.አ.አ በ2012 በለንደን በተካሄደው 30ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች ነበር። በወቅቱ ሙሉዓለም ግርማ በ50 ሜትር ወንዶች ነጻ ቀዘፋ ውድድር እንዲሁም ያኔት ስዩም በ50 ሜትር ሴቶች ነጻ የቀዘፋ ውድድር ቢሳተፉም ከመጀመሪያው ዙር አላለፉም። እ.አ.አ በ2016 በሪዮ ዴጂኔሮ በተካሄደው 31ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች ሮቤል ኪሮስ በ100 ሜትር ነጻ ቀዘፋ፣ ራሔል ገብረስላሴ በ50 ሜትር ሴቶች ነጻ የቀዘፋ ውድድር ቢካፈሉም ከመጀመሪያ ዙር መሻገር አልቻሉም። በቶኪዮ እ.አ.አ በ2020 በተካሄደው 32ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች አብዱልማሊክ ቶፊክ በ50 ሜትር ወንዶች ነጻ ቀዘፋ ቢሳተፍም ወደ ቀጣዩ ዙር ሳይሸጋገር ቀርቷል።              
ኢትዮጵያውያን አትሌቶች የሚሳተፉባቸው የመካከለኛ ርቀት የማጣሪያ ውድድሮች ዛሬ ይደረጋሉ 
Aug 3, 2024 188
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 27/2016(ኢዜአ)፦በፓሪስ እየተካሄደ በሚገኘው 33ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች የኢትዮጵያ አትሌቶች የሚካፈሉባቸው የመካከለኛ ርቀት ውድድሮች ይካሄዳሉ። ዘጠነኛ ቀኑን ባስቆጠረው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች ዛሬ ከቀኑ 6 ሰዓት ከ20 ላይ በሚደረገው የ800 ሜትር ሴቶች የሁለተኛ ዙር ማጣሪያ (Repechage Round) አትሌት ሀብታም ዓለሙ በድጋሚ ለግማሽ ፍጻሜ ለማለፍ ትወዳደራለች። አትሌት ሀብታም ትናንት በመጀመሪያ ዙር ማጣሪያ 2 ደቂቃ ከ2 ሴኮንድ ከ19 ማይክሮ ሴኮንድ 7ኛ መውጣቷ ይታወቃል። በሁለተኛው ዙር ማጣሪያ በምድብ አራት የተደለደለች ሲሆን በምድቡ 8 አትሌቶች ይሳተፋሉ። የሁለተኛው ዙር የማጣሪያ ውድድር በአራት ምድብ ተከፍሎ የሚካሄድ ሲሆን ከየምድቡ አንደኛ የሚወጡ አትሌቶች በቀጥታ ወደ ግማሽ ፍጻሜው ይገባሉ። ከቀጥታ አላፊዎቹ ውጪ ሁለት ፈጣን ሰዓት ያላቸው ተወዳዳሪዎች ግማሽ ፍጻሜውን ይቀላቀላሉ። 1 ደቂቃ ከ56 ሴኮንድ ከ71 ማይክሮ ሴኮንድ የአትሌት ሀብታም የርቀቱ የግል ምርጥ ሰዓት ነው። በ800 ሜትር ሴቶች የሁለተኛ ዙር ማጣሪያ (Repechage Round) 31 አትሌቶች ይሳተፋሉ። ትናንት በ800 ሜትር ሴቶች በተካሄደው የመጀመሪያ ዙር ማጣሪያ አትሌት ፅጌ ዱጉማ አትሌት ወርቅነሽ መሰለ ከየምድባቸው አንደኛ በመውጣት በቀጥታ ለግማሽ ፍጻሜ ማለፋቸው ይታወቃል። በስድስት ምድብ ተከፍሎ በተደረገው የመጀመሪያ ዙር ማጣሪያ ከየምድቡ ከአንድ እስከ ሶስት የወጡ አትሌቶች በቀጥታ ለግማሽ ፍጻሜው አልፈዋል። የግማሽ ፍጻሜ ውድድሩ ነገ ከምሽቱ 3 ሰዓት ከ35 ደቂቃ ላይ ይከናወናል። ከምሽቱ 2 ሰዓት ከ15 ደቂቃ ላይ በሚደረገው በ1500 ሜትር ወንዶች የሁለተኛ ዙር ማጣሪያ (Repechage Round) ደግሞ አትሌት አብዲሳ ፈይሳ ይወዳደራል። አትሌት አብዲሳ ትናንት በ1500 ሜትር ማጣሪያ በምድብ 1 ተወዳድሮ በ3 ደቂቃ ከ39 ሴኮንድ ከ67 ማይክሮ ሴኮንድ 14ኛ ወጥቶ ውድድሩን ቢያጠናቅቅም ወደ ግማሽ ፍጻሜው ለማለፍ ሁለተኛ እድል አግኝቷል። የዓለም አቀፉ ኦሊምፒክ ኮሚቴ በ33ኛው ኦሊምፒክ ጨዋታዎች ‘Repechage Round’ ወይም ሁለተኛ እድል የተሰኘ አዲስ አሰራር አስተዋውቋል። በአዲሱ የውድድር መመሪያ መሰናክልን ጨምሮ ከ200 እስከ 1500 ሜትር ርቀቶች የሚሳተፉ አትሌቶች በመጀመሪያ ዙር ማጣሪያ ቀጥታ ወደ ቀጣዩ ዙር ባያልፉም በድጋሚ ወደ ግማሽ ፍጻሜ መግባት በሚያስችላቸው ሁለተኛ ዙር ማጣሪያ የመካተት እድል ያገኛሉ። ይህ ሁለተኛ እድል ውድድራቸውን ያቋረጡ፣ ከውድድር ውጪ የተደረጉና ውድድር ያላካሄዱ አትሌቶችን አይጨምርም። በዚሁ መሰረት አትሌት አብዲሳ ፈይሳ በ1500 ሜትር ወንዶች ማጣሪያ በምድብ 1 የተደለደለ ሲሆን ከአንድ እስከ ሶስት ከወጣ ወደ ግማሽ ፍጻሜ ያልፋል። አትሌት አብዲሳ 3 ደቂቃ ከ32 ሴኮንድ ከ37 ማይክሮ ሴኮንድ የርቀቱ የግል ምርጥ ሰዓቱ ነው። የሁለተኛው ዙር ማጣሪያው በሁለት ምድብ ተከፍሎ የሚደረግ ሲሆን 27 አትሌቶች ይሳተፋሉ። በ1500 ሜትር ወንዶች ትናንት በተካሄደው የመጀመሪያ ዙር ማጣሪያ አትሌት ኤርሚያስ ግርማና አትሌት ሳሙኤል ተፈራ በቀጥታ ወደ ግማሽ ፍጻሜ ማለፋቸው ይታወቃል። በሶስት ምድብ በተካሄደው ማጣሪያ ከየምድቡ ከአንድ እስከ ስድስት የወጡ አትሌቶች በቀጥታ ለግማሽ ፍጻሜው ማለፋቸው ይታወቃል። የወንዶች 1500 ሜትር የግማሽ ፍጻሜ ውድድር ነገ ከምሽቱ 4 ሰዓት ከ10 ደቂቃ ላይ ይደረጋል። በተያያዘም ትናንት በ10000 ሜትር ወንዶች የፍጻሜ ውድድር አትሌት በሪሁ አረጋዊ ሁለተኛ በመውጣት ለኢትዮጵያ የብር ሜዳሊያ አስገኝቷል። ኢትዮጵያ በ33ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች ያገኘችው የመጀመሪያ ሜዳሊያም ሆኗል።  
ኢትዮጵያ የመጀመሪያ ሜዳሊያዋን በአትሌት በሪሁ አረጋዊ አገኘች
Aug 3, 2024 190
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 26/2016(ኢዜአ)፦ በ33ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች ኢትዮጵያ በ10,000 ሜትር ወንዶች የፍጻሜ ውድድር አትሌት በሪሁ አረጋዊ ሁለተኛ በመውጣት ለኢትዮጵያ የብር ሜዳሊያ አስገኝቷል። ዩጋንዳዊው አትሌት ጆሹዋ ቼፕቴጋይ የኦሊምፒክን ክብረ ወሰን በመስበር ውድድሩን አሸንፏል። ማምሻውን በተካሄደው የፍጻሜ ፍልሚያ አትሌት በሪሁ 26 ደቂቃ ከ43 ሴኮንድ ከ44 ማይክሮ ሴኮንድ ሁለተኛ ወጥቷል። አትሌቱ በመጨረሻዎቹ ሜትሮች ላይ ከኋላ በመነሳት ያደረገው እልህ አስጨራሽ ትግል የሚደነቅ ነበር። አትሌት በሪሁ ከአራት ዓመት በፊት በቶኪዮ በተካሄደው 32ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች በተመሳሳይ ርቀት ተወዳድሮ 4ኛ መውጣቱ የሚታወስ ነው። በ32ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች በርቀቱ የወርቅ ሜዳሊያ አግኝቶ የነበረው ሰለሞን ባረጋ 26 ደቂቃ ከ44 ሴኮንድ ከ48 ማይክሮ ሴኮንድ 7ኛ ደረጃን ይዞ አጠናቋል። ሌላኛው ኢትዮጵያዊ አትሌት ዮሚፍ ቀጄልቻ 26 ደቂቃ ከ44 ሴኮንድ ከ02 ማይክሮ ሴኮንድ 6ኛ ወጥቷል። ውድድሩን ዩጋንዳዊው አትሌት ጆሹዋ ቼፕቴጋይ የግል አጨራረስ ብቃቱን በመጠቀም በ26 ደቂቃ ከ43 ሴኮንድ ከ14 ማይክሮ ሴኮንድ የኦሊምፒክ ክብረ ወሰንን በመስበር የወርቅ ሜዳሊያውን ወስዷል። ቼፕቴጋይ የርቀቱ የዓለም ክብረ ወሰን ባለቤት ነው። አሜሪካዊው ግራንት ፊሸር በ26 ደቂቃ ከ43 ደቂቃ ከ46 ሴኮንድ ሶስተኛ በመውጣት የነሐስ ሜዳሊያ አግኝቷል። ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ጥሩ ሊባል የሚችል የቡድን ስራ ቢሰሩም በመጨረሻው ዙር በአጨራረስ ድክመትና የመጨረሻዎቹ ሜትሮች ላይ ወደፊት ተስፈንጥሮ ሊወጣ የቻለ አትሌት ባለመኖሩ ምክንያት የታሰበው የወርቅ ሜዳሊያ ሳይገኝ ቀርቷል።
በ800 ሜትር ማጣሪያ አትሌት ወርቅነሽ መለሰና አትሌት ፅጌ ዱጉማ በቀጥታ ለግማሽ ፍጻሜ አለፉ
Aug 3, 2024 133
አዲሰ አበባ፤ሐምሌ 26/2016(ኢዜአ):- በ33ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች በ800 ሜትር ሴቶች የመጀመሪያ ዙር ማጣሪያ አትሌት ወርቅነሽ መለሰና አትሌት ፅጌ ዱጉማ በቀጥታ ለግማሽ ፍጻሜ አልፈዋል። አትሌት ሀብታም ዓለሙ በሁለተኛ ዙር ማጣሪያ(Repêchage Round) ወደ ግማሽ ፍጻሜ ለማለፍ ነገ በድጋሚ ትወዳደራለች። በምድብ 3 የተወዳደረችው አትሌት ወርቅነሽ መለሰ 1ደቂቃ ከ58 ሴኮንድ ከ7 ማይክሮ ሴኮንድ አንደኛ በመውጣት ለግማሽ ፍጻሜ አልፋለች። በርቀቱ የነበራትን የግል ምርጥ ሰዓትም አሻሽላለች። በምድብ 5 የነበረችው አትሌት ፅጌ ዱጉማ 1 ደቂቃ ከ57 ሴኮንድ ከ90 ማይክሮ ሴኮንድ አንደኛ ደረጃን በመያዝ ግማሽ ፍጻሜውን ተቀላቅላለች። በአንጻሩ በምድብ 1 ተደልድላ የነበረው አትሌት ሀብታም ዓለሙ 2 ደቂቃ ከ2 ሴኮንድ ከ19 ማይክሮ ሴኮንድ ሰባተኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች። ይሁንና አትሌት ሀብታም የዓለም አቀፉ የኦሊምፒክ ኮሚቴ በ33ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች እየተገበረ ባለው የሁለተኛ ዙር የማጣሪያ እድል(Repêchage Round) ነገ በድጋሚ ለግማሽ ፍጻሜ ለማለፍ ትወዳደራለች። ነገ ከቀኑ 6 ሰዓት ከ20 በሚካሄደው የሁለተኛ ዙር ማጣሪያ አትሌት ሀብታም በምትደለደልበት ምድብ ከአንድ እስከ ሶስት ከወጣች ወደ ግማሽ ፍጻሜው ታልፋለች። የ800 ሜትር ሴቶች የግማሽ ፍጻሜ ውድድር እሁድ ሐምሌ 28 ቀን 2016 ዓ.ም ከምሽቱ 3 ሰዓት ከ35 ደቂቃ ላይ ይካሄዳል። በስድስት ምድቦች በተካሄደው የማጣሪያ ውድድር ከየምድቡ ከአንድ እስከ ሶስት የወጡ አትሌቶች በቀጥታ ለፍጻሜው አልፈዋል። ዛሬ ቀደም ብሎ በ5000 ሜትር ሴቶች በተካሄደው የማጣሪያ ውድድር አትሌት ጉዳፍ ፀጋይ፣አትሌት እጅጋየሁ ታዬና አትሌት መዲና ኢሳ ለፍጻሜው አልፈዋል።
አትሌት ኤርሚያስ ግርማና አትሌት ሳሙኤል ተፈራ በ1500 ሜትር ማጣሪያ በቀጥታ ወደ ግማሽ ፍጻሜ አለፉ
Aug 2, 2024 149
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 26/2016(ኢዜአ)፦ አትሌት ኤርሚያስ ግርማና አትሌት ሳሙኤል ተፈራ በ1500 ሜትር ማጣሪያ በቀጥታ ወደ ግማሽ ፍጻሜ አልፈዋል። 33ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች ዛሬ 8ኛ ቀኑን ይዟል። ቀትር ላይ በ1500 ሜትር ወንዶች የመጀመሪያ ዙር ማጣሪያ ውድድር ተደርጓል። በምድብ 2 የተወዳደረው አትሌት ኤርሚያስ ግርማ 3 ደቂቃ ከ35 ሴኮንድ ከ21 ማይክሮ ሴኮንድ አንደኛ በመውጣት በቀጥታ ለግማሽ ፍጻሜ አልፏል። በምድብ 3 የተወዳደረው አትሌት ሳሙኤል ተፈራ 3 ደቂቃ ከ37 ሴኮንድ ከ34 ማይክሮ ሴኮንድ ስድስተኛ ደረጃን ይዞ በቀጥታ ወደ ግማሽ ፍጻሜው ተሸጋግሯል። በምድብ 1 የተወዳደረው አትሌት አብዲሳ ፈይሳ 14ኛ ደረጃን ይዞ አጠናቋል። ይሁንና አትሌት አብዲሳ ወደ ግማሽ ፍጻሜ ለማለፍ የሚያስችለውን ዳግም እድል አግኝቷል። የዓለም አቀፉ ኦሊምፒክ ኮሚቴ በ33ኛው ኦሊምፒክ ጨዋታዎች እየተገበረ ባለው አዲስ አሰራር አትሌቶቹ ውድድራቸውን አጠናቀው ወደ ቀጣዩ ዙር ባያልፉ እንኳን በድጋሚ ወደ ግማሽ ፍጻሜ መግባት በሚያስችላቸው የዙር ውድድር (repechage round) ይካተታሉ። በዚሁ መሰረት በማጣሪያው ውድድራቸውን ያጠናቀቁ ተወዳዳሪዎች ወደ “ሬፔቼጅ ራውንድ” በመግባት የሚወዳደሩ ሲሆን የተሻለ ውጤት ያስመዘገቡ አትሌቶች ወደ ግማሽ ፍጻሜው ያልፋሉ። በሶስት ምድብ በተካሄደው ማጣሪያ ከየምድቡ ከአንድ እስከ ስድስት የወጡ አትሌቶች በቀጥታ ለግማሽ ፍጻሜው አልፈዋል። “ሬፔቼጅ ራውንድ” ወይም ሁለተኛ እድል መሰናክልን ጨምሮ ከ200 እስከ 1500 ሜትር ርቀቶች አትሌቶች ወደ ቀጣዩ ዙር ባያልፉም ውድድራቸውን ካጠናቀቁ በድጋሚ የማለፍ እድል የሚያገኙበት የውድድር አማራጭ ነው።
የባህልና ስፖርት ሚኒስትር ሸዊት ሻንካ የአዲስ አበባ ስታዲየም የእድሳት ስራን ተመለከቱ
Aug 2, 2024 146
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 26/2016(ኢዜአ)፦የባህልና ስፖርት ሚኒስትር ሸዊት ሻንካ የአዲስ አበባ ስታዲየም እድሳትና በዙሪያው ያሉ የስፖርት መሰረተ ልማቶች እንቅስቃሴን ተመልክተዋል። ስታዲየሙ በዓለም አቀፉ የእግር ኳስ ማህበር (ፊፋ) እና በአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን (ካፍ) የተቀመጡ መስፈርቶችን ባለማሟላቱ የእግር ኳስ ጨዋታዎችን እንዳያስተናግድ መታገዱ ይታወቃል። ሚኒስትሯ ሸዊት ሻንካ ፊፋና ካፍ ባስቀመጡት መስፈርት መሰረት በስታዲየሙ እየተከናወኑ የሚገኙ የጥገና ስራዎችን ተዘዋውረው ተመልክተዋል።   የግንባታው ተቋራጮች ለሚኒስትሯ የስታዲየሙ እድሳት ያለበትን ደረጃና ተጓዳኝ ሁኔታዎች አስመልክቶ ገለጻ አድርገዋል። የአዲስ አበባ ስታዲየም እድሳት በሰኔ ወር 2013 ዓ.ም መጀመሩን ኢዜአ ከባህልና ስፖርት ሚኒስቴር ያገኘነው መረጃ ያመለክታል። የአዲስ አበባ ስታዲየም የእድሳት ስራ በሁለት ምዕራፍ የተከፈለ ሲሆን የመጀመሪያው ምዕራፍ ዕድሳት ስራ ተጠናቋል። የምዕራፍ ሁለት እድሳት ከ97 በመቶ በላይ የደረሰ ሲሆን ቀሪ ውስን ስራዎች በቅርቡ ይጠናቀቃሉ ተብሎ ይጠበቃል። ለስታዲየሙ የመጀመሪያ ምዕራፍ እድሳት 47 ሚሊዮን ብር እንዲሁም ለሁለተኛው ምዕራፍ 190 ሚሊዮን ብር ወጪ ተደርጓል።   ከስታዲየሙ ውጪ የመኪና ማቆሚያ ስፍራዎች፣ የበይነ መረብ የቲኬት ሽያጭና በቴክኖሎጂ የታገዘ የደህንነት ስርዓት መዘርጋትን ጨምሮ ሌሎች በስታዲየሙና ዙሪያ ያሉ የውጫዊ ገጽታ ስራዎች በመከናወን ላይ ይገኛሉ። የባህልና ስፖርት ሚኒስትር ሸዊት ሻንካ ከቀናት በፊት የብሔራዊ ስታዲየም (አደይ አበባ ስታዲየም) የግንባታ ሂደት በመጎብኘት ግንባታው በተቀመጠለት የጊዜ ገደብ ደረጃውን ጠብቆ እንዲሰራ አቅጣጫ መስጠታቸው የሚታወስ ነው።  
በፓሪስ ኦሊምፒክ ኢትዮጵያ ሜዳሊያ የምትጠብቅበት የ10 ሺህ ሜትር ወንዶች ፍጻሜ ዛሬ ማምሻውን ይደረጋል
Aug 2, 2024 205
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 26/2016(ኢዜአ)፦በ33ኛው የፓሪስ የኦሊምፒክ ጨዋታዎች ዛሬ የሚካሄደው የ10 ሺህ ሜትር ወንዶች ፍጻሜ በኢትዮጵያውያን ዘንድ በጉጉት ይጠበቃል። በፍጻሜው የሚካፈሉ የኢትዮጵያ አትሌቶች በ32ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች በተመሳሳይ ርቀት ሀገራቸውን ወክለው መወዳደራቸው ከዘንድሮው ተሳትፏቸው የተለየ ግጥምጥሞሽን ፈጥሯል። በፓሪስ እየተካሄደ የሚገኘው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች ዛሬ 8ኛ ቀኑ ላይ ይዟል። በ10 ሺህ ሜትር ወንዶች ፍጻሜ ከምሽቱ 4 ሰዓት ከ20 80 ሺህ ተመልካች በሚያስተናግደው ስታደ ፍራንስ ብሔራዊ ስታዲየም ይከናወናል። ኢትዮጵያ በፍጻሜው በሰለሞን ባረጋ፣ ዮሚፍ ቀጄልቻና በሪሁ አረጋዊ ትወከላለች። አትሌት ሰለሞን እ.አ.አ በ2020 በቶኪዮ በተካሄደው 32ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች በ10 ሺህ ሜትር ፍጻሜ የወርቅ ሜዳሊያ ማግኘቱ የሚታወስ ነው። ለሁለተኛ ጊዜ በኦሊምፒክ ጨዋታዎች የሚሳተፈው አትሌት ሰለሞን 26 ደቂቃ ከ34 ሴኮንድ ከ93 ማይክሮ ሴኮንድ የርቀቱ የግል ምርጥ ሰዓቱ ነው። የመምና የጎዳና ላይ ውድድር ሯጭ የሆነው ዮሚፍ ቀጄልቻ በኦሊምፒክ ሁለተኛ ተሳትፎውን ያደርጋል።   በቶኪዮ በተከናወነው 32ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች በ10000 ሜትር ፍጻሜ 8ኛ ደረጃን ይዞ ማጠናቀቁ የሚታወስ ነው። አትሌት ዮሚፍ እ.አ.አ ሰኔ 14 2024 በስፔን ማላጋ በተካሄደ የ10 ሺህ ሜትር ውድድር 26 ደቂቃ ከ31 ሴኮንድ ከ01 ማይክሮ ሴኮንድ በማስመዝገብ የርቀቱን የግል ምርጥ ሰዓት አስመዝግቧል። ሌላኛው በውድድሩ ኢትዮጵያን ወክሎ የሚሳተፈው አትሌት በሪሁ አረጋዊ ነው፤በሪሁ በ32ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች በ10000 ሜትር ተወዳድሮ 4ኛ ደረጃን ይዞ አጠናቋል።   አትሌቱ እ.አ.አ በ2022 በኔዘርላንድ ሄንግሎ በተካሄደ ውድድር 26 ደቂቃ 46 ሴኮንድ ከ13 ማይክሮ ሴኮንድ በመግባት የርቀቱን የግል ምርጥ ሰዓት ተመዝግቧል። ሶስቱ አትሌቶች እ.አ.አ በ2020 በተካሄደው 32ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች በ10000 ሜትር ወንዶች ፍጻሜ ኢትዮጵያን ወክለው ተወዳድረው ነበር፤ ዘንድሮውም በተመሳሳይ ርቀት መሳተፋቸው የተለየ አጋጣሚ ሆኗል። በ26 ደቂቃ ከ11 ሴኮንድ ከ00 ማይክሮ ሴኮንድ የርቀቱ የዓለም ክብረ ወሰን ባለቤት የሆነው የ27 ዓመቱ ዩጋንዳዊ ጆሹዋ ቼፕቴጋይ ውድድሩን ያሸንፋሉ ተብሎ ከሚጠበቁ አትሌቶች መካከል ይገኝበታል። ቼፕቴጋይ በ32ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች በ10000 ሜትር የብር፣ በ5000 የወርቅ ሜዳሊያ አግኝቷል፤ አትሌቱ የ5000 ርቀት የዓለም ክብረ ወሰን ባለቤት ጭምር ነው። በውድድሩ ጠንካራ ፉክክር ይደረጋል ተብሎ ይጠበቃል። ከፍጻሜው ውድድር በተጨማሪ ኢትዮጵያውያን አትሌቶች የሚሳተፉባቸው የማጣሪያ ውድድሮች ይደረጋሉ። ከቀኑ 6 ሰዓት ከ5 ደቂቃ በ1500 ሜትር ወንዶች ማጣሪያ ሳሙኤል ተፈራ፣ ኤርሚያስ ግርማና አብዲሳ ፈይሳ ይወዳደራሉ። አትሌቶቹ በሚወዳደሩባቸው ምድቦች ከአንድ እስከ ስድስተኛ ያለውን ደረጃ ይዘው ካጠናቀቁ እሁድ ሐምሌ 28 ቀን 2016 ዓ.ም ለሚካሄደው የግማሽ ፍጻሜ ውድድር ያልፋሉ። የዓለም አቀፉ ኦሊምፒክ ኮሚቴ በ33ኛው ኦሊምፒክ ጨዋታዎች እየተገበረ ባለው አዲስ አሰራር አትሌቶቹ ውድድራቸውን አጠናቀው ወደ ቀጣዩ ዙር ባያልፉ እንኳን በድጋሚ ወደ ግማሽ ፍጻሜ መግባት በሚያስችላቸው የዙር ውድድር (repechage round) ይካተታሉ። “ሬፔቼጅ ራውንድ” መሰናክልን ጨምሮ ከ200 እስከ 1500 ሜትር ርቀቶች አትሌቶች ወደ ቀጣዩ ዙር ባያልፉም ውድድራቸውን ካጠናቀቁ በድጋሚ የማለፍ እድል የሚያገኙበት የውድድር አማራጭ ነው። ከምሽቱ 1 ሰዓት ከ10 ደቂቃ በ5000 ሜትር ሴቶች ማጣሪያ ጉዳፍ ፀጋይ፣ መዲና ኢሳና እጅጋየሁ ታዬ ይሳተፋሉ። አትሌቶቹ ከየምድባቸው ከ1 እስከ 8 ያለውን ደረጃ ይዘው ካጠናቀቁ ሰኞ ሐምሌ 29 ቀን 2016 ዓ.ም ለሚካሄደው የፍጻሜ ውድድር ማለፋቸውን ያረጋግጣሉ። ከምሽቱ 2 ሰዓት ከ45 በ800 ሜትር ሴቶች ማጣሪያ ፅጌ ዱጉማ፣ ሀብታም ዓለሙና ወርቅነሽ መለሰ ኢትዮጵያን ወክለው ይወዳደራሉ። አትሌቶቹ በየምድባቸው ከአንድ እስከ ሶስት ከወጡ እሁድ ሐምሌ 28 ቀን 2016 ዓ.ም ለሚካሄደው ግማሽ ፍጻሜ ያልፋሉ። በቀጥታ ካላለፉም በ “ሬፔቼጅ ራውንድ” የድጋሚ ማለፊያ የውድድር አማራጭ ውስጥ ይገባሉ። በተያያዘም ትናንት በ20 ኪሎ ሜትር ወንዶች የእርምጃ ውድድር ፍጻሜ አትሌት ምስጋና ዋቁማ 6ኛ በመውጣት መልካምና ተስፋ ሰጪ ውጤት አስመዝግቧል።
ኢትዮጵያ በኦሊምፒክ ጨዋታዎች ተሳትፎዋ እስካሁን ስንት ሜዳሊያ አግኝታለች? 
Aug 1, 2024 177
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 25/2016(ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ በኦሊምፒክ ጨዋታዎች ተሳትፎዋ እስካሁን ስንት ሜዳሊያ አግኝታለች? የ128 ዓመት ታሪክ ያለው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች የተጀመረው እ.አ.አ በ1896 በግሪክ አቴንስ ነበር። በወቅቱ 14 ሀገራት በታሪካዊው ስፖርታዊ ውድድር ላይ ተሳትፈዋል። ኢትዮጵያ በኦሊምፒክ ጨዋታዎች ላይ መሳተፍ የጀመረችው ውድድሩ ከተጀመረ ከ60 ዓመታት በኋላ ነው። ለመጀመሪያ ጊዜ በውድድሩ የተሳተፈችው በአውስትራሊያ ሜልቦርን እ.አ.አ በ1956 በተካሄደው 16ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች ነው። ኢትዮጵያም በመጀመሪያ ተሳትፎዋ በአትሌቲክስና ብስክሌት 12 ስፖርተኞችን ይዛ ቀርባለች። በመጀመሪያው የኦሊምፒክ ተሳትፎዋ ምንም ሜዳሊያ ባለመግኘቷ ደረጃ ውስጥ መግባት አልቻለችም።   ኢትዮጵያ የዘንድሮውን የኦሊምፒክ ተሳትፎዋ በውድድሩ ታሪክ ለ15ኛ ጊዜ ነው። ከዚህ ቀደም በነበራት የ14 ጊዜ ተሳትፎ በአትሌቲክስ፣ ብስክሌት፣ ቦክስ፣ ውኃ ዋናና ወርልድ ቴኳንዶ ስፖርቶች ተሳትፋለች። ኢትዮጵያ በኦሊምፒክ የእስካሁኑ ተሳትፎዋ 23 የወርቅ፣ 12 የብር እና 23 የነሐስ በአጠቃላይ 58 ሜዳሊያዎችን አግኝታለች። ሁሉም ሜዳሊያዎች የተገኙት በአትሌቲክስ ስፖርት ብቻ ነው። 36 አትሌቶች 58ቱን ሜዳሊያዎች አስገኝተዋል። ኢትዮጵያ በፓሪስ እየተካሄደ በሚገኘው 33ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች በአትሌቲክስና በውኃ ዋና 38 ስፖርተኞችን አሳትፋለች። የኦሊምፒክ ጨዋታዎች እስከ ነሐሴ 5 ቀን 2016 ዓ.ም ይቆያል።      
አትሌት ምስጋና ዋቁማ በ20 ኪሎ ሜትር የእርምጃ ውድድር 6ኛ ደረጃን ይዞ አጠናቀቀ
Aug 1, 2024 170
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 25/2016(ኢዜአ)፦በ33ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች የ20 ኪሎ ሜትር ወንዶች የእርምጃ ውድድር ፍጻሜ ኢትዮጵያን ወክሎ የተወዳደረው አትሌት ምስጋና ዋቁማ 6ኛ ደረጃን ይዞ አጠናቋል። በፓሪስ እየተካሄደ በሚገኘው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች የአትሌቲክስ መርሐ ግብር ዛሬ ተጀምሯል። ማለዳ ላይ በተደረገው የ20 ኪሎ ሜትር ወንዶች የእርምጃ ፍጻሜ ውድድር ምስጋና ዋቁማ 1 ሰዓት ከ19 ደቂቃ ከ31 ሴኮንድ በመግባት 6ኛ ደረጃን ይዞ አጠናቋል። አትሌት ምስጋና በውድድሩ በርቀቱ የኢትዮጵያን ክብረ ወሰንና የራሱን የግል ምርጥ ሰዓት አሻሽሏል። በመጀመሪያ የኦሊምፒክ ተሳትፎው አበረታች የሚባል ውጤት አስመዝግቧል። በውድድሩ ኢኳዶራዊው ብሪያን ዳንኤል ፒንታዶ 1 ሰዓት ከ18 ደቂቃ ከ55 ሴኮንድ አንደኛ በመውጣት የወርቅ ሜዳሊያ አግኝቷል።   ብራዚላዊው ካዮ ቦንፊም 1 ሰዓት ከ19 ደቂቃ ከ9 ሴኮንድ ሁለተኛ፣ ስፔናዊው አልቫሮ ማርቲን 1 ሰዓት ከ19 ደቂቃ ከ11 ሴኮንድ ሶስተኛ ደረጃን ይዘው አጠናቀዋል። የእርምጃ ውድድሩ በአስቸጋሪ የአየር ፀባይ ምክንያት በ30 ደቂቃ ዘግይቶ መጀመሩን የዓለም አቀፉ የኦሊምፒክ ኮሚቴ መረጃ ያመለክታል። በውድድሩ ላይ ከተሳተፉ 49 አትሌቶች መካከል 46ቱ ውድድራቸውን አጠናቀዋል። የፔሩው ሴዛር አጉስቶ ሮድሪጌዝና የሕንዱ አትሌት አክሽዲፕ ሲንግ ውድድሩን አቋርጠዋል። የ28 ዓመቱ የሜክሲኮ አትሌት ሆዜ ሉዊስ ከውድድሩ ውጪ እንዲሆን መደረጉን የዓለም አቀፉ ኦሊምፒክ ኮሚቴ መረጃ ያመለክታል። በተያያዘም የ20 ኪሎ ሜትር ሴቶች የእርምጃ ውድድር ፍጻሜ በአስቸጋሪ የአየር ሁኔታ ከተያዘለት ጊዜ 30 ደቂቃ ዘግይቶ እንደሚጀመር ታውቋል። በዚሁ መሰረት ውድድሩ ከረፋዱ 4 ሰዓት ከ50 ደቂቃ ላይ ይከናወናል።
በፓሪስ ኦሊምፒክ ኢትዮጵያ የምትሳተፍበት የአትሌቲክስ ውድድር ዛሬ ይጀመራል
Aug 1, 2024 166
አዲስ አበባ፤ሐምሌ 25/2016(ኢዜአ):- በፓሪስ እየተካሄደ በቢሚገኘው 33ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች ኢትዮጵያ የምትሳተፍበት የአትሌቲክስ ውድድር ዛሬ ይጀመራል። የፓሪስ ኦሊምፒክ ጨዋታዎች ከተጀመረ ዛሬ ሰባተኛ ቀኑን ይዟል። በውድድሩ ከ203 ሀገራት የተወጣጡ 10 ሺህ 500 ገደማ ስፖርተኞች በ32 የስፖርት ዓይነቶች በመሳተፍ ላይ ይገኛሉ። ከሀገራት በተጨማሪ በዓለም አቀፉ ኦሊምፒክ ኮሚቴ ጥላ ስር የሚወዳደሩ ገለልተኛ አትሌቶችና የስደተኞች ኦሊምፒክ ቡድን ተሳታፊ ናቸው። ኢትዮጵያም በአትሌቲክስና ውሃ ዋና 38 ስፖርተኞችን ታሳትፋለች። የኦሊምፒክ የአትሌቲክስ መርሐ ግብር ዛሬ እንደሚጀመር የዓለም አቀፉ ኦሊምፒክ ኮሚቴ መረጃ ያመለክታል። ከጠዋቱ 2 ሰዓት ከ30 በሚካሄደው የወንዶች የ20 ኪሎ ሜትር የእርምጃ የፍጻሜ ውድድር አትሌት ምስጋና ዋቁማ ኢትዮጵያን ወክሎ ይሳተፋል። አትሌት ምስጋና በተርኪዬ አንታሊያ ከተማ ሚያዚያ 13 ቀን 2016 ዓ.ም በተካሄደው 30ኛው የዓለም አትሌቲክስ የእርምጃ ውድድር የቡድን ሻምፒዮና ላይ በ20 ኪሎ ሜትር እርምጃ ውድድር 1 ሰዓት ከ20 ደቂቃ ከ51 ሴኮንድ በመግባት በርቀቱ የግሉን ምርጥ ሰዓት አስመዝግቧል። አትሌቱ የገባበት ጊዜ የኢትዮጵያ የርቀቱ ክብረ ወሰንም ነው። በሰኔ ወር 2016 ዓ.ም በካሜሮን ዱዋላ በተካሄደው 23ኛው የአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና በ2 ኪሎ ሜትር የእርምጃ ውድድር አትሌት ምስጋና የወርቅ ሜዳሊያ አግኝቷል። በጋና ከየካቲት 29 እስከ መጋቢት 14 ቀን 2016 ዓ.ም በተከናወነው 13ኛው የአፍሪካ ጨዋታዎች አትሌት ምስጋና በ20 ኪሎ ሜትር የወንዶች እርምጃ ውድድር አንደኛ በመውጣት የወርቅ ሜዳሊያ ማግኘቱ የሚታወስ ነው። በሚያዚያ ወር 2015 ዓ.ም በዛምቢያ ንዶላ በተካሄደው 2ኛው የአፍሪካ የታዳጊና ወጣቶች አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ በ10 ሺህ ሜትር የእርምጃ ውድድር የወርቅ ሜዳሊያ ለሀገሩ አስገኝቷል። በ33ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች መክፈቻ ከዋናተኛዋ ሊና አለማየሁ ጋር የኢትዮጵያን ባንዲራ የያዘው አትሌት ምስጋና በውድድሩ ላይ ሲሳተፍ በታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው። አትሌቱ በ20 ኪሎ ሜትር የእርምጃ ውድድር ለመጀመሪያ ጊዜ የተሳተፈው በሞሪሺየስ ከሁለት ዓመት በፊት በተካሄደው 22ኛው የአፍሪካ የአትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ ነው። በወቅቱ አራተኛ ደረጃን ይዞ አጠናቋል። አትሌት ምስጋና ኢትዮጵያ ብዙም በማትታወቅበት የ20 ኪሎ ሜትር የእርምጃ ውድድር ስኬታማ የመሆን ሕልም አለው። አትሌቱ በውድድሩ የሚሳተፈው የዓለም አቀፉ ኦሊምፒክ ኮሚቴ (አይኦሲ) በሰጠው የዓለም አቀፍ ኮታ አማካኝነት ነው። በ20 ኪሎ ሜትር የወንዶች የእርምጃ ውድድር ከ26 ሀገራት የተወጣጡ 49 አትሌቶች ይሳተፋሉ። ስዊድናዊው ፔርሱስ ካርልስትሮም፣ ስፔናዊው አልቫሮ ማርቲን፣ ብራዚላዊው ካዮ ቦንፊምና ቻይናዊው ጁን ዣንግ ውድድሩን ያሸንፋሉ ተብለው ከሚጠበቁ አትሌቶች መካከል ይገኙበታል። በ20 ኪሎ ሜትር ወንዶች የኦሊምፒክ ክብረ ወሰን የተያዘው በቻይናዊው አትሌት ቼን ዲንግ ነው። አትሌቱ እ.አ.አ በ2012 በለንደን በተካሄደው 30ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች 1 ሰዓት ከ18 ደቂቃ ከ46 ሴኮንድ በመግባት የሪከርዱ ባለቤት ሆኗል። ከረፋዱ 4 ሰዓት ከ20 ላይ የ20 ኪሎ ሜትር ሴቶች የእርምጃ ውድድር ፍጻሜ ይካሄዳል። የ33ኛው ኦሊምፒክ ጨዋታዎች የአትሌቲክስ መርሐ ግብር እስከ ነሐሴ 5 ቀን 2016 ዓ.ም ይቆያል። ኢትዮጵያ በ1500 ሜትር፣ በ3000 ሜትር መሰናክል፣ በ5000 ሜትር፣ በ10000 ሜትርና በማራቶን በሁለቱም ጾታዎች ትሳተፋለች። በተጨማሪም በ800 ሜትር በሴቶችና በ20 ኪሎ ሜትር የእርምጃ ውድድር በወንዶች ትካፈላለች። ኢትዮጵያ ከአትሌቲክስ በተጨማሪ በውሃ ዋና በሴቶች በሊና አለማየሁ ተወክላለች። ዋናተኛዋ ሊና ሐምሌ 27 እና 28 ቀን 2016 ዓ.ም በሚካሄደው የ50 ሜትር ነጻ ቀዘፋ ውድድር ላይ ትሳተፋለች። 33ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች እስከ ነሐሴ 5 ቀን 2016 ዓ.ም ይቆያል።
ናፍቆት ድሬዳዋ በዓል በስፖርት ፌስቲቫል እየተከበረ ነው
Jul 28, 2024 456
ድሬዳዋ፤ ሐምሌ 21/2016(ኢዜአ)፦ ከተለያዩ የዓለም ሀገራት የመጡ የድሬዳዋ ተወላጆች እና ወዳጆች የተሳተፉበት ናፍቆት ድሬዳዋ በዓል በስፖርት ፌስቲቫል እየተከበረ ነው። በዓሉ በውጭ ካሉ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን ማህበረሰብ አባላት ጋር ያለውን ትስስር በማጠናከር አባላቱ በሀገር ገፅታ ግንባታና በልማት ላይ የድርሻቸውን እንዲወጡ ምቹ አጋጣሚ እየፈጠረ መሆኑን የድሬዳዋ አስተዳደር ከንቲባ ከድር ጁሃር ተናግረዋል። በዓሉ ዛሬ በስፖርት ፌስቲቫል በደመቀ ሁኔታ እየተከበረ ሲሆን በድሬዳዋ ከዚራ የዛፍ ጥላ ጎዳናዎች ላይ በእግር በመጓዝ እና የአስተዳደሩ ቀበሌዎች የተለያዩ የድሬዳዋ መገለጫ የሆኑትን የባህላዊ ምግቦች ትዕይንት በማሳየት ነው። የከዚራ የዛፍ ጥላ ስር የእግር ጉዞን የመሩት የድሬዳዋ አስተዳደር ከንቲባ ከድር ጁሃር ሲሆኑ የካቢኔ አባላትም ተሳትፈዋል። በአግር ጉዞው እና በምግብ ትዕይንቱ ላይ ከመላው ዓለም የመጡ የድሬዳዋ ተወላጆች እና ወዳጆች ታድመዋል።   ከንቲባ ከድር በእዚህ ወቅት እንደገለጹት፣ በዓሉ ዳያስፖራዎችን ከእናት ሀገራቸው እና ከቀያቸው ጋር ያላቸውን ትስስር በማጠናከር በሀገር ልማት፣ ሰላምና ብልፅግና ማረጋገጥ ላይ የድርሻቸውን እንዲወጡ ያግዛል። በተለይ በበዓሉ ላይ የተገኙ የሁለተኛው ትውልድ የዳያስፖራ ማህበረሰብ አባላት የወላጆቻቸውን ሀገር ወግ እና ባህላቸውን ለማወቅና ለመላመድ ጭምር አበርክቶው የጎላ መሆኑን ነው ያስረዱት። ባለፉት ዓመታት የዳያስፖራው ማህበረሰብ አባላት በኢንቨስትመንት እና በማህበራዊ ልማቶች ላይ ያበረከቱትን አስተዋጽኦን ከንቲባ ከድር በአብነት ጠቅሰዋል። የድሬዳዋ አስተዳደር ባህልና ቱሪዝም ፅህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ሚካኤል እንዳለ በበኩላቸው በዓሉ ለሦስተኛ ጊዜ እንደሚከበር ገልጸው፣ በዓሉ የሀገርን ገጽታ በመገንባትና የዳያስፖራው ማህበረሰብ በሀገር ሁለንተናዊ የለውጥ ጉዞ ላይ የድርሻውን እንዲወጣ ምቹ ሁኔታ ፈጥሯል ብለዋል። የዘንድሮው በዓል የተጀመረውን ይህን የለውጥ ጉዞ ለማጠናከር ያስችላል፤ በተለይ ድሬዳዋ ያላትን የቱሪስት መዳረሻዎች ለማስተዋወቅና ተጠቃሚነትን ለማሳደግ ጠቀሜታ አለው ሲሉም አክለዋል። ከዛሬ ጀምሮ ለአምስት ቀናት በሚዘልቀው ናፍቆት የድሬዳዋ በዓል ላይ በዳያስፖራው ማህበረሰብ የተገነቡ የተለያዩ የኢንቨስትመንት ፕሮጀክቶች ተመርቀው ወደ አገልግሎት ይገባሉ ተብሎ ይጠበቃል። በፌስቲቫሉ ላይ የብስክሌት ውድድሮች እንዲሁም በሶማሌ ክልል እና በድሬዳዋ አስተዳደር አመራሮች መካከል አዝናኝ የእግር ኳስ ውድድር እንደሚካሄድም ተጠቁሟል። ለሦስተኛ ጊዜ መከበር በጀመረው ናፍቆት ድሬ በዓል ላይ የዳያስፖራ ማህበረሰብ አባላት እና በሀገር ውስጥ ከተለያዩ ከተሞች የሚገኙ የድሬዳዋ ተወላጆችና ወዳጆች እየተሳተፉ ነው።      
የ33ኛው ኦሊምፒክ ጨዋታዎች የመክፈቻ ስነ ስርዓት እየተካሄደ ነው
Jul 26, 2024 480
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 19/2016(ኢዜአ)፦በፓሪስ የሚካሄደው 33ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች የመክፈቻ ስነ ስርዓት በመከናወን ላይ ይገኛል። በመክፈቻ ስነ ስርዓቱ ላይ የዓለም አቀፉ ኦሊምፒክ ኮሚቴ ፕሬዝዳንት ቶማስ ባክ፣ የፈረንሳይ ፕሬዝዳንት ኢማኑኤል ማክሮን፣ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ዋና ፀሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ፣ የተለያዩ የሀገራት መሪዎችና ተወካዮች እንዲሁም ሌሎች ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል። የዘንድሮው ኦሊምፒክ መክፈቻ በውድድሩ ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ ከስታዲየም ውጪ በወንዝ ላይ እየተደረገ ነው። በውድድሩ ላይ የሚሳተፉ 10 ሺህ 500 ስፖርተኞች በሰሜናዊ ፈረንሳይ በሚገኘው ሴይን ወንዝ ላይ በመርከብ የ3 ነጥብ 7 ኪሎ ሜትር በማቋረጥ የመክፈቻ ስነ ስርዓቱ የሚካሄድ ይሆናል። የመክፈቻ ስነ ስርዓቱን 300 ሺህ ተመልካች በስፍራው በመገኘት እንደሚከታተለው ይጠበቃል። በኦሊምፒክ ጨዋታዎች ከ203 ሀገራት የተወጣጡ 10 ሺህ 500 አትሌቶች በ32 የስፖርት አይነቶች እንደሚወዳደሩ የዓለም አቀፉ ኦሊምፒክ ኮሚቴ መረጃ ያመለክታል። ከሀገራቱ በተጨማሪ በዓለም አቀፉ ኦሊምፒክ ኮሚቴ ጥላ ስር ገለልተኛ አትሌቶችና የኦሊምፒክ የስደተኞች ቡድን ይሳተፋሉ። ኢትዮጵያም በአትሌቲክስና በውሃ ዋና የስፖርት ዓይነቶች በ38 ስፖርተኞች የምትካፈል ሲሆን አትሌቶቹ ከሚያዚያ 2016 ዓ.ም አንስቶ ከፍተኛ ዝግጅት ሲያደርጉ ቆይተዋል። 33ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች እስከ ነሐሴ 5 ቀን 2016 ዓ.ም ይቆያል።
በ33ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች ለሚሳተፉ ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ዓለም አቀፍ መስፈርትን ያሟላ ምርመራ ተደርጓል
Jul 26, 2024 399
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 19/2016(ኢዜአ)፦ በፓሪስ በሚካሄደው 33ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች ለሚሳተፉ ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ዓለም አቀፍ መስፈርትን ያሟላ ምርመራና የክትትል ስራ መከናወኑን የኢትዮጵያ ብሔራዊ ፀረ-አበረታች ቅመሞች ባለሥልጣን አስታወቀ። ኢትዮጵያ በኦሊምፒክ ጨዋታዎች የፀረ-አበረታች ቅመሞች አማካሪ ቡድን ውስጥ አፍሪካን በብቸኝነት መወከሏንም ገልጿል። 33ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች ዛሬ በፓሪስ የሚጀመር ሲሆን የዓለም አቀፉ ኦሊምፒክ ኮሚቴ በውድድሩ አበረታች ቅመሞች ምርመራና ቁጥጥር የተለየ ትኩረት ሰጥቷል። በዓለም አቀፉ ኦሊምፒክ ኮሚቴ የአበረታች ቅመሞች ምርመራ እንዲያደርግ ፈቃድ የተሰጠው ተቀማጭነቱን በስዊዘርላንድ ሉዛን ያደረገው ' ኢንተርናሽናል ቴስቲንግ ኤጀንሲ' የተሰኘው ገለልተኛ ተቋም ነው። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ፀረ-አበረታች ቅመሞች ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ መኮንን ይደርሳል የዓለም አቀፉ የፀረ-አበረታች ቅመሞች ኤጀንሲ(ዋዳ) ባስቀመጠው አሰራር መሰረት በውድድሩ ለሚሳተፉ ኢትዮጵያውያን አትሌቶች የአበረታች ቅመሞች ምርመራ መደረጉን ገልጸዋል። ባለስልጣኑ ስፖርተኞቹ ከአበረታች ቅመሞች የጸዱና ነፃ ሆነው እንዲወዳደሩ የቅድመ መከላከልና የቁጥጥር ስራ ማከናወኑን ተናግረዋል። ኢትዮጵያ ከአበረታች ቅመሞች የፀዳ ስፖርት እንዲፈጠር በትኩረት እየሰራች መሆኗን ጠቅሰው፤ በኦሊምፒክ ጨዋታዎችም ላይ ያለው መልካም ተሞክሮ እንዲቀጥል አስፈላጊ ጥረት መደረጉን ነው ዋና ዳይሬክተሩ የተናገሩት። ምርመራዎቹ ለስፖርተኞች የተከለከሉ ብሎ የለያቸው ቅመሞችን መሰረት በማድረግ መከናወኑና ሁሉም አትሌቶች ነጻ መሆናቸውን አመልክተዋል። ከክትትልና ቁጥጥር ስራው በተጨማሪ ለአትሌቶች የአበረታች ቅመሞችን አስመልክቶ የግንዛቤ መፍጠር ስራ ማከናወኑን ጠቅሰዋል። በቀጣይም ስፖርተኞች፣ አሰልጣኞችና የቡድን መሪዎች በጉዞና በውድድር ወቅት አበረታች ቅመሞችን አስመልክቶ አስፈላጊውን ጥንቃቄ እንዲያደርጉ አሳስበዋል። በተያያዘም በ33ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች ኢትዮጵያ የዓለም አቀፉ የፀረ-አበረታች ቅመሞች ኤጀንሲ(ዋዳ) ባቋቋመው አማካሪ ቡድን ውስጥ አፍሪካን የወከለች ብቸኛ ሀገር መሆኗን አመልክተዋል። ኢትዮጵያ አፍሪካን በወከል የአበረታች ቅመሞች ክትትልና ቁጥጥር ስራ ላይ እንደምትሳተፍና ለዋዳ የተለያዩ ምክረ ሀሳቦችን እንደምታቀርብ ተናግረዋል። የዓለም አቀፉ ኦሊምፒክ ኮሚቴ በፓሪስ በሚካሄደው 33ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች በአበረታች ቅመሞች ላይ ከሚያደርገው ቁጥጥርና ክትትል በተጨማሪ ስፖርተኞችን የማስተማር ስራ ያከናውናል። የዓለም አቀፉ ኦሊምፒክ ኮሚቴና የዓለም አቀፉ የፓራኦሊምፒክ ኮሚቴ ከእ.አ.አ 1960ዎቹ መጀመሪያ አንስቶ በኦሊምፒክ ውድድሮች ላይ የአበረታች ቅመሞች ክትትልና ቁጥጥር እንደሚያደርጉ መረጃዎች ያመለክታሉ። ዛሬ በፓሪስ በሚጀመረው በ33ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች በእያንዳንዱ ውድድር በሚደረግበት ስፍራ የፀረ-አበረታች ቅመሞች ቁጥጥር ቦታ ተዘጋጅቷል። በዚህም 360 የሚሆኑ ግለሰቦች የአበረታች ቅመሞች ናሙና በመውሰድ ምርምራ ያደርጋሉ፣ የአትሌቶችን በውድድር የመሳተፍ ተገቢነትም ያረጋግጣሉ ተብሏል። ኢትዮጵያ በዘንድሮው የፓሪስ በኦሊምፒክ ጨዋታዎች በአትሌቲክስና ውሃ ዋና የስፖርት ዓይነቶች በ38 ስፖርተኞች ትወከላለች።  
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም