ሰሜን ምዕራብ ዕዝ ግዳጅና ተልዕኮውን በጀግንነት እየተወጣ የሚገኝ ጠንካራ ዕዝ ነው -ጄኔራል አበባው ታደሰ 

አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 24/2016(ኢዜአ)፦ የጦር ኃይሎች ምክትል ጠቅላይ ኤታማዦር ሹም  ጄኔራል አበባው ታደሰ ሰሜን ምዕራብ ዕዝ በየትኛውም ጊዜና ቦታ የሚሠጠውን ግዳጅና ተልዕኮውን በጀግንነት እየተወጣ የሚገኝ ጠንካራ ዕዝ ነው ሲሉ ተናገሩ።
 
ይህንን ጥንካሬ ማስቀጠልና በቀጣይ ለሚሰጠው ግዳጅና ተልዕኮ በሁሉም መስክ የበለጠ መዘጋጀት ይጠበቅበታል ሲሉም አሳስበዋል። 

ጄኔራል አበባው ታደሠ ከዕዙ ከፍተኛ አመራሮች ጋር በመሆን በሰሜን ምዕራብ ዕዝ ጠቅላይ መምሪያ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር አካል በሆነው የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር ላይ ተሳትፈዋል። 

የመከላከያ ዘመቻ ዋና መምሪያ ኃላፊ ሌተናል ጄኔራል በላይ ስዩም፣ የሰሜን ምዕራብ ዕዝ አዛዥ ሌተናል ጄኔራል ብርሃኑ በቀለ፣የምስራቅ ዕዝ ምክትል አዛዥ ሜጄር ጄኔራል ግዛው ኡማን ጨምሮ ጄኔራል መኮንኖችና የጠቅላይ መምሪያው ስታፍ አባላት  በችግኝ ተከላው ላይ ተሳትፈዋል። 


 

በዕለቱም ለምግብነት የሚውሉ የፓፓዬ፣ የአቡካዶና ሌሎች የሀገር በቀል ችግኞች በክብር እንግዶቹና በጠቅላይ መምሪያው ስታፍ አባላት መተከላቸውን የኢፌዴሪ መከላከያ ሰራዊት መረጃ ያመለክታል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም