ከ550 ቢሊየን ብር በላይ ተጨማሪ በጀት ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሊቀርብ ነው 

አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 29/2016(ኢዜአ)፦ለ2017 በጀት ዓመት ከ550 ቢሊየን ብር በላይ ተጨማሪ በጀት በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ለማፀደቅ ዝግጅት መደረጉን ገንዘብ ሚኒስቴር ገለጸ።

የ2017 የፌዴራል መንግሥት በጀት 971 ነጥብ 2 ቢሊየን ብር ሆኖ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መጽደቁ ይታወሳል።

በጀቱ ከባለፈው ዓመት ጋር ሲነጻጸር የ21 ነጥብ 1 በመቶ እድገት ያሳየ ነበር።

ከዚህ ውስጥ ለመደበኛ በጀት 451 ነጥብ 3 ቢሊየን ብር ለካፒታል በጀት ደግሞ 283 ነጥብ 2 ቢሊየን ብር ተይዟል።

የገንዘብ ሚኒስትር ዴኤታው እዮብ ተካልኝ (ዶ/ር) የማክሮ ኢኮኖሚ ፖሊሲ ትግበራውን አስመልክቶ በሰጡት ማብራሪያ የፖሊሲ ማሻሻያው ዘላቂና አስተማማኝ ኢኮኖሚ ለመገንባት መሠረት የሚጥል ነው ብለዋል።

የፖሊሲ ማሻሻያው ተግባራዊ መደረጉን ተከትሎ የተለያዩ የፋይናንስ ምንጮች ድጋፍ እያደረጉ መሆኑንም ነው ያነሱት።

ይህን ተከትሎ ገንዘብ ሚኒስቴር ለ2017 በጀት ዓመት ይፋ ካደረገው የፌዴራል መንግሥት በጀት ተጫማሪ በጀት እንደሚያፀድቅ ተናግረዋል።

ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ለማፀደቅ የተዘጋጀው ከ550 ቢሊየን ብር በላይ ሲሆን፤ ከዚህ ወስጥ 240 ቢሊየን ብሩ ለማኅበራዊ ልማት የሚውል ነው ብለዋል።

መንግሥት የማክሮ ኢኮኖሚ ፖሊሲውን በተሟላ መልኩ ገቢራዊ ሲያደርግ ዝቅተኛ ገቢ ያላቸውን ዜጎች ታሳቢ በማድረግ መሆኑንም አብራርተዋል።

በዚህም ቋሚ ገቢ ያላቸውና በልማታዊ ሴፍትኔት ለሚታገዙ ዜጎች በቂ ድጎማ ለማድረግ ተጨማሪ በጀቱ ወሳኝ ሚና አለው ብለዋል።

ተጨማሪ በጀቱ ለዘይት፣ ለነዳጅና ለመድኃኒት ድጎማ እንዲውል በማድረግ በፖሊሲው ትግበራ ጊዜ ሊደርሱ የሚችሉ ስጋቶችን አስቀድሞ ለመከላከል እንደሚያስችል አብራርተዋል።

ከዚህ ባለፈ አገራዊ ወጪን በራስ ገቢ ለመሸፈን የሚደረገው ጥረት ተጠናክሮ እንደሚቀጥልና የፖሊሲ ትግበራው የገቢ አቅምን በማሳደግ በኩል ወሳኝ ሚና እንዳለው አንስተዋል።

ኢኮኖሚው የሚያመነጨውን ገቢ በአግባቡ በመሰብሰብ ለተለያዩ የልማት ሥራዎች እንደሚውል ጠቁመዋል።

 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም