የሩሲያ-አፍሪካ አጋርነት ፎረም የአፍሪካ ኅብረት አጀንዳ 2063 ዓላማን ለማሳካት የሚያስችል ነው - ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ(ዶ/ር)

አዲስ አበባ፤ ህዳር 1/2017(ኢዜአ)፦ የሩሲያ-አፍሪካ አጋርነት ፎረም የአፍሪካ ኅብረት አጀንዳ 2063 ዓላማን ለማሳካት የሚያስችል ነው ሲሉ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ(ዶ/ር) ገለጹ።

በውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ(ዶ/ር) የተመራ ልዑክ በሩሲያ-ሶቺ ከተማ በተካሄደው የሩሲያ-አፍሪካ አጋርነት ፎረም የሚኒስትሮች ጉባዔ ላይ ተሳትፏል፡፡

ጉባዔው በሩሲያ እና አፍሪካ መካከል ያለውን የረጅም ጊዜ ታሪካዊ ግንኙነት ያጎላ መሆኑን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ጌዲዮን ጢሞቲዎስ(ዶ/ር) በመድረኩ ገልጸዋል።


 

የሩሲያ-አፍሪካ አጋርነት ፎረም የአፍሪካ ኅብረት አጀንዳ 2063 ዓላማን ለማሳካት የሚያስችል መሆኑንም ተናግረዋል።

ኢትዮጵያ በአፍሪካ ቀንድ ሰላምና መረጋጋትን ለማስፈን ቁርጠኛ መሆኗን በመድረኩ መግለጻቸውን ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የተገኘው መረጃ ያመላክታል።

በአፍሪካ እና ሩሲያ መካከል በተለይም በውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት እና ንግድ ዘርፎች ያለውን የኢኮኖሚ ትብብር ማጠናከር እንደሚገባም አስገንዝበዋል፡፡

የጋራ ተጠቃሚነትን ከፍ ለማድረግም በሳይንስና ቴክኖሎጂ ዘርፍ ያለውን ትብብር ማሳደግ ይገባል ሲሉም ገልጸዋል፡፡

ምርታማነትን ማሳደግ፣ እንደ አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ያሉ አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን መጠቀም፣ ኢንዱስትሪን ማስፋት የአየር ንብረት ለውጥ ተግዳሮቶችን በመፍታት ረገድ ቁልፍ መስኮች መሆናቸውን አብራርተዋል፡፡

በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ማሻሻያ ለማድረግ እና አፍሪካ በድርጅቱ የፀጥታው ምክር ቤት ቋሚ ውክልና እንድታገኝ ሩሲያ ድጋፍ ለማድረግ ያላትን ዝግጁነት ኢትዮጵያ በደስታ ትቀበለዋለችም ነው ያሉት፡፡

ሚኒስትሩ ከጉባዔው ጎን ለጎን ከበርካታ የአፍሪካ ሀገራት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች ጋር የሁለትዮሽ ውይይት ማድረጋቸውም ተገልጿል፡፡

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም