በኬኒያ የተለያዩ አካባቢዎች እየጣለ ያለው ከባድ ዝናብ በርካቶችን ከቄያቸው አፈናቀለ - ኢዜአ አማርኛ
በኬኒያ የተለያዩ አካባቢዎች እየጣለ ያለው ከባድ ዝናብ በርካቶችን ከቄያቸው አፈናቀለ
አዲስ አበባ፤ህዳር 22/2017(ኢዜአ)፦በኬኒያ የተለያዩ አካባቢዎች እየጣለ ያለው ከባድ ዝናብ በርካቶችን ከቄያቸው ማፈናቀሉ ተገለጸ።
የኬንያ መንግስት በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች የጣለውን ከባድ ዝናብ ተከትሎ ተጨማሪ የጎርፍ አደጋ ሊከሰት እንደሚችል ማስጠንቀቂያ ሰጥቷል።
በኬኒያ የተለያዩ አካባቢዎች ወቅቱን ያልጠበቀ ከባድ ዝናብ እየጣለ ነው።
የአደጋ ምላሽ ቡድን አባላት በሚጥለው ከባድ ዝናብ ምክንያት በደረሰው የጎርፍ አደጋ የተጎዱ ከ240 በላይ አባወራዎችን አደጋ ከደረሰበት ሥፍራ ማንሳት መጀመራቸውን የሀገር ውስጥና ብሔራዊ አስተዳደር ሚኒስቴር በኬንያ ዋና ከተማ ናይሮቢ በሰጠው መግለጫ ማስታወቁን ዥንዋ ዘግቧል።
ሚኒስቴሩ በቪክቶሪያ ሀይቅ ተፋሰስ እና በሰሜን ምዕራብ ክልሎች ከፍተኛ ዝናብ በመጣሉ የጎርፍ አደጋ መከሰቱን በመግለጫው አስታውቋል።
"የአደጋ ምላሽ ቡድኑ ከብሔራዊ የመንግስት አስተዳደር ጋር በመተባበር በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች ያለውን ሁኔታ በመከታተል ለተጎዱ ወገኖች ድጋፍ እየሰጡ ነው" ሲል ዘገባው አመልክቷል።
በሳምንቱ መጨረሻ እርጥበት አዘል አውሎ ነፋሶች ይጠበቃል ሲል ያመለከተው ዘገባው፤ የሰሜን እና ምስራቃዊ ኬንያ እንዲሁም የባህር ዳርቻ እና የስምጥ ሸለቆ አካባቢዎች የጎርፍ ማስጠንቀቂያዎች መሰጠታቸውንም አክሏል።
ይሁን እንጂ በሚቀጥለው ሳምንት ዝናቡ ሊቀንስ የሚችልባቸው ሁኔታዎች እንደሚኖሩ የሚኒስቴሩን መግለጫ ጠቅሶ ዥንዋ አስታውቋል።
ሚኒስቴሩ በተጨማሪም ሀይቅ ዳር በሆነችው ኪሱሙ 200 የሚጠጉ አባዎራዎች መጎዳታቸውን አመልክቶ፤ 100 ሄክታር ማሳ ላይ የተዘሩ ሰብሎች መውደማቸውን ጠቁሟል።
"ለደህንነታቸው ሲባል ለጊዜው ወደ ሌላ ቦታ የሚዘዋወሩ የጎርፍ ተጋላጭ አካባቢ ነዋሪዎች የአደጋ ምላሽ ከሚሰጡ ቡድኖች ጋር እንዲተባበሩ ሚኒስቴሩ ማሳሰቡን" ዘገባው አመክቷል።
2024 መጀመሪያ ላይ የጣለው ያልተለመደ ዝናብ ኤልኒኖ ተብሎ ከሚጠራው የአየር ሁኔታ ጋር ተዳምሮ ለአየር ንብረት ለውጥ በጣም ተጋላጭ በሆነችው በኬንያ ከፍተኛ ጉዳት ማስከተሉን ዘገባው አስታውሷል።
በኬኒያ በመጋቢት እና ሰኔ መካከል በጣለው ከባድ ዝናብ እና ጎርፍ ከ300 በላይ ሰዎችን ህይወት መቅጠፉን ያመለከተው ዘገባው፣ በዚህ ወቅት 188 ሰዎች ቆስለዋል፣ 38 የሚሆኑት ሌሎች ሰዎች ደግሞ ደብዛቸው መጥፈቱን ዘገባው ጠቁሟል።
በነዚሁ ጊዚያት በጎርፉ ምክንያት ከ293 ሺህ 200 በላይ ሰዎች ተፈናቅለው ወደ 306 ሺህ 520 የሚጠጉ ሰዎች ጉዳት እንደደረሰባቸው ከብሔራዊ የአደጋ መከላከል ማእከል ያገኘውን መረጃ ጠቅሶ ዥንዋ ዘግቧል።