በአፍሪካ ሠማያት ሥር የነገሰዉ አየር መንገድ - ኢዜአ አማርኛ
በአፍሪካ ሠማያት ሥር የነገሰዉ አየር መንገድ
ዩሱፍ ባንጉራ ይባላሉ፡፡ እንግሊዝ ለንደን ከሚገኘዉ ኢኮኖሚክስ እና የፖለቲካ ሳይንስ ኮሌጅ የዶክተሬት ድግሪያቸውን አግኝተዋል፡፡ ለ22 ዓመታት በተለያዩ የምርምር ፕሮጀክቶች ላይ ሰርተዋል፡፡ በናይጄሪያ በአህመዱ ቤሎ ዩኒቨርሲቲ የፖለቲካ ሳይንስን ለስምንት ዓመታት አስተምረዋል፡፡ ተቀማጭነቱን ናይጀሪያ ባደረገው ‘ኢንተርቬንሽን’(Intervention) ለሚሰኝ የበይነ መረብ ጋዜጣ ፅሁፎቻቸውን ያቀርባሉ፡፡ ከሰሞኑ ስለኢትዮጵያ አየር መንገድ ስኬት ያቀረቡትን ፅሁፍ ወደ አማርኛ መልሰነዋል፡፡ እነሆ!
“የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከኢትዮጵያ አልፎ ዓለም አቀፍዊነትን ተላብሷል። ዛሬ ላይ ኢትዮጵያ በአቬሽን ዘርፍ ከአፍሪካ ሠማያት ባለፈ የዓለም ልዕለ ኃያል አገር ሆናለች ”ይላሉ ዩሱፍ ባንጉራ (ዶ/ር)
ዩሱፍ ባንጉራ (ዶ/ር)
በአፍሪካ ሠማያት ሥር የነገሰዉ አየር መንገድ
የአፍሪካ አቪዬሽን ኢንዱስትሪ ፋና ወጊ ነው፤ የአፍሪካ ሠማያት ልዕለ ኅይል። በየዓመቱ ሚሊዮኖችን ያጓጉዛል፤ በመላ ዓለም የመዳረሻዎቹ ብዛት የትየለሌ ነው። በሚያመነጨው ገቢ በአፍሪካ ግንባር ቀደም ነው። ይህ በአፍሪካ ሠማያት ላይ የነገሰው የኢትዮጵያ አየር መንገድ ነው።
እ.ኤ.አ በ2023 ብቻ 13 ነጥብ 8 ሚሊየን መንገደኞችን አጓጉዟል። በ40 አፍሪካ ሀገራት ዉስጥ 60 መዳረሻዎች አሉት። በዓለም ዙሪያ ወደ 136 ከተሞች ይበራል። እ.ኤ.አ 2023/24 ብቻ አየር መንገዱ 7 ነጥብ 2 ቢሊየን ዶላር ገቢ አግኝቷል። በዓለም አቀፍ ደረጃ በመዳረሻ ብዛት አራተኛዉ ግዙፍ አየር መንገድ ነው።
ከአፍሪካ ግዙፍ አየር መንገዶች ግንባር ቀደሙ ነው። በ2023 ብቻ አየር መንገዱ የ154 አዉሮፕላኖች ባለቤት ነበር። የግብፅ አየር መንገድ 70 አዉሮፕላኖች አሉት። በአዉሮፕላን ብዛት ሁለተኛ ደረጃ ላይ ይቀመጣል። የሞሮኮዉ አየር መንገድ ኤር ማሮክ በ51 አዉሮፕላኖች ሦስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። የኬኒያ አየር መንገድ 34 እንዲሁም የደቡብ አፍሪካ አየር መንገድ 17 አውሮፕላኖችን ይዘው ይከተላሉ።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ በመዳረሻ ብዛትም ቀዳሚ ነዉ፡፡ የሞሮኮዉ ኤር ማሮክ በ24 የአፍሪካ ከተሞች መዳረሻ አለዉ። የግብፅ አየር መንገድ ወደ 44 የአፍሪካ ከተሞች የሚበር ቢሆንም 16ቱ በዚያዉ በግብፅ ዉስጥ የሚገኙ ናቸዉ። በአፍሪካ ዉስጥ በመዳረሻ ብዛት ሊወዳደረዉ የሚችለዉ የኬኒያ አየር መንገድ ብቻ ነው። የኬኒያ አየር መንገድ በአፍሪካ ወደ 56 ከተሞች የበረራ መዳረሻዎች አሉት። ሆኖም የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ 60 የአፍሪካ ከተሞች በመብረር ብልጫዉን ይይዛል። የዓለም አቀፍ መደረሻቸዉን ስናይ ልዩነታቸዉ ሰፊ ነዉ። የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከአፍሪካ ዉጭ በሚገኙ 96 ከተሞች ሲበር፥ የኬኒያ ኤር ዌይስ ግን ወደ 14 ከተሞች ብቻ ይደርሳል። በሌላ አገላለፅ አንድ ሰዉ ከአፍሪካ ወደ እስያ፣ አውሮፓ፣ ሰሜን አሜሪካ ወይም ላቲን አሜሪካ የሚሄድ ከሆነ ከኬኒያ አየር መንገድ ይልቅ የኢትዮጵያ አየር መንገድን ምርጫዉ ያደረጋል ማለት ነዉ።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ በአፍሪካ የመጀመሪያው ዓለም አቀፍ አየር መንገድ ነው። የአየር መንገዱ በቻይና 10 ከተሞች፣ በአሜሪካ 8 ከተሞች፣ በህንድ 6 ከተሞች የበረራ መደረሻ አሉት። ወደ አብዛኛዎቹ የምዕራብ አውሮፓ አገሮች፤ ሩሲያ እና ፖላንድ ውስጥ ያሉ ከተሞች ጨምሮ ይበራል። በአብዛኛዎቹ የመካከለኛው ምሥራቅ እና የእስያ አገሮች በሚገኙ ከተሞች; እንዲሁም በላቲን አሜሪካ ውስጥ ብራዚል፣ አርጀንቲና፣ ቺሊ እና ኮሎምቢያ መዳረሻዎች አሉት።
በአቪዬሽን ኢንዱስትሪ ታሪክ ውስጥ በዋናነት የሚነሳው የኢትዮጵያ አየር መንገድ አፍሪካ እርስ በእርስ እና ከተቀረው ዓለም ጋር በማስተሳሰር ጉልህ ሚና እየተጫወተ ነው። እንደ ናይጄሪያ ኤርዌይስ፣ ጋና ኤርዌይስ እና ኤር አፍሪክ ያሉ ነባር አየር መንገዶች አገልግሎታቸዉ በአካባቢያዊ ደረጃ የተወሰነ ነዉ። የኢትዮጵያን አየር መንገድ ለአፍሪካዊያን ጥራት ያለው አገልግሎት በመስጠት የአህጉሪቷ ኩራት መሆኑን አስመስክሯል።
በአፍሪካዊያን ትስስር ውስጥ ትልቅ ሚና እየተጫወተ ያለ አየር መንገድ ነዉ። አፍሪካዊያንን እርስ በርስ እና ከሌላዉ ዓለም ጋር በተመጣጣኝ ዋጋ ያገናኛል። አየር መንገዱ ባለፉት አምስት ዓመታት የአፍሪካ ምርጥ አየር መንገድ ሽልማትን በተከታታይ ማሸነፍ ችሏል።
አሁን ላይ ብዙ የአፍሪካ ሀገራት አየር መንገዶቻቸውን ለማስፋፋት ወይም ከኪሳራ ለመታደግ ከኢትዮጵያ አየር መንገድ ጋር መስራት ይፈልጋሉ። የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከዛምቢያ ኤርዌይስ፣ ማላዊ ኤርላየን፣ ኤር ኮንጎ እና ጊኒ ኤርዌይስ 50 በመቶ የሚጠጋ ድርሻ አለዉ። በ2023 በምዕራብ አፍሪካ ምርጥ አየር መንገድ ተብሎ ከተሸለመዉ አስካይ አየር መንገድ ደግሞ 27 በመቶ ድርሻ አለው። የኢትዮጵያ አየር መንገድ በአስካይ አየር መንገድ ስትራቴጂክ እና ቴክኒካል ኦፕሬሽን ይመራል። ኢትዮጵያዊ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ተመድቦለታል።
በአየር መንገዱ በነበረን ቆይታ ያየነዉ....
ይህን የአፍሪካ ኩራት የሆነዉን አየር መንገድ በቅርቡ ወደ ደቡብ አፍሪካ፣ ኢትዮጵያ እና ናይጄሪያ ባደረግነው ጉዞ በቅርበት አይተነዋል። አየር መንገዱን በስድስት ሳምንታት ጊዜ ውስጥ ስምንት ጊዜ ተጠቀመናል። ከጄኔቫ-አዲስ አበባ፣ ከአዲስ አበባ-ዊንድሆክ፣ ከኬፕታውን-አዲስ አበባ፣ ከአዲስ አበባ-ጄኔቫ፣ ከጄኔቫ-አዲስ አበባ፣ ከአዲስ አበባ-አቡጃ፣ ከሌጎስ-አዲስ አበባ እና ከአዲስ አበባ-ጄኔቫ ተንሸራሽረንበታል። በአውሮፓ የሚኖሩ ብዙ ናይጄሪያውያን በቀጥታ ወደ ሌጎስና አቡጃ በቀጥታ ከመብረር ይልቅ የኢትዮጵያን አየር መንገድ በመጠቀም በአዲስ አበባ አድርጎ መጓዝ ወጭ ቆጣቢ እንደሆነ ይናገራሉ።
ከሁለት ሳምንት በፊት ወደ አቡጃ እና ሌጎስ ስንጓዝ የኢትዮጵያ አየር መንገድን በመምረጣችን የትኬታችንን ዋጋ ከ50 ከመቶ በላይ ቀንሰናል። ብዙ ተሳፋሪዎች አሁን ተመሳሳይ ስሌት አላቸዉ። ከአዲስ አበባ ወደ ጄኔቫ የሄድንበት በረራ ከሌጎስ ወደ ማንቸስተር የሚሄዱ መንገደኞች ጋር ነበር። አዲስ አበባ ቦሌ አየር ማረፊያ ወደ አውሮፓ፣ እስያ እና መካከለኛው ምሥራቅ ትራንዚት በሚያደርጉ የምዕራብ፣ ምሥራቅ እና ደቡብ አፍሪካዊያን የተሞላ ነበር።
ወደተለያዩ አገራት ለሚገዙ አፍሪካዊያን አዲስ አበባ የቦሌ ኤርፖርት ዋና የአፍሪካዊያን መዉጫና መግቢያ በር ሆኖ ያገለግላል። አዲስ አበባ ቦሌ ኤርፖርት አራት ጊዜ ትራንዚት ባደረግንበት ወቅት ልክ ትልቅ ዓለም አቀፍ የንግድ ከተማ ውስጥ እንደሆንን እየተሰማን ነበር። አየር መንገዱ ለደህንነት ቅድሚያ ይሰጣል። ከተለያዩ አህጉራት የመጡ ብዙ ቁጥር ያላቸው ትራንዚት መንገደኞች ጥብቅ የደህንነት ፍተሻዎች ይደረግላቸዋል።
ጄምስ ፒርሰን፣ በአየር መንገዱ ቡኪንግ መረጃ መሠረት በ2023፤ 11 ሚሊዮን መንገደኞች በአዲስ አበባ ቦሌ አየር ማረፊያ በኩል ትራንዚት ማድረጋቸዉን ይናገራል። በአዲስ አበባ ቦሌ ኤርፖርት ዉስጥ ከአስሩ መንገደኞች ሰባቱ ትራንዚተር ናቸዉ። ለዚህ ከፍተኛ ቁጥር የትራንዚተር ቁጥር ቀጣናዊ እና ክፍለ አህጉራዊ የገበያ ቦታዎች አስተዋፅኦ አበርክተዋል።
ወደ አፍሪካ ለሚደረጉ በረራዎች ዱባይን ተክቷል….
አዲስ አበባ የአፍሪካ ዱባይ ሆናለች፡፡ መግቢያቸዉም መዉጫቸዉም አዲስ አበባ ናት፡፡ የኢትዮጵያ መንግሥት አየር መንገዱ የአፍሪካዊያን የመግቢያ እና መዉጫ በር መሆኑን ተረድተዋል። ለተሳፋሪዎች በርካታ የደህንነት ፍተሻዎች ይደረጋል። ትራንዚተሮች ሁለት ጠንካራ ፍተሻ እና አንድ ቀላል ፍተሻዎችን ማለፍ ይኖርባቸዋል። ጉዟቸው ከቦሌ ኤርፖርት የሚጀምሩ መንገደኞች አጠቃላይ አራት ፍተሻዎችን ማለፍ ይኖርባቸዋል። እነዚህ በርካታ ፍተሻዎች አሰልቺ እና አድካሚ ሊመስሉ ይችላሉ። ነገር ግን ለመንገደኞቹ ደህንነት ከፍተኛ ጥንቃቄ ለሚያደርግ አየር መንገድ የግድ ነዉ።
መንግሥታት ትርፋማ ድርጅቶችን ማስተዳደር ይችላሉ?
እንደ ኒዮሊበራል የገበያ አስተሳሰብ መንግሥት ትርፋማ የንግድ ድርጅቶችን በባለቤትነት ሲያስተዳድር ብልሹ አሰራር ይስፋፋል ብሎም ድርጅቱን ለኪሳራ ይዳርገዋል። መከራከሪያቸዉ ደግሞ መንግሥት ትላልቅ የንግድ ተቋማትን ሲያስተዳድር ለኃላፊዎቹ ፖለቲካዊ ሹመት ይሰጣል። በመሆኑም እነዚህን ተሿሚዎች ቢያጠፉ ለመቅጣት ወይም ከሥራ ለማባረር ይቸግራል በማለት መንግሥት አትራፊ የንግድ ተቋማትን ማስተዳደ እንደሌለበት ይገልጻል። ይህ ካልሆነ ድርጅቱ ይከስራል ወይም ከገበያ ይወጣል።
ነገር ግን ይህ የኒዮሊበራል የገበያ ፍልስፍና በኢትዮጵያ አየር መንገድ አይሰራም። አየር መንገዱ ሙሉ በሙሉ በመንግሥት ሥር ይተዳደራል። እዚህ ላይ ጥያቄ መሆን የሚገባዉ በአፍሪካ በመንግሥት ባለቤትነት የተያዙ አየር መንገዶች ለምን ለኪሳራ ተዳረጉ የሚለዉ ነዉ። ለምሳሌ የደቡብ አፍሪካ አየር መንገድ በመንግሥት ቢተዳደርም በገበያዉ ለመቆየት እየተንገዳገደ ይገኛል።
የኢትየጵያ አየር መንገድ በ1946 እና 1975 መካከል ባሉት ጊዜያት ከትራንስ ወርልድ አየር መንገድ /TWA/ ጋር በነበረው ስትራቴጂካዊ አጋርነት የቴክኖሎጂ አጠቃቀም አቅምን አሳድጓል። እንዲሁም መልካም የሥራ ባህል እንዲያዳብር እንደረዳዉ አቶ አርከበ ዕቑባይ እና ታፈረ ተስፋቸዉ ያቀረቡት ጽሑፍ ያሳያል።
ከአጼ ኃይለ ሥላሴ ከመንበረ ሥልጣን መወገድ በኋላ ወታደራዊ ሶሻሊስት መንግሥት ሥልጣኑን ሲቆናጠጥ አየር መንገዱ ከሞላ ጎደል ለኪሣራ ተዳርጎ ነበር። ከ1991 ወዲህ ያሉ መንግሥታት የኢትዮጵያ አየር መንገድን ተቋማዊ ነፃነት እንዲኖረዉ አድርገዋል።
አየር መንገዱ ዓለም አቀፍ የንግድ መርሆች መሠረት በማድረግ ሥራውን ያከናዉናል። ይህ ነፃነቱ በአፍሪካ የአቪዬሽን መሪ ሆኖ በዓለም አቀፍ ገበያ ውስጥ ጎልቶ እንዲወጣ አስችሎታል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ መንግሥታት ዓለምአቀፍ ትርፋማ ተቋማትን መፍጠርና ማስተዳደር እንደሚችሉ ማሳያ ይሆናል።
የዚህ ፅሁፍ ሀሳብ የደራሲዉ መሆኑን እንገልፃለን፡፡