የአሜሪካ 39ኛ ፕሬዝዳንት ጂሚ ካርተር በ100 ዓመታቸው አረፉ

አዲስ አበባ፤ ታኅሳስ 21/2017 (ኢዜአ)፡- የአሜሪካ 39ኛው ፕሬዝዳንት የነበሩት ጂሚ ካርተር በ100 ዓመታቸው ከዚህ ዓለም በሞት ተለዩ።

የቀድሞ ፕሬዝዳንቱ በመጨረሻው ጊዜያቸው በፔሊንስ ጆርጂያ በሚገኘው መኖሪያ ቤታቸው “በቤተሰቦቻቸው ተከበው ነበር” ሲል ካርተር ሴንተር በሰጠው መግለጫ አስታውቋል።

ፕሬዝዳንት ጆ ባይደን ካርተርን “ውድ ጓደኛ” እና “ልዩ መሪ” ሲሉ የተሰማቸውን ሀዘን አስመልክተው በሰጡት መግለጫ ገልጸዋል።

ተመራጩ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በበኩላቸው አሜሪካውያን ለቀድሞው ፕሬዝዳንት “የምስጋና እዳ አለባቸው” ብለዋል።

የአሜሪካ መንግሥት የቀድሞ ፕሬዝዳንቱን ሥርዓተ ቀብር ለመፈጸም ዝግጅት እያደረገ ስለመሆኑ የሲ.ኤን.ኤን ዘገባ አመልክቷል።

የቀድሞ ፕሬዝዳንት ጂሚ ካርተር ባለቤት ሮዛሊን ካርተር እ.ኤ.አ. በ2023 ወርሃ ኅዳር በ96 ዓመታቸው ከዚህ ዓለም በሞት ተለይተዋል።

ሁለቱ ጥንዶች ለ75 ዓመታት አብረው በትዳር አብረው ኖረዋል።

ካርተር እ.ኤ.አ. ከ1977 እስከ 1981 አሜሪካን በፕሬዝዳንትነት መርተዋል።

ፕሬዝዳንት ካርተር እ.ኤ.አ. በ1980 በተካሄደው ፕሬዝዳንታዊ ምርጫ የካሊፎርኒያ ገዢ በነበሩት ሮናልድ ሬገን ሲሸነፉ የካርተር ማእከልን እ.ኤ.አ. በ1982 አቋቁመው ወደ በጎ አድራጎት ተግባር ተሰማርተው ነበር።

የካርተር ማእከልም ከኢትዮጵያ ጋር በሽታን በከላከልና በመቆጣጠር፣ የምግብ ምርትን በማሳደግ፣ ግጭትን በማስወገድና በምርጫ ታዛቢነት በመሳተፍ የረጅም ጊዜ ግንኙነት ነበረው።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም