ባለፉት የለውጥ አመታት ለመጪው ቴክኖሎጂ ዝግጁ የሚያደርጉ ምቹ መደላድሎች ተፈጥረዋል-የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር

አዲስ አበባ፤ጥር 22/2017(ኢዜአ)፦ባለፉት የለውጥ አመታት ለመጪው ቴክኖሎጂ ዝግጁ የሚያደርጉ ምቹ መደላድሎች መፈጠራቸውን የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር አስታወቀ።

የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ይሹሩን አለማየሁ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንዳሉት ከለውጡ በኋላ ባሉት አመታት ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ተዘጋጅቶ ወደ ትግበራ በመገባቱ በዘርፉ በርካታ ለውጦች መጥተዋል።

እስካሁን ባለው 11 ነጥብ 5 ሚሊዮን ዜጎች ለዲጂታል መታወቂያ መመዝገባቸውን ገልፀው፥ የዲጂታል ክፍያ አማራጮችን የማስፋት ስራ እየተሰራ መሆኑንም አስረድተዋል።

በዚህም የቴሌኮምና ኤሌክትሮኒክስ ተደራሽነትን በማስፋት በኩል ውጤታማ ስራ መከናወኑን ጠቅሰው፥ ኔትወርኩን ከ 2 ጂ ወደ 5 ጂ ማሳደግ መቻሉን ተናግረዋል።

ከ800 በላይ የመንግስት አገልግሎቶች በኦንላይን እየተሰጡ መሆናቸውን ጠቁመዋል።

አስተማማኝ የዲጂታል ስርዓት ለመፍጠር በተከናወኑ ተግባራት ጠንካራ የሳይበር ደህንነት ተቋም መገንባቱን አብራርተዋል።

በአምስት ሚሊዮን ኢትዮጵያዊያን ኮደርስ መርኃ ግብር ከ460 ሺህ በላይ ዜጎች ለስልጠና መመዝገባቸውንና ከእነዚህም ውስጥ ከ127 ሺህ በላይ የምስክር ወረቀት መውሰዳቸውን ገልፀዋል።

በለውጡ አመታት ስታርት አፖችን ለማበረታታት የሚያስችሉና ለመጪው ቴክኖሎጂ ዝግጁ የሚያደርጉ ምቹ መደላድሎች መፈጠራቸውንና የተለያዩ የህግ ማዕቀፎች መዘጋጀታቸውንም አስረድተዋል።

የለውጡ ሂደት የሚኒስቴሩን አቅም በማሳደግ ቴክኖሎጂን ከመቅዳት በራስ ወደ መፍጠር ያሸጋገረና ለገበያ የሚቀርቡ የፈጠራ ውጤቶች እንዲበራከቱ ማድረጉንም ጠቁመዋል።

ጥራቱን የጠበቀ ምርት ለአለም አቀፍ ገበያ ለማቅረብ የሚያስችል የጥራት መንደር መገንባቱንም ገልፀዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም