ነጋሪ 20

1

ነጋሪ 5ኛ ዓመት ቁጥር 20 መጋቢት 2014 ዓ.ም ዋጋ 15 ብር



2

ማ ስ ታ ወ ቂ ያ



3



4

አድራሻ፦ አራዳ ክፍለ ከተማ

ስልክ ቁጥር +251-11-55-00-11 +251-11-56-39-31

+251-11-56-52-21

ፋክስ ቁጥር +251-11-55-16-09 enanegari@gmail.comበኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት

በየሁለት ወሩ የምትታተም መጽሔት

ማውጫ

መስከረም 2009 ዓ.ም ተመሰረተች

“አዲስ ገጽ አዲስ ምዕራፍ”

አርበኝነት በዕይታዊ

ጥበብ መነጽር

26 32

18

የኢኮኖሚ ለውጡ አንዱ ተስፋ



5

ዋና አዘጋጅ አብዱራህማን ናስር

ም/ ዋና አዘጋጅ ጌታቸው ሰናይ

ከፍተኛ አዘጋጅ ፍቅርተ ባልቻ

አዘጋጅ አየለ ያረጋል መንገሻ ገብረሚካኤል

አርት ዳይሬክተር ነብዩ መስፍን nebiyou1st@gmail.com

ፎቶግራፍ በሀይሉ አስፋው

እርምት ባለሙያ ትዝታ ሁሴን

እነሆ!

አሁን ያለንበት ወቅት በሁሉም አቅጣጫ ጥንካሬ፣ ትጋትና ጥበብ የሚጠይቅ ነው።

በዚህ ወር መጀመሪያ ላይ ብልጽግና ፓርቲ “ከፈተና ወደ ልዕልና” በሚል መሪ ሀሳብ የመጀመሪያውን ጉባዔ አካሂዷል። በበርካታ ፈተናዎች ውስጥ ያለፈው ፓርቲ በጉባዔው ላይ የተደረሱባቸው ዋና ዋና ሀሳቦችን በማንሳት በዚህ ዕትም ቀርበዋል። የአገሪቷን ሰላምና ደህንነት ከማረጋገጥ፣ ኢኮኖሚውን ከችግር ለማውጣትና የኑሮ ውድነትን ለመቋቋም የሚያስችሉ እርምጃዎችን በመውሰድ ፓርቲው ምን ዓይነት አቋም ያዘ? የሚሉ ሀሳቦች ተነስተዋል።

እያንዳንዱ ዜጋ ጉልበቱን፣ እውቀቱንና ገንዘቡን በማቀናጀትና በንቃት በመሳተፍ የአገራችንን እድገት ማፋጠን ግድ የሚልበት ወቅት ነው። በውጭ የሚኖረው ኢትዮጵያዊና ትውልደ ኢትዮጵያዊ የወቅቱን ሁኔታ በመገንዘብ ያለውን ተሳትፎ እያሳደገ መምጣትም የወቅቱ ጥያቄ ነው። ለዚህ ነው ነጋሪ በቁጥር ሃያ ዕትሟ የዳሰሰቻቸው ርዕሰ ጉዳዮች እነዚህን መሰረታዊ ነጥቦች እንዲጎሉ ቅድሚያ የሰጠችው።

ነጋሪ መጽሄታችሁ “የአገራቸው ልጆች በቁርጥ ቀን” በማለት በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያንና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን ሀሳብ ያጋራቻችሁ ከየት ተነስቶ እዚህ ደረሰ የሚሉትን ነጥቦች በመጥቀስ ነው። ስደተኛ ተቀብላ በክብር ስታስተናግድ የቆየች አገር በተለያዩ ጊዜያት በተፈጠሩ ፓለቲካዊ ሁኔታዎች ምክንያት ዜጎቿ ለፍልሰት መዳረጋቸወን ታስታውሰናለች። ይህ እውነታ እንዳለ ሆኖ በውጭ የሚኖሩት ወደ አገራቸው በመምጣት፣ ባሉበትም ለአገራቸው የሚጠቅም ነገር በማድርግ ከጎኗ መሆን ከጀመሩ ሰነባብተዋል። በአሁኑ ወቅት ለአገራቸው የሚያደርጉት አስተዋጽኦ እያደገም መጥቷል። የፖለቲካ፣ የኢኮኖሚና ማህበራዊ ተሳትፏቸው እየጎለበተ መምጣቱን አንድ ርዕሰ ጉዳይ አድርገነዋል።

የአድዋ ድል በሁሉም አቅጣጫ የሚታይ ነው። ኢትዮጵያ የነጻነት ቀንዲል የሆነችበት፣ አፍሪካዊያን ለትግል እንዲነሳሱ በሥነ ልቦና ያጀገነችበት የድል ብርሃን ነው። ይህን የድል ብርሃን በተለያየ መንገድ መፈተሽ ተገቢ ነው። ነጻነትን ከማወጅ ባሻገር በቀጣይ ዘመን የአድዋ የድል መንፈስ አስፈላጊ መሆኑን ጥቁምታ መስጠት ወቅቱ የሚጠይቀው ሆኗል። አፍሪካ ሰላምና መረጋጋትን በመፍጠር ነገን ለመዋጀት የአድዋ መንፈስ ያስፈልጋታል።

በተበታተነ ሳይሆን በአንድነት መንፈስ አህጉሪቷን ለመታደግ መነሳሳት የግድ ያስፈልጋል። 21ኛው ክፍለ ዘመን ለአፍሪካ መልካም እድልና ፈተና የያዘ ነው። እድሉን ለመጠቀም ህብረትና አንድነት ወሳኝ ነው። ሳይንስና ቴክኖሎጂን ታሳቢ ማድረግም አይከፋም። ይህን ለማድረግ ግን ከመቼውም ጊዜ በላይ ሰላምና ደህንነት ማረጋገጥ ያስፈልጋል። ፖለቲካዊ መረጋጋት ትኩረት የሚነፈገው ጉዳይ ሊሆን አይችልም።

አድዋ ልዩነትን ወደ ጎን በመተው ለነጻነት የተደረገ ትግል ነው። ዛሬም የአፍሪካ አገሮች ተበታትነው ሳይሆን በአንድነት በመሆን ዘመኑን መዋጀት ግድ ይላቸዋል። ይህን ጉዳይ “አፍሪካ - 21ኛውን ክፍለ ዘመን በአድዋ የድል መንፈስ” በሚል ርዕስ ሀሳባችንን ለማጋራት ወደናል።

ታሪክን በልዩ ልዩ የጥበብ ዘርፎች መሰነድ ዘመናት የተሻገረ ይትበሃል ነው። ከዚህ የታሪክ መሰነጃ መካከል የሥዕል ጥበብ አንዱ ነው። በዚህ ጥበብ ፍቅር ተተርኳል፣ ሰላም ተዘምሯል፣ የጦርነት አስከፊነት ተሰብኳል፣ ጀግንነት ታውጃል፣ ማንነት ተገልጿል . . . ብዙ ጉዳዮች ተዳሰዋል። ከብዙዎቹን አንዱ አርበኝነት በስነ ሥዕል እንዴት ታየች? የሚለውን ጥያቄ አንሰተን ምላሽ ፈልገናል። ከዘመነ መነሻው እስከ አሁን ድረስ የጥበብ ትሩፋትን ዳሰናል። እንደምትወዱት እርግጠኞች ነን።

ሌሎች በግብርና፣ በጤና ዘርፍ ላይ ትኩረታቸውን ያደረጉ ያሉ ጽሁፎች ትምህርት ሰጪነታቸው ጉልህ ነው።

መልዕክትየአገራቸው ልጆች - በቁርጥ ቀን

6

ኢትዮጵያ የጥቁሮች የነጻነት ቀንዲል

12

አፍሪካ 21ኛውን ክፍለዘመን በአድዋ የድል

መንፈስ 40

የዳግማዊ አድዋ ብስራት 48

ኢኮኖሚውን ለመታደግ - ግብርና

54

የእውቀት ማዕድ 60

የሁሉንም ትኩረት የሚሻው የጾታ ጥቃት

66

እንመርመር፤ እንከተብ! 72



6

የአገራቸው ልጆች- በቁርጥ ቀን!

የመረጃ መረብ



7

የአገራቸው ልጆች- በቁርጥ ቀን!

በነፃነት አብርሃም

ኢትዮጵያ ለበርካታ ዘመናት የፍልሰት መነሻ እንዳልነበረች የታሪክ ድርሳናት ምስክር ናቸው። የሌሎች አገሮችን ዜጎች ተቀብላ በማስተናገድ ቀዳሚ ስፍራ ይዛ የቆየች፤ አሁንም የተለያዩ ጎረቤት አገሮች ዜጎችን በመቀበልና መጠለያ አዘጋጅታ በመንከባከብ ትታወቃለች። ከዚህ ቀደም የእስራኤል፣ የአርመኖች፣ የዓረብ፣ የግሪክ፣ የቱርክ ስደተኞችን በእንግድነት በመቀበል አክብራ በማስተናገድ

ስምና ዝና ማትረፏን ታሪክ ዘክሮታል። በክብር ተቀብላ በደግነት አስተናግዳና በፍቅር ተንከባክባ ያኖረች ስለመሆኗ ብዙዎች ምስክርነታቸውን ያለማቅማማት ይለግሷታል።

የታሪክ ድርሳናት እንደሚያመለክቱት ወደ ውጭ መሄድ የተጀመረው እኤአ በ1903 ተማሪዎችን ወደ አሜሪካ በመላክ ነው። ትምህርት ፍለጋ። ይህ የሆነው ንጉሰ ነገስት ምኒልክ ከአሜሪካ ጋር በጀመሩት የዲፕሎማሲ ግንኙነት መሰረት ነበር። በተመሳሳይም በዓፄ ኃይለሥላሴ የሥልጣን ዘመን ከአውሮፓና አሜሪካ የትምህርት እድል ያገኙ ኢትዮጵያዊያን ወደ እዚያው ተጉዘዋል። በወቅቱም ወደ ውጭ ከሄዱት መካከል ብዙዎቹ ወደ አገራቸው በመመለስና የተማሩትን በተግባር ለመተርጎም በሚያስችላቸው ስራ ላይ በመሰማራት ለውጥ ለማምጣት መሞከራቸውን መረጃዎች ያመለክታሉ።

ነገር ግን የ1966 ዓ.ም አብዮት መፈንዳትን ተከትሎ ቀደም ብለው የወጡ ዜጎች በሄዱበት አገር በመቅረት የስደት ኑሮን ለመጋፈጥ ተገደዋል። ኢትዮጵያ በእርስ በርስ ጦርነት ስትታመስ፣ ፖለቲካዊ አለመግባባቶች ሲፈጠሩ አንዱ



8

አሳዳጅ፣ ሌላው ተሳዳጅ በሆነበት ክፉ ጊዜ ፍልሰት እየተስፋፋ ሄደ። በአገሪቷ ተከስተው በነበሩ ማሕበራዊና ኢኮኖሚያዊ ምስቅልቅሎች ምክንያት ሕይወታቸውን ለማቆየትና ችግራቸውን ለማቃለል ፍልሰትን በአማራጭነት የተቀበሉት ብዙዎች ናቸው። የደርግ መንግሥት ተቀይሮ ኢህአዴግ አገሪቷን ከተቆጣጠረ በኋላም ወደ ውጭ አገር የሚሄዱ ዜጎች ቁጥር እያደገ መምጣቱን መረጃዎች ያመለክታሉ። ይህም ሆኖ ወደ ውጭ የሚፈልሱ ዜጎች ቁጥር ከምስራቅ አፍሪካ አገሮች ጋር ሲነጻጸር ዝቅተኛ ነው።

ይሁን እንጂ በሰሜን አሜሪካ፣ አውሮፓ፣ መካከለኛው ምስራቅ፣ አውስትራሊያና አፍሪካ አገሮች በፖለቲካ ስደተኝነት፣ በትምህርት እድልና በስራ ፍለጋ የፈለሱ ዜጎች ብዛት ከሶስት ሚሊዮን በላይ እንደሚጠጋ መረጃዎች ያሳያሉ።

በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያንና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን ሁሉም አንድ የሚያደርጋቸው ጉዳይ በኢትዮጵያ መጻኢ እድል ላይ የበኩላቸውን አስተዋጽኦ ለማድረግ ፍላጎታቸው ከፍተኛ መሆኑ ነው። ለዚህም ሌት ተቀን ሲለፉ ይስተዋላል። በማንኛውም ሁኔታና አጋጣሚ ከአገራቸው ወጥተው በሰው አገር የተለያዩ ፈተናዎች ቢገጥማቸውም የአገራቸው ደህንነት ያሳስባቸዋልና “እኔም ለአገሬ አለሁ” በሚል መንፈስ እየተረባረቡ ይገኛሉ። አገሬ ዞሮ መግቢያዬ ብቻ ሳይሆን “ከልቤ የማላወጣሽ የማልረሳሽ፤ የዘመናት አርማዬ ነሽ” በሚል

ከጎኗ መሆናቸውን በተለያዩ አጋጣሚዎችና መንገዶች ሲገልጹ ቆይተዋል፤ እየገለጹም ነው።

“አገራችን በከፍተኛ ደረጃ የሰው ኃይል ወደ ውጭ ከሚፈልሱባት አገሮች አንዷ መሆኗ እሙን ነው። ይህ በአገር ውስጥ ያለውን የሰለጠነ የሰው ኃይል ፍልሰት በተወሰነ ደረጃ መቀነስ ላይ ትኩረት ሰጥቶ የመስራትን፤ በሌላ በኩል ደግሞ በውጭ አገር ከሚኖሩ የዳያስፖራ አባላት ጋር ጠንካራ ትስስር በመፍጠር በአገር ውስጥ በሚካሄድ የልማት እንቅስቃሴዎች ላይ በንቃት የሚሳተፉበትንና ተጠቃሚ የሚሆኑበትን ምቹ ሁኔታ የመፍጠር አስፈላጊነትን በጉልህ የሚያመለክት ነው” በማለት ነው የዳያስፖራ ፖሊሲ በሚል ርዕስ የተሰራጨ ሰነድ የሚያትተው።

ቀደም ባሉት ዓመታት በአገራችን በተለያዩ ጊዜ በተከሰቱ ፖለቲካዊ ሁኔታዎች በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያንና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን በሚፈለገው መጠን በአገራቸው ጉዳይ ላይ ተሳትፎ እንዲያደርጉ ዕድሉ ሳይከፈትላቸው ቆይተዋል። በዓፄ ኃይለሥላሴ ሥርዓት በትምህርትም ሆነ በስራ ምክንያት ወደ ተለያዩ አገሮች የወጡ ዜጎች በ1953 ዓ.ም በንጉሱ ላይ የመፈንቅ ለመንግሥት ሙከራ ተደርጎ እስከ ከሸፈበት ወቅት ድረስ ከአገራቸው ጋር የነበራቸው ግንኙነት መልካም ነበር። ንጉሱም ወደ ውጭ በወጡ ወቅት በኤምባሲ ግብዣ በማድረግ አግኝተው እንደሚያነጋግሯቸው፣ እነርሱም በአክብሮት ይቀበሏቸው እንደነበር ታሪክ ያሳያል። የ1953 ዓ.ም መፈንቅ

ምንጭ፡- ኢትዮጵያን ዲያስፖራ ኤጀንሲ ድረገፅ



9

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ

አህመድ በአሜሪካና በአውሮፓ

አገሮች “በፍቅር እንደመር፤

በይቅርታ እንሻገር፤ ግንቡን

እናፍርስ፤ ድልድዩን እንገንባ” በሚል መርህ ባደረጉት

ጉዞና በውጭ ከሚኖሩት

ኢትዮጵያዊያንና ትውልደ

ኢትዮጵያዊያን ጋር በተፈጠረው

ቅርርብ የተገኘው ውጤት

ለአገራዊ የጋራ መግባባት

መልካም አጋጣሚ መፍጠሩ

እሙን ነው።

ለመንግሥት ሙከራ ከተደረገ በኋላ ግን ተማሪዎቹ ለእርሳቸው ያላቸው አመለካከት እየተቀየረ፣ እርሳቸውም እነርሱን የማግኘት ፍላጎት እያጡ መምጣታቸው ይነገራል። ዜጎች ከአገራቸው ጋር የነበረው ግንኙነት እየላላ መምጣት ወደ ኋላ ላይ የራሱ አሉታዊ ተጽዕኖ ማሳረፉ አልቀረም። ዘላቂ የሆነና በጠንካራ መሰረት ላይ የተገነባ ግንኙነት እንዳይፈጥሩ ሳያደርግ አልቀረም።

የደርግ መንግሥት ሥልጣን ከያዘም በኋላ ስደቱ እየከፋ፣ ግንኙነቱ እየጠፋ መጥቷል። በተለይም በሰሜን የአገሪቷ ክፍል ተጠናክሮ የነበረው የእርስ በርስ ጦርነትና በየቦታው ተፈጥሮ የቆየው ግጭት በውጭ የሚኖሩ ዜጎች ከአገራቸው ጋር ጠንካራ ትስስር እንዳይፈጥሩ፣ ህጋዊ መሰረት ያለው ግንኙነት እንዳይከሰት ማድረጉ እሙን ነው።

በኢትዮጵያ በወቅቱ በነበረው ተጨባጭ ሁኔታ መሰረት ደርግ ከስልጣን እስከሚወገድ ድረስ ባለው ጊዜ ከውስጥ ወደ ውጭ መፍለስ እንጂ ወደ አገር ውስጥ መመለስ ብርቅ ነበር። ምናልባት ቤተሰቦቻቸውን ለመጠየቅ የሚመጡ በስደት የሚኖሩበትን አገር ዜግነት የያዙ መሆናቸውን መረጃዎች ያመለክታሉ። በዚህ ወቅት አገር ከዜጎቿ ልታገኝ የሚገባውን መሰረታዊ ጥቅም አጥታለች። እነርሱም ከአገራቸው ማግኘት ያለባቸውን ጥቅም፣ የመብት ጥበቃና የተለያዩ ፍላጎቶቻቸው ሳይሟላላቸው ቀርቷል።

ደርግ በሚከተለው ርዕዮተ ዓለምም ሆነ እየተካሄደ በነበረው ጦርነት ምክንያት ዜጎች ከውጭ ምንም ዓይነት ነገር እንዳይልኩ አግዶ መቆየቱ፣ የእውቀት ሽግግር እንዳይካሄድ ምቹ ሁኔታ ያለመኖሩ፣ ቴክኖሎጂ ያለመስፋፋቱ በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያንና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን ለአገራቸው ሊያደርጉት የሚችሉት ሳያከናውኑ፤ የሕሊና ነፃነታቸውንና እርካታቸውን ሳያገኙ እንዲቆዩ አድርጓል። የእነርሱን ሙሉ ለሙሉ ተሳትፎ ለማድረግና የተዋጣለት ደረጃ ላይ ለማድረስ የተጀመረው ትግል ዛሬ ላይ መሰረቱን ልል አድርጎት ቆይቷል ማለት ይቻላል።

በውጭ ለሚኖሩ ኢትዮጵያዊያንና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን ነገሮች እየተቀየሩ የመጡት የኢህአዴግ መንግሥት ወደ ሥልጣን ከመጣ በኋላ ነው። በአገራቸው ጉዳይ ላይ የመሳተፍ እድል ቀስ በቀስ እየተከፈተ መጥቷል። ትውልደ ኢትዮጵያዊያን መሆናቸውን የሚያመለክት መታወቂያ በመስጠት ወደ አገራቸው እንዲገቡ፣ በአገራቸው ልማት ዘርፍ እንዲሰማሩ፣ መታወቂያውንም የያዙ በአገራቸው ውስጥ ስራ መስራት እንዲችሉ የተደረገበት ወቅት ነበር።

መንግሥት በውጭ የሚኖሩትን ዜጎች ወደ አገራቸው እንዲመለሱ፣ በልማት እንዲሳተፉ ጋብዟል። በአገሪቷ የነበሩ የተለያዩ አሳሪ ሕጎች ተቀይረው ምቹ ሁኔታ ለመፍጠር የሚያስችሉ አሰራሮች ተዘርግተዋል። በተለይም በ2000 ዓ.ም በኢትዮጵያ ሁለተኛ ሚሊኒየም ላይ ብዙዎቹ ኢትዮጵያዊያንና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን ወደ አገራቸው ለመግባት ችለዋል። ለዘመናት የናፈቋትን አገራቸውን በማግኘት ደስታቸውን ለመግለጽ በቅተዋል። በዚያውም በተቻላቸው መጠን

ለቤተሰቦቻቸው፣ ለአገራቸው ድጋፍ አድርገዋል። በተለያዩ መስኮች እውቀታቸውን ለማካፈል፣ ቴክኖሎጂ ወደ አገር ውስጥ እንዲገባ ለማድረግ እንደሚጥሩ ቃል ገብተዋል። በወቅቱ ኢህአዴግ የሚመራው መንግስት ባሳየው የአዲሱ ሚሊኒየም መልካም አቀባበል ምክንያት በውጭ በሚኖሩት ዜጎችና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን መካከል ግንኙነቱ እየተሻሻለ መምጣት መቻሉ ድጋፏን ከመቼውም ጊዜ በላይ አሳድጎት ነበር።

ነገር ግን በአገር ውስጥ በተጀመረው የለውጥ እንቅስቃሴና የፖለቲካ ውጥረት ምክንያት ግንኙነቱ ዳግም ሻከረ። በለውጥ እንቅስቃሴው ውስጥም በውጭ የሚኖሩትን ኢትዮጵያዊያንና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን የራሳቸውን አስተዋጽኦ ጀመሩ። በተቃውሞው ተሳተፉ። በተለያየ መልኩ ለውጡን በመደገፍ የአገር ውስጥ የፖለቲካ ለውጥ እንዲሳለጥ የበኩላቸውን ሚና ተጫወቱ። መገናኛ ብዙሃንና አዲሶቹን ሚዲያዎች በመጠቀም ፖለቲካዊ ተሳትፏቸውን አሳደጉ። ከኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ድጋፍ የበለጠ ለውጡ እንዲፋጠን የበኩላቸውን እንቅስቃሴ ማድረጋቸውን ታሪክ ይዘክርላቸዋል።

በተለይ በአሜሪካና አውሮፓ የሚገኙት ፖለቲካዊ እንቅስቃሴያቸው ከፍተኛ ነበር ማለት ይቻላል። በአገር ውስጥ እየተካሄደ በነበረው የኢ-ዴሞክራሲያዊ እንቅስቃሴ፣ ሰብዓዊ መብት ጥሰት በተለያዩ መንገዶች በማጋለጥ ለለውጡ አጋር መሆናቸውን አሳዩ። ይህም ከወቅቱ መንግስት ጋር የነበራቸው ግንኙነት በግልጽ እየተበላሸ እንዲመጣ አደረገው። እነርሱ በአገራቸው ጉዳይ ላይ ፖለቲካዊ፣ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተሳትፎ የማድረግ ፍላጎታቸውን በተግባር እያጠናከሩ የመጡበትም ወቅት ነበር።

በ2010 ዓ.ም ለውጥ ከመጣ በኋላም በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያንና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን አገራዊ ተሳትፎ ጎለበተ። በተለይ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐብይ አህመድ በአሜሪካና በአውሮፓ አገሮች “በፍቅር እንደመር፤ በይቅርታ እንሻገር፤ ግንቡን እናፍርስ፤ ድልድዩን እንገንባ” በሚል መርህ ባደረጉት ጉዞና በውጭ ከሚኖሩት ኢትዮጵያዊያንና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን ጋር በተፈጠረው ቅርርብ የተገኘው ውጤት ለአገራዊ የጋራ መግባባት መልካም አጋጣሚ መፍጠሩ እሙን ነው።

በተለይም ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ “ዳያስፖራ ሰላምን፣ እውቀትን፣ ጥበብን ያስተምር። መለያየት አሳፋሪ እንደሆነ ይናገር። አንድ ሆኖ አንድነት ያስተምር” በማለት ያስተላለፉት መልዕክት አገራቸው የእነሱን አንድነትና ጥበብ እንደምትፈልግ በግልጽ ያሳየ ነበር።

በ2011 ዓ.ም የኢትዮጵያ ዳያስፖራ ኤጀንሲ ከተቋቋመ በኋላ “እኔ ለአገሬ፤ አገሬም ለእኔ” በሚል መርህ አገራዊ ተሳትፋቸው እያደገ መጥቷል። በአቅም ግንባታ ተግባራት፣ በንግድና ቱሪዝም፣ የአገር መልካም ገጽታ በመገንባት በኩል የበኩላቸውን ድርሻ እየተወጡ ይገኛሉ።

ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጠነከረ የመጣው ተሳትፎ ኢትዮጵያ በተለያየ መልኩ ለሚያጋጥማት ችግር የራሱ መፍትሔና ድጋፍ እየሰጠ ይገኛል። በቅርቡ እንኳን የአሸባሪው ህወሓት ወረራን ተከትሎ በአገራችን ላይ የተከሰቱትን ችግሮች ለመፍታትና ከአገራቸው ጎን በመቆም ዋነኛ ተዋናይ ሆነዋል። ገንዘብ በማዋጣት፣ የውጭ ምንዛሪ በመላክ፣ የኢትዮጵያን እውነታ ለዓለም ሕዝብ በማሳወቅ ከፍተኛ ጥረት ሲያደርጉ ቆይተዋል። እያደረጉም ነው።

በተለይም በኢትዮጵያ ላይ እየተደረገ ያለውን ያልተገባ የውጭ ጣልቃ ገብነት በመቃወም የ”#በቃ” ዘመቻን በማካሄድና እውነታን በመግለጥ ከአገራቸው ጎን መሆናቸውን አሳይተዋል። የዘመቻው አካል የሆኑ ሰልፎች በ40 የተለያዩ ዓለም ከተሞችም አካሂደዋል። አንዳንድ የውጭ አገሮች ኢትዮጵያ ሰላም እንዳልሆነች በማስመሰል ዜጎቻቸውን ከአገራችን ለማስወጣት ተደጋጋሚ ጥሪ ሲያቀርቡ ስህተት መሆኑን በተጨባጭ አሳይተዋል። ለዚህ ደግሞ በውጭ ለሚኖሩ ኢትዮጵያዊያንና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን አገራቸው ላደረገችው ጥሪ የሰጡት ፈጣንና መልካም ምላሽ ተጠቃሽ ነው። ጥሪውን ተቀብለው ወደ አገራቸው መጥተዋል። የእነርሱ ወደ አገር ቤት መምጣት ትርጉሙ ዘርፈ ብዙ መሆኑ ሳይታለም የተፈታ ነው።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ አህመድ በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያንና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን ወደ አገራቸው መምጣታቸውን ተከትሎ “በመላው ዓለም የሚገኙ ኢትዮጵያዊያን ዳያስፖራዎች አገራችን ሰው በፈለገችበት ጊዜ ለአገራቸው የቁርጥ ቀን ልጆች መሆናቸውን አስመስክረዋል ብለን በድፍረት መናገር እንችላለን። አንዳንዶች ኢትዮጵያን ለመድፈር በተነሡ ጊዜ፣ ሌሎች የኢትዮጵያን እውነት በውሸት ለመሸፈን በተነሡ ጊዜ፣ የቀሩትም በኢትዮጵያ ላይ ተገቢ ያልሆነ ጫና ለማሳደር በተነሡ ጊዜ፣ ዳያስፖራ ወገኖቻችን ለኢትዮጵያ ሲሉ በአንድነት ቆመዋል። የፖለቲከኞችን በሮች አንኳኩተዋል።



10

አደባባዮችን በሰልፍ አጥለቅልቀዋል፤ ታላላቅ ተቋማትን ሞግተዋል፤ የመሪዎችን የተሳሳተ ፖሊሲ ተጋፍጠዋል፤ ሚዲያዎች የኢትዮጵያን እውነት እንዲያንጸባርቁ ጫና ፈጥረዋል።” በማለት የተናገሩት ሀሳብ በውጭ የሚኖሩት ኢትዮጵያዊያንና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን በአገራቸው ጉዳይ ላይ የያዙትን ቁርጥ አቋም የሚያሳይ ነው።

አገራቸው ከገቡም በኋላ ያሳዩት እንቅስቃሴና ለወገኖቻቸው ያበረከቱት አስተዋጽኦ ሲታይ ለተወሰነ ጊዜ ሻክሮ የቆየው ግንኙነት በመልካም እየተጠናከረ መምጣቱን ያመላክታል።

የኢትዮጵያ ዳያስፖራ ኤጀንሲ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ዶክተር መሀመድ እንድሪስ “ከታላቁ ጉዞ ወደ አገር ቤት ጥሪ ጋር ተያይዞ አዲስ ዓይነት የዳያስፖራ ተሳትፎ መስመርና መነሳሳት በሁሉም ባለድርሻ አካላት ተፈጥሯል” ያሉት ሀሳብ የተፈጠረው መልካም ግንኙነት ወደ ላቀ ደረጃ መሻገር የሚችልበትን አቅጣጫ አመላካች ነው።

አገራቸው ያደረገችላቸውን ጥሪ ተቀብለው ከመጡ በኋላም በተለያዩ አካባቢዎች በመዘዋወር አጋርነታቸውን አሳይተዋል። በተለይ አሸባሪው ህወሓት በአማራና አፋር ክልሎች በወረራ ይዟቸው በቆዩ አካባቢዎች ያደረሰውን ጥፋት ተመልክተዋል። የኢ-ሰብዓዊነትን ጥግ፣ የንጹሐን ጭፍጨፋ፣ በመንግሥትና በግል ተቋማት ላይ የደረሰውን ውድመት በመመልከት ስሜታቸውን አጋርተዋል። ሀዘናቸውን ገልጸዋል። ድጋፋቸውን ሰጥተዋል።

ለእናት አገራቸው ከመቼውም ጊዜ በላይ ያላቸውን አለኝታነታቸውን በተግባር ለማሳየት ዝግጁነታቸውን

አንጸባርቀዋል። እሰከ ዛሬ ድረስ በሽብር ቡድኑ ወረራ ጉዳት ለደረሰባቸው አካባቢዎች የሚገኙ ዜጎችን በመጎብኘት እና አስፈላጊ የሆኑ የምግብ፣ የአልባሳት፣ የመድኃኒት የመሳሰሉ ግብዓቶችን በማቅረብ ድጋፋቸውን እያደረጉም ይገኛሉ።

ከጣልያን አገር የመጡ ወይዘሮ ሂሩት ኃይሉ እና ዶክተር በየነ በእጅጉ የሚያረጋግጡት ሀሳብም ይሄንኑ ነው። በኢትዮጵያ በተለይም በጦርነት በተጎዱት አካባቢዎች አረጋዊያን፣ ሴቶች እና ሕፃናት የወገኖቻቸውን ድጋፍ አጥብቀው የሚሹበት ሁኔታ ላይ እንደሚገኙ አስተውለዋል።

“እነዚህን ጉዳት የደረሰባቸውን የሕብረተሰብ ክፍሎች መልሶ ማቋቋም እና የሞራል እገዛ ማድረግ ከሁሉም ዜጋ የሚጠበቅ ኃላፊነት ነው” በማለት ይገልጻሉ።

እነርሱ በጦርነቱ የተጎዱ አካባቢዎችን መልሶ ለመገንባት በሚደረገው ጥረት ላይ የበኩላቸውን ድጋፍ ለማድረግ ዝግጁ ናቸው። ከዚህ አኳያ የተጎዱ ዜጎችን በሁለንተናዊ መልኩ ለማገዝ የሚያስችሉ ፕሮጀክቶችን ለመተግበርም እንቅስቃሴ ተጀምሯል። ለዓመታት በኖሩበት አገር ያገኙትን ልምድና ክህሎት በመቀመር ለአገር እድገትና የሕዝብ ተጠቃሚነት ለመስራትም ዝግጁ ናቸው።

ከእነዚህ በተጨማሪ በኢትዮጵያ ልማትና እድገት ላይ ለመሳተፍ የእውቀት፣ የሳይንስና ቴክኖሎጂ ሽግግር ለማድረግ በመንፈስም በአካልም መዘጋጀታቸውን ነው በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያንና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን የሚያረጋግጡት።

በጀርመን አገር ነዋሪ ወጣት ዳዊት ስብሃቱ እና ወይዘሮ

ሊያ መላኩ “ኢትዮጵያዊያን በሙያችንም ሆነ በገንዘባችን ለማገዝ እንዲሁም ዘላቂነት ያለው የዲፕሎማሲ ስራዎችን ለማከናወን ዝግጁ ነን” ማለታቸው ከላይ የተጠቀሰውን ነጥብ ያጠናክረዋል።

እስከአሁን ባለው ተጨባጭ ሁኔታ ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ የመጣው ግንኙነትና ለአገራቸው ትኩረት መስጠት ጉዳይ በውጭ የሚኖሩት ዜጎች ኢትዮጵያን በመደገፍ ረገድ አበረታች ተሳትፎ እያደረጉ ናቸው። በአገሩ ጉዳይ ላይ ተቀራርቦ መስራት እየተጠናከረ መጥቷል። ባለፉት ረጅም ዓመታት በጣም በዘገምተኝነት ሲጓዝ የቆየው ግንኙነት እየተፋጠነና እየጠነከረ መምጣቱ በግልጽ ታይቷል። በአገር ኢኮኖሚ ተሳትፎው፣ በጉዳቷ ወቅት ቀድሞ መገኘቱ ታላቅ ማሳያ አድርጎ መውሰድ ይቻላል።

“ለታላቁ የሕዳሴ ግድባችን ጥብቅና ከመቆም ባሻገር ገንዘባቸውን በመላክ የግድቡ ሥራ እንዲፋጠን አስችለዋል። ለተጎዱ ወገኖቻችን በየጊዜው የዓይነትና የገንዘብ ድጋፍ አድርገዋል። የኢትዮጵያ የውጭ ምንዛሪ ባልተገባ ጫና በተፈተነ ጊዜ ከሚበሉት ቀንሰው ለአገራቸው ለግሰዋል። አገራቸው የህልውና ፈተና ሲገጥማት በቻሉት ሁሉ ግንባር ቀደም ሆነው ተሰልፈዋል። በማኅበራዊ ሚዲያ የሚገጥመንን ፈተና ለመመከት ጊዜያቸውንና ዕውቀታቸውን ሠዉተዋል” በማለት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ የገለጹት የተነሳውን ሀሳብ ያጸናል።

የኖርዌይ የዳያስፖራ አስተባባሪዎች ቴዎድሮስ ማህተቤ እና የኢትዮጵያን ግሎባል ውሜን አልያንስ መስራችና ፕሬዚዳንት ወይዘሮ ኢትዮጵያ አለማየሁ እንደሚናገሩት፤ በቅርቡ በአሸባሪው ህወሓት ግድያ ወላጆቻቸውን



11

ያጡ ሕፃናትን ለማሳደግና በቡድኑ ፆታዊ ጥቃት የተፈፀመባቸውን ሴቶች በዘላቂነት ለማገዝ የተቋቋመው ኮሚቴ ስራ ጀምሯል። ለሕፃናቱ የስነ-ልቦና ክትትል ማድረግ ያስፈልጋል። በተጨማሪም “የማሳደግና የመንከባከብ ኃላፊነት የሁላችንም ሊሆን ይገባል” ብለዋል።

በደቡብ አፍሪካ ጆሃንስበርግ የሚኖሩት ፓስተር ወርቅነህ ዘርፉ እና ወይዘሮ እልፍነሽ ኃይሌ “ወቅቱ አገሪቷ ከመቼውም ጊዜ በላይ የሕዝቦቿን ድጋፍና ርብርብ የምትሻበት፣ ዳያስፖራውም በእውቀትና ቴክኖሎጂ ሽግግር ሙያዊ እገዛ በማድረግ አለኝታነቱን በተግባር የሚያሳይበት ነው” በማለት የሌሎቹን ሀሳብ አጥብቀው መጋራታቸውን አሳይተዋል።

በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያንና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን አገር ወዳድነታቸውን በተግባር የሚያሳዩበት ወቅት ላይ መሆናቸውን ተረድተውታል። የአገራቸውን ጥሪ በተግባር የመመለስ ስራ ላይም ተሰልፈዋል። ለዚህም ነው የተጎዱ ዜጎችን ከመደገፍ ባለፈ በጥቃቱ የወደሙ የሕዝብ መገልገያ ተቋማትና መሰረተ ልማቶችን መልሶ በማቋቋም ተሳትፎውን ለማጎልበት ቆርጦ የተነሳው።

በተለያዩ “የልማት መስኮች ኢንቨስት በማድረግና የቴክኖሎጂ እውቀታችንን በማጋራት በኢትዮጵያ እድገት ላይ አሻራችንን ለማኖር ተዘጋጅተናል” ያሉት አገራዊ ሁኔታው ተስፋ ሰጪ መሆኑን በማረጋገጥ ነው። በተለያዩ የኢንቨስትመንት መስኮች መሰማራት፣ የውጭ ኢንቨስትመንትን መሳብ፣ የቱሪዝም መስህቦችን እና ምርቶችን በማስተዋወቅ የድርሻችንን እንወጣለን በማለትም ነው ቃል የገቡት። ለአገር እና ለወገን በሚጠቅም ዘርፍ ላይ በመሰማራት ለኢኮኖሚ ልማት አስተዋፅኦ ለማድረግ የመዘጋጀት ምስጢራቸውም ይሄው ነው።

“በኢትዮጵያ ያለው ወቅታዊ ሁኔታ ዳያስፖራውን በአገሩ ጉዳይ አንድ እንዲሆን አድርጎታል፤ ልቡና ቀልቡ ኢትዮጵያ ላይ ብቻ ሆኗል” በማለት በአውስትራሊያ ሜልቦርን ነዋሪ አቶ ተክሌ ላምቦሮ የገለጹት የብዙዎችን አመለካከት ያንጸባርቃል። በውስጥም በውጭም ያሉ በመተባበርና በመደጋገፍ አገሪቷን ማጠናከር የግድ የሚል ነው።

የቀድሞው የእስራኤል ፓርላማ (ክኔሴት) አባል ሽሎሞ ሞላ “ኢትዮጵያ በዘላቂነት የኢኮኖሚ እድገቷን ማረጋገጥ የምትችልበት የውሃ፣መሬትና ሌሎች የተፈጥሮ ሀብቶች አሏት። ይህን አቅም ለመጠቀም የሚያስችል ቴክኖሎጂዎች አስፈላጊ ናቸው” ይላሉ። ይህም ኢትዮጵያ ከውጭ የሚኖሩ ልጆቿ ተባብረው እድገቷን ለማምጣት የሚያስችል ስራ ማከናወን እንዳለባቸው ያሳያል። አንድም በራሳቸው ሀብት፣ እውቀትና ጉልበት፤ አንድም ለአገራቸው ዲፕሎማት የመሆን ስራን በማከናወን የተሻለችውን ኢትዮጵያ መገንባት ያስፈልጋል።

ለዚህም ነው የቀድሞው የእስራኤል ፓርላማ (ክኔሴት) አባል ሽሎሞ፤ በእስራኤል የሚገኙ ኢትዮጵያዊያንና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን አገራቸው በቴክኖሎጂ በመታገዝ የተፈጥሮ ሃብቷን መጠቀም እንድትችል ፕሮጀክቶች መንደፉቸውን ያመለከቱት። በተለይ የእርሻ ቴክኖሎጂ ድጋፍ ለኢትዮጵያ የግብርና ዘርፍ እድገት ወሳኝ ሚና እንደሚኖረውና በዚህ ረገድ “የእስራኤል ተመክሮን እንደ ማሳያ ይወሰዳል” በማለት ነው የሚገልጹት።

“ኢትዮጵያ አሁን ካለችበት ወቅታዊ ችግር በፍጥነት እንድትሸጋገር በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያንና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን ሚናቸው እና ተሳትፏቸው መጠናከር አለበት” በማለት በደቡብ አፍሪካ ፕሪቶሪያ ሱዋኔ ዩኒቨርሲቲ የኢኮኖሚክስ መምህር ፕሮፌሰር ሙላቱ ፍቃዱ የተናገሩት ሀሳብ ጉዳዮ በውስጥም በውጭም ያለው ተቀናጅቶ መስራት እንደሚጠበቅበት ያረጋግጣል።

እነዚህ ሀሳቦችን ስንመለከት ነው “ኢትዮጵያ በልጆቿ ጥረት ሕዳሴዋ እውን ይሆናል” የሚለውን እምነት

የምንይዘው። እውቀትና ቴክኖሎጂ ብቻ ሳይሆን ከውጭ የሚላክ ሀዋላ /ሬሚታንስ/ የአገሪቷን ኢኮኖሚ ለመደገፍ ጉልህ ሚና እንዳለውም የታወቀ ነው። ይህን ደግሞ ማንኛውም ወገን የሚስተው አይደለም።

እዚህ ላይ ፕሮፌሰር ሙላቱ የሚያነሱትን ሀሳብ መጥቀስ ይገባል። እርሳቸው እንደሚሉት በእስያ የሚገኙ አገሮች ከአጠቃላይ ምርታቸው ከግማሽ በላይ የሚሆነውን ከውጭ አገር በሚገባ ገንዘብ ያገኛሉ። በመሆኑም ከውጭ የሚላክ ገንዘብ ለኢትዮጵያም እንደ ተጨማሪ የሀብት ማሰባሰቢያ ተደርጎ መወሰድ አለበት፤ መንግሥትም ትኩረት ሰጥቶ ሊሰራበት ይገባል።

“በተለይም ዳያስፖራው ገንዘቡን ያለምንም ችግርና ቅድመ ሁኔታ ወደ አገር ቤት እንዲልክ ለማድረግ ቀልጣፋ የገንዘብ ፍሰት መኖር አለበት” ብለዋል።

ባለፉት ሶስት ዓመታት በአማካይ ሦስት ቢሊዮን ዶላር በየዓመቱ ወደ አገር ውስጥ መላኩን ከኢትዮጵያ ዳያስፖራ ኤጀንሲ የተገኘው መረጃ ያመላክታል።

ኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ጫናውን ለመመከት በአገር ውስጥ የማምረት አቅሟን ማሳደግና ዓለም ዓቀፍ የገበያ አማራጮቿን ማስፋት ይጠበቅባታል። ኢትዮጵያ በዓለም ገበያ ልታቀርባቸው የምትችለው እና ያልተጠቀመችባቸው የግብርና እና ኢንዱስትሪ ውጤቶች አሏት። በዚህም ወደ ውጭ የሚላኩ ምርቶችን በማሳደግ በአውሮፓ፣ በእስያ እና በአፍሪካ አገሮች ያሉ የገበያ አማራጮችን ማስፋት ይገባል። የግብርና መር ኢኮኖሚውን ወደ ኢንዱስትሪ መር ኢኮኖሚ ለማሸጋገር የሚያስችሉ ስራዎችን በተጠናከረ ሁኔታ መስራትም አስፈላጊ ነው።

“የአገሪቷ ምርቶችና የፋብሪካ ውጤቶች የጥራት ደረጃቸውን የጠበቁ እንዲሆኑና በዓለም ገበያ ተወዳዳሪ ሆነው እንዲወጡ ማድረግ ይገባልም” ብለዋል። በሌላ በኩል የአገሪቷን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማጎልበት በቀጣናው ከሚገኙ ጎረቤት አገሮች ጋር ሁለንተናዊ ትስስር ማጠናከር ይጠበቃል።

በማንኛውም የልማትና የእድገት እንቅስቃሴዎች ከአፍሪካ በተለይም ከጎረቤት አገሮች ጋር ያለውን ትብብር ማጠናከር ያስፈልጋል። በጤናው፣ በትምህርት፣ በኢንዱስትሪና በሌሎች የተለያዩ ጉዳዮች ላይ በማሳተፍ የልማት እንቅስቃሴዎችን ማፋጠን ይቻላል። መንግሥት ልማትና ሌሎች እንቅስቃሴዎችን ለመደገፍ የሚያወጣቸውን ወጪዎች ጥናትን መሰረት ያደረጉና ወጪ ቆጣቢ ሊሆኑም እንደሚገባ ይገልጻሉ - ፕሮፌሰር ሙላቱ።

የኢኮኖሚ አስተዳደር ሥርዓቱን በመፈተሽና የተሻለ የፖሊሲ አማራጭ በመከተል ጫናውን መቋቋም ይገባልም። ፖሊሲዎችን፣ ሕጎችን፣ መመሪያዎችን እና አጠቃላይ የአሰራር ሂደቶችን ካለው ወቅታዊ ሁኔታ አኳያ መቃኘት ያስፈልጋል።

በመላው ዓለም የሚገኙ

ኢትዮጵያዊያን ዳያስፖራዎች

አገራችን ሰው በፈለገችበት ጊዜ

ለአገራቸው የቁርጥ ቀን ልጆች

መሆናቸውን አስመስክረዋል

ብለን በድፍረት መናገር

እንችላለን። ”

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ አህመድ

““



12

ኢትዮጵያ የጥቁሮች - የነፃነት ቀንዲል

ማህበራዊ



13

መንደርደሪያ እንደ አውሮፓዊያን አቆጣጠር በ1885 በጀርመን ከተማ በርሊን የአውሮፓ አገሮች አፍሪካን ለመቀራመት ያደረጉት ሥምምነት የአፍሪካን የአሁኑን የኢኮኖሚ ቁመና፣ ማኅበራዊ ውቅርና ፖለቲካዊ ምስቅልቅሎሽ ሥረ-መሠረት ነው ብሎ መደምደም ይቻላል።

“ጉልበት ሁሉን ማድረግ ይችላል” በሚል አስተሳሰብ የተመራው ጉባዔ የምዕራባዊያኑን ፍላጎት አቅም በሌላቸው አፍሪካዊያን ላይ ይጫን ዘንድ ምክንያት ሆኗል። ይህንን ተከትሎ የወቅቱ ኃያላን አገሮች የአፍሪካን ካርታ ጠረጴዛቸው ላይ አስቀምጠው እንደየፍላጎታቸው ቅኝ ለመግዛት የሚፈልጉትን አገር በጣታቸው በመጠቆም መርጠዋል፤ ኃይላቸውን ሊያረጋግጥ የሚችለውን ጦር በማዝመት አህጉሪቷን ተቆጣጥረዋል።

ቀድሞውኑ ከ16ኛው እስከ 19ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ድረስ በአህጉሪቷ የገነነው የአትላንቲክ የባሪያ ንግድም ድፍን የአፍሪካ ሕዝቦች ለዳግም ግዞት እንዲዘጋጁ ትልቅ መደላድል ፈጥሯል። ከአትላንቲክ ማዶ የምትገኘውን አሜሪካ እንዲያቀኑ አያሌ ጥቁሮች ተግዘው ወዛቸውን ሲገብሩ ቆይተዋል። ይህም ለኋለኛው የቤት ባርነት አብቅቷቸዋል። ይህንን ተመርኩዘው አፍሪካዊያንን በብረት መዳፍ ለመግዛት ወደ አህጉሪቷ የመጡት ከአልፕስ ተራራ ጀርባ ያሉት ነጮች ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ በለስ ቀንቷቸዋል። በበርሊኑ ጉባኤ መሠረትም ኢትዮጵያን ለመቆጣጠር

በበረከት ሲሳይ

ኢትዮጵያ የጥቁሮች - የነፃነት ቀንዲል



14

ያቀናችው ጣሊያን እንደ ሌሎቹ አውሮፓዊያን አገሮች ተልዕኮው ቀላል አልሆነላትም፤ ገና ሳትጀምረው ውድቀቷ ታወጀ።

ጣሊያንን የገጠሟት ነፃነታቸውን አሳልፈው የማይሰጡ፣ ለሉዓላዊነታቸውና ለግዛት አንድነታቸውም ደማቸውን የሚያፈሱ፣ አጥንታቸውን የሚከሰክሱ ሕዝቦች ናቸው። እነዚህን ሕዝቦች ለማንበርከክና ለማስገበር የተለያዩ ዲፕሎማሲያዊ ስልቶችን ለመጠቀም በበርካታ መንገዶች ጥራለች። ነገር ግን ጣሊያን ፍርቱና ሊቀናት አልቻለም። የኋላ ኋላ በዳግማዊ ዓፄ ምኒልክ የተመራው ጦር በጄነራል ኦሬስቴ ባራቴሪ ፊታውራሪነት ኢትዮጵያን በኃይል ለመውረር ከመጣው የጣሊያን ጦር ጋር አድዋ ላይ ገጠመ። ታሪክ እንደሚዘክረው ግማሽ ቀን ባልሞላው የጦር ሜዳ ውሎ የጣሊያን ኢትዮጵያን የማንበርከክና በቅኝ ግዛት ድቅድቅ ጨለማ ውስጥ የመክተት ቀቢጸ ተስፋ በኢትዮጵያዊያን የተባበረ ክንድ መከነ።

በጥቁር ሕዝቦች ተጋድሎ የተገኘውን ድል፤ የጣሊያን ደጋፊ የነበረው እንግሊዛዊ ጸሐፊ ጆርጅ ባርክሌይም “ጨለማው አህጉር ለመጀመሪያ ጊዜ ኃያላን በሆነው አውሮፓ ላይ ያደረገው አመጽ” (the first revolt of dark continent against domineering Europe) በማለት ገለጸው። ይህ ገለፃው ለአፍሪካዊያን ያለውን ጨለምተኛ አመለካከት የሚያሳብቅ ነው። ራሳቸውን ኃያላን አድርገው በመቁጠር በየትኛውም አካባቢ በማንኛውም ሁኔታ ጥቁሮችን ማንበርከክ የሚችሉ አድርጎ የሚመለከትበት የእምነት መሰረቱ መናጋቱን ያሳያል። ኢትዮጵያም ለዘመናት ይዛ የቆየችውን ነፃነቷን በልጆቿ መስዋዕትነት አስከበረች። ይህን በተመለከተ በዋሺንግተን ዩኒቨርሲቲ የታሪክ ፕሮፌሰሩ ራይሞንድ ጆናስ “The Battle of Adwa, African Victory in the Age of Empire” በሚለው መጽሐፉ “አድዋ የሚያስታውሰን ነገር ቢኖር እውነተኛ ነፃነትን ተከላክለን የምንጠብቀው ብቻ መሆኑን ነው፤ ይህም ኢትዮጵያ ባደረገችው በጽናት የመከላከል (የመቃወም) ደረጃ ነው የተሳካው” በማለት ገልጾታል። ፕሮፌሰሩ ኢትዮጵያዊያን ነፃነታቸውን ለማስከበር አስፈላጊውን ሁሉ መስዋዕትነት የሚከፍሉ ጠንካራ ሕዝቦች መሆናቸው በእጅጉ አስደንቆታል። ይህም ለዛሬይቱ ኢትዮጵያ ጽኑ መሰረት ነው። ኢትዮጵያዊያን በአድዋ ያስገኙት ድልም ለራሳቸው ብቻ ሳይሆን ለመላው ጥቁር ሕዝብ የነፃነት ቀንዲል መሆኑንም መስክሯል። የአድዋ ድል ለኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን ለአፍሪካ እና በየቦታው የሚከሰቱ ተግዳሮቶችን ለማስቆም ለቆረጡ ሕዝቦች ጭምር መሆኑን በመግለጽ አድናቆቱን ከመቸር አልተቆጠበም።

ኢትዮጵያ ለመጀመሪያ ጊዜ ጥቁር በነጭ ላይ የተቀዳጀው ድል ባለቤት መሆኗ በዘመኑ የነበረውን መሰረታዊ ዓለም አቀፍ አረዳድ የነቀነቀነ ታላቅ ታሪካዊ ክስተት ነበር። በተለይም ጥቁር ነጭን እንደሚያሸንፍና የራሱንም ታሪክ በራሱ መጻፍ እንደሚችል በማሳየት፣ በተግባርም

በማስመስከር ታላቅ መልዕክት አስተላልፏል። በግርድፉም፤ የአድዋ ድል ከሄሮደተስ እስከ ዳርዊን ያሉት በርካታ ዘመን ተሻጋሪ ጸሐፊዎች “ጥቁር ሕዝቦች ነጭ ያለውን ዓይነት የአእምሮ ልዕቀት መያዝ አይችሉም” በሚል አመለካከታቸውን ለማስረጽ በብዙ የወተወቱትን የሐሰት ትርክት አምክኖባቸዋል። በአንፃሩም አድዋ በትክክለኛ አመራር፣ ሃብትን በማሰባሰብና አንድነትን በመፍጠር አፍሪካዊያን ከተንቀሳቀሱ የአገራቸውን ጥቅም ማስከበር እንደሚችሉ አረጋግጧል። የነፃነት ቀንዲል አብርቷል።

“ኢትዮጵያኒዝምና ፓን አፍሪካኒዝም”

የአድዋ ድል ለአውሮፓዊያን በዘመናት ውስጥ የማይሻር ግልጽ መልዕክት አስተላልፏል። አፍሪካዊያን የእነርሱን ኃያልነት በመጋፈጥና በመታገል ማሸነፍ እንደሚችሉ ትምህርት መስጠቱን በርካታ የታሪክ ድርሳናት አብዝተው ይመሰክራሉ። በተለይም ደግሞ በጣሊያን ላይ በደረሰው የጥቁር ሕዝቦች ክንድ በአድዋ ላይ ሽንፈትን የተከናነበው የወቅቱ የአገሪቷ ጠቅላይ ሚኒስትር ፍራንሴስኮ ክሪስፒና

ካቢኔያቸው ከሥልጣን መውረዳቸው በመላው አውሮፓ የኢትዮጵያ ኃያልነት እንዲናኝ በር ከፍቷል።

በሌላ በኩል ደግሞ በተለያዩ የዓለም አገሮች ለሚገኙ ጥቁር ሕዝቦች ካሉበት የተለያዩ የግዞት ዓይነቶች ከቅኝ ግዛትም፣ ከባርነትና ከሌሎችም ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ብዝበዛ ነፃ መውጣት እንደሚችሉ ቀጥተኛ መልዕክት አስተላልፏል። የአድዋ ድል ኢትዮጵያን በተለይም በግዞት ለነበረው ለመላው አፍሪካ የሥነ- ልቦና መነቃቃት ከመፍጠሩም በላይ የነፃነት ቀንዲል ሆና እንድትቀጥል ያስቻለ ክስተት ነበር። የአድዋን ድል ተከትሎ በመላው ጥቁር ሕዝቦች ዘንድ የናኘው የኢትዮጵያ የአሸናፊነት መንፈስ ወደሌሎች እየተጋባ በመምጣት ወደር አልተገኘለትም።

“ኢትዮጵያ” ማለት የጥቁር ሕዝብን እውነተኛ ማንነት የሚወክል ሆኖ ሲቀርብ ቆይቷል። ይህንን ተከትሎ ኢትዮጵያ “የነፃነት፣ የነፃ አገርና የአርነት ቀንዲል” ሆና በብዙ ጥቁር ነጻነት ናፋቂዎች ዘንድ ተስላ ቆይታለች። ለዚህም ነው ጳውሎስ ሚልኪያስና ጌታቸው መታፈሪያ “The Battle of Adwa” በሚለው መጽሐፋቸው “ኢትዮጵያ የሚለው ስም በጥቅሉ ሁሉንም ጥቁሮች



15

አፍሪካ የሚለውን ይወክላል፤ በዋናነት ግን በጊዜው በቅኝ ያልተገዛች ብቸኛ የአፍሪካ አገር መሆኗን ነው የሚያሳየው። በዚህም ኢትዮጵያ የአውሮፓን ኃይልና ግዞት የምትታገልና ተከላካይ ግንብ ሆና ትመሰላለች” በማለት ያሰፈሩት።

ይህ የመላው ጥቁር ሕዝቦች ተቀጽላ መጠሪያ የሆነው ኢትዮጵያ የሚለው ስም በ18ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ገደማ ተጠንስሷል ከተባለው ፓን አፍሪካኒዝም አስተሳሰብ ጋር ታላቅ ትስስር እንዳለው ነው መረጃዎች የሚያሳዩት።

ፓን አፍሪካኒዝም ጥቁር ሕዝቦች አንድ የጋራ ታሪክ፣ የሕይወት ፍልስፍና፣ የዘር ግንድና ተመሳሳይ የሕይወት ልምድ የተካፈሉ ሕዝቦች መሆናቸውን መሰረት ያደረገ አስተሳሰብ ነው። ይህም በምዕራባዊያኑ የተጠነሰሰው አስተሳሰብ ድንበር ተሻግሮ የሚኖሩ አፍሪካዊያን ያሉባቸውን የቅኝ ግዛት፣ የባሪያ ንግድና የማኅበራዊ ጭቆና ተላቀው የጥቁር ሰዋዊ ክብር መላበስን ግቡ ያደረገ አስተሳሰብ ነው። እዚህ ላይ ነው የአድዋ ድል የፓን አፍሪካኒዝም አስተሳሰብ ለሚያቀነቅኑ አካላት ለንቅናቄያቸው መስፈንጠሪያ ያደረጉት።

ኢትዮጵያ በእውነትም የፓን አፍሪካኒዝም ንቅናቄን

እንዲወለድና እንዲፋፋም ትልቅ ሚና ተጫውታለች። ታዋቂዎቹ አፍሮ አሜሪካኖች ዱ ቦይስ፣ ማርከስ ጋርቬይ፣ ጆርጅ ፓድሞርና የምዕራብ አፍሪካው ካስሌይ ሃይፎርድ የመሰሉ የፓን አፍሪካኒዝም አቀንቃኞች ቀደም ሲል “ኢትዮጵያኒዝም” በጥቁሮች መካከል በፈጠረው የወንድማማችነት አስተሳሰብ አማካኝነት መነሳሳት ፈጥሮላቸዋል። ይህንንም ተከትሎ ነው ዊልሰን ሞሰስ “The Golden Age of Black Nationalism” በሚለው መጽሐፉ “ኢትዮጵያኒዝም አትላንቲክ ውቅያኖስን ተሻጋሪ የፖለቲካ ንቅናቄ ብቻ ሳይሆን ከኮንጎ ሸለቆ እስከ ጃማይካ ተራሮች እንዲሁም እስከ ኒውዮርክ አደባባይ ላይ የሚገኙትን መላውን ጥቁር ሕዝብ ያሰባሰበ ነው” በማለት የገለጸው። በተለይም በካሪቢያን አገሮችና በአሜሪካ በመላው የጥቁር ሕዝቦች መካከል የተፈጠረውን የመነቃቃትና የትግል ሞገድ አንደኛው መንስኤ “ኢትዮጵያኒዝም” መሆኑን ዋልሰን ሞሰስ ያመላከተውን ሀሳብ ማጤን ይቻላል።

ይህ ንቅናቄ እጅጉን እየተጠናከረ መምጣቱ በግልጽ የተስተዋለው ኢትዮጵያ ለዳግም የፋሺስት ጣሊያን ወረራ በተዳረገችበት ወቅት ነበር ማለት ይቻላል። በተለይም በአሜሪካ በአፍሮ አሜሪካኖች ዘንድ የታየው

ቁጭትና ውግንና የሚዘነጋ አይደለም። እንዲያውም ከኢትዮጵያ ጎን ተሰልፈው ፋሺስት ጣሊያንን ለመውጋት ፍቃደኛ የነበሩ በኒው ዮርክ ሄርልም የሚኖሩ የጥቁር ሕዝቦች ማኅበረሰብ በዚህ ረገድ ተጠቃሽ ናቸው። ከዚህ በላይም የአሜሪካ መንግሥት ኢትዮጵያን በተመለከተ የሚከተለውን የውጭ ፖሊሲ እንዲያስተካክል ጭምር ከፍተኛ ግፊት ሲያደርጉ ቆይተዋል። ይህም በአሜሪካ የዘር መድሎ የሚፈጸምባቸው አፍሮ አሜሪካዊያን የሚደርስባቸውን ጭቆና ተገንዝበው ትግል እንዲያካሂዱ “Civil Right Movement” /የጥቁሮች የእኩልነት እንቅስቃሴ/ እንዲጀመር አስችሏል።

በተለይም ደግሞ በቅኝ ግዛት ውስጥ የነበሩት የአፍሪካ አገሮች ከባርነት እንዲወጡም ኢትዮጵያውያን የነፃነት ምልክት አድርጎ የተቋቋመው ፓን አፍሪካኒዝም ትልቅ መሰረት ጥሏል። ጋና የመጀመሪያዋ የአፍሪካ አገር በመሆን ነጻነቷን ከተቀዳጀች በኋላ በምዕራቡ ዓለም ትኩረት ያደረገው የፓን አፍሪካኒዝም እንቅስቃሴ ወደ አፍሪካ አህጉር በማምጣትና የኋላ ኋላም የአፍሪካ አገሮች ነፃነት እውን መሆንን በሂደትም ለአፍሪካ ኅብረት መመስረት ትልቅ ሚና ተጫውቷል።

አፍሪካ ሕብረትና ትሩፋቱ ምንም እንኳን ኢትዮጵያ ለጥቁር ሕዝቦች የነፃነት ትግል መነቃቃትና መስፋፋት የራሷ ድርሻ ቢኖራትም የቀድሞ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ለአሁኑ አፍሪካ ኅብረት መቋቋም የሌሎች የአፍሪካ አገሮች ሚና የሚዘነጋ አይደለም። ኢትዮጵያ ከሌሎች ሰባት ነፃ የአፍሪካ አገሮች ጋር በመሆን እንደ አውሮፓዊያኑ አቆጣጠር በ1958 በጋና መዲና አክራ የመጀመሪያውን የፓን አፍሪካኒዝም ስብሰባ አካሂዳለች። ከዚህ በኋላም ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ የቀድሞ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት የአሁኑ የአፍሪካ ኅብረት ለመቋቋም የሚያስችለውን የ32 አገሮች ስብሰባ በአዲስ አበባ እንደ አውሮፓዊያን አቆጣጠር በ1963 እንዲካሄድ አደረጉ።

ስብሰባው በተለይም “የአፍሪካ ውህደት እንዴት ይከናወን” በሚለው ላይ ልዩነት የነበረውን የሞኖሮቪያና የካዛብላንካን ጎራ በማቀራረብና ወደ አንድ የጋራ አስተሳሰብ በማምጣት በታሪክ ታላቅ ሥፍራ የተሰጠው ነው። የአፍሪካ አንድነት ድርጅት መቋቋምም ቀደም ሲል በነ ሄነሪ ሲልቬስተር ዊሊያም “ፓን አፍሪካኒዝም” እየተባለ የተቀነቀነውን፣ በነ ማርክሰ ጋርቬይ “አፍሪካ ለአፍሪካዊያን” እንዲሁም በዱ ቦይስ “የመላው አፍሪካ ነፃነት” በማለት የተቀጣጠለው የመላው የጥቁሮች ሕዝብ ራዕይ እውን እንዲሆን አስችሏል።

የአፍሪካ አንድነት ድርጅት መቋቋም በቀዳሚነት አፍሪካዊ ወንድማማችነት እንዲጠናከርና እንዲጎለብት አስችሏል። በተለይም በወቅቱ አንገብጋቢ ጉዳይ የነበረው ቀሪዎቹ የአፍሪካ አገሮች ከቅኝ ግዛት እንዲላቀቁ የአንበሳውን ድርሻ ተጫውቷል።



16

ድርጅቱ በተመሰረተበት ዓመት አፍሪካን ነፃ የሚያወጣ ኮሚቴ ተቋቁሞ ወደ ሥራ የገባ ሲሆን፤ በተለይም በቅኝ ግዛት ወስጥ ለነበሩ የአፍሪካ አገሮች ትግላቸውን እንዲያቀጣጥሉ የሞራልና የመሳሪያ ድጋፍ ሲያደርግ ቆይቷል። በዓለም አቀፍ ደረጃም ቅኝ ግዛት ኢ-ሰብዓዊ ድርጊት በመሆኑ ከአፍሪካዊያን ጫንቃ ላይ እንዲነሳ ዲፕሎማሲያዊ ጥረቶችን አካሂዷል። ይህም የኋላ ኋላ አፍሪካዊያን ነፃነታቸውን እንዲቀዳጁና ቅኝ ግዛትን እንዲያስወግዱ መንገድ ከፍቷል።

ድርጅቱ አፍሪካዊያን ነፃነታቸውን መቀዳጀታቸውን ተከትሎ በኢኮኖሚው መስክም የእርስ በእርስ ትብብርና መደጋገፍ እንዲኖር ለማስቻል አከባቢያዊ የኢኮኖሚ ማኅበረሰብ እንዲመሰረት አድርጓል። ይህም የእርስ በእርስ ንግድ እንዲስፋፋ፣ ኢንቨስትመንት እንዲሳለጥና የጋራ ገበያ እንዲፈጠር አሁን ላይ አገሮች ለሚያደርጉት ጥረት ትልቅ መሰረት የጣለ ክሰተት ነው።

ያም ሆነ ይህ የቀድሞ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት የአሁኑ የአፍሪካ ኅብረት ፖለቲካዊ ትልም ሩቅ መንገድ ቢቀረውም እስከአሁን ከሞላ ጎደል አሳክቷል ማለት ይቻላል። አፍሪካዊያን በጋራ ፖለቲካዊ አጀንዳዎች ላይ የጋራ ሥምምነትና ተልዕኮዎች እንዲኖራቸውና ለስኬቱም በጋራ እንዲሮጡ በር ከፍቷል። የአፍሪካ አገሮች ምንም እንኳን በተለያዩ ፖለቲካዊ ችግሮች እየተፈተኑ ቢሆንም ሕብረቱ አሁንም ቢሆን ቁልፍ መፍትሔዎች ከማስቀመጥ አልቦዘነም።

በተለይ በአፍሪካ ዘላቂ ሰላምና ደኅንነት እንዲኖርና የዜጎች ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች የተከበሩባት አህጉር ለመፍጠር አቅዶ እየተንቀሳቀሰ ነው። ይህም ሕብረቱ በተደጋጋሚ እንደሚገልጸው አፍሪካዊ ችግር አፍሪካዊ መፍትሔ የሚለውን ራዕይ እውን ከማድረግ አኳያም ትልቅ እርምጃ ነው። በሌላ በኩል በኢኮኖሚ መስክ በአፍሪካ አገሮች መካከል የኢኮኖሚ ትስስር እንዲፈጠርና በአህጉሪቷ የእርስ በእርስ ንግድና ኢንቨስትመንት እንዲጠናከር አበርክቶው ላቅ ያለ ነው። አሁን ላይ አፍሪካ ይህንን እቅዷን የሚደግፉ የተለያዩ የኢኮኖሚ አጀንዳዎች ያሏት ሲሆን፤ ይህንንም እውን በማድረግ የበለጸገች አፍሪካ ለመፍጠር እየተጋች ነው። ለዚህም ደግሞ የአፍሪካ ሕብረት መቋቋም ትልቅ እገዛ እያደረገ ይገኛል።

ዘመናዊ የቅኝ ግዛት አስተሳሰብና ፍላጎት

በርካታ የአፍሪካ አገሮች ከቅኝ ግዛት መውጣታቸውን ተከትሎ ለዘመናት የተነፈጉትን ነፃነት ቢያጸኑም የምዕራባዊያኑ የቅኝ ግዛት ፍላጎት ግን ከቶውንም ሊያበቃ አለመቻሉ ግርምትን የሚጭር ነው። በተለይም በቅኝ ግዛት ሥር የነበሩ አፍሪካዊያን በቀድሞ ገዥዎቻቸው ጥላ ስር እንዲሆኑ መዋቅራዊ ቅርቃር ውስጥ መግባታቸው የዚህ ችግር ማሳያ ናቸው። ለዚህም ነው የአንዳንድ አፍሪካ አገሮች በተለይም የምዕራብ አፍሪካ አገሮች

የሚስተዋልባቸው ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ፈተናዎች ከቀድሞ ገዥዎቻቸው ጋር የተቆራኘው።

ከዚህ ባለፈ አሁንም ቢሆን የምዕራባዊያኑ ፍላጎት በኢኮኖሚ ገና ያልጠነከረችውንና በፖለቲካም እምብዛም መረጋጋት የማይታይባትን አፍሪካን በእጃቸው ለማስገባት የተለያዩ ጥረቶች በማድረግ ላይ መሆናቸው በግልጽ ይስተዋላል። ይህንን ገቢር ለማድረግ እንደ ከዚህ ቀደሙ ጦር ማዝመት አላስፈለጋቸውም። በአህጉሪቷ ውስጥ ያሉትን ፖለቲካ፣ ኢኮኖሚና ማኅበራዊ ችግሮችን ማባበስ እንደዋነኛ ስልቶች መጠቀማቸውን ተያይዘውታል።

በተለይም በኢኮኖሚ መስክ የአፍሪካ አገሮች ምዕራባዊያን የሚፈልጉትን ዓይነት የኢኮኖሚ ፖሊሲ በመቅረጽ የነፃ ገበያ ስርዓትንና ‘የኒዮ ሊበራል’ አስተሳሰብ እንዲከተል፣ ገበያ መር ኢኮኖሚ እንዲኖር፣ ከገበያው ላይ መንግሥት የተቆጣጣሪነት ሚናውን እንዲያነሳ በማድረግ የምዕራባዊያኑን የኢኮኖሚ ተጠቃሚነትን እድል በማስፋት ላይ ያተኮረ ነው።

በዚህም ምዕራባዊያን ቀድመው በገነቧቸው ግዙፍ ድንበር ተሻጋሪ ኩባንያቸው /Multinational Corpo- rations/ አማካኝነት የአፍሪካ አንጡራ ሃብት ያለከልካይ ተጠቃሚ እንዲሆኑ ማስቻል ነው። ለዚህም ነው የኢኮኖሚ ግባቸውን እውን ለማድረግ የአፍሪካ አገሮች ላይ ከፍተኛ ጫና ሲያደርጉ የሚስተዋለው። አንድ አፍሪካዊ አገር ግዙፍ የመሰረተ ልማት ግንባታ ለማካሄድ ብድርና ድጋፍ የሚያገኘው ምዕራባዊያኑ ያስቀመጡትን የኢኮኖሚ ሞዴል እንዲከተል ለማድረግ መዋቅራዊ ጫና በማሳደር ነው። ለአብነትም በምዕራባውያኑ አስተሳሰብ የተቃኙት ግዙፎቹ የዓለም ባንክ /WB/ና የዓለም የገንዘብ ተቋም /IMF/ ብድርና ድጋፍ ለመስጠት የተለያዩ ቅድመ ሁኔታዎች ያስቀምጣሉ። በዋነኛነትም የመዋቅር ማሻሻያ መርሃ ግብር (structural adjustment program) የሚሉትን ቅደመ ሁኔታ እንዲያሟሉ በማስገደድ በቀላሉ

የምዕራባዊያን መንግሥታት ፍላጎት ተከትለው ለዘመናዊ የቅኝ ግዛት ሥልት ራሳቸውን እንዲያስገዙ መንገዱን ይከፍቱላቸዋል። በሌላ በኩል አፍሪካዊያን ብድር ውስጥ እንዲገቡና የኢኮኖሚ ፈተናቸውን እንዲላቀቁ የሚፈጥሩት ትርክት መዳረሻው አፍሪካዊያን በምዕራባዊያኑ ላይ ጥገኛ እንዲሆኑ የሚያደርግ ክስተት ነው።

ምዕራባዊያን የሚፈልጉትን የኢኮኖሚ ሞዴል ያልተከተሉ አፍሪካዊ አገሮችን ሰብዓዊና ዴሞክራሲ መብቶች ተጣሱ የሚል ሰበብ በመፍጠር የቀጥታም ሆነ ተዘዋዋሪ ጫና በማሳደር ለማንበርከክ ብዙ ርቀት ይሄዳሉ። የአንድን አገር መንግሥት ያዳክማልና ስሙንም ለማጉደፍ ይመቻል ያሉትን ሁሉ ይፈጽማሉ። አንድም በታላላቅ መገናኛ ብዙኃናቸው አልያም ደግሞ በይፋዊ መንግሥታዊ መረጃ ማስተላለፊያ መንገዶች የማጣጣል ሥራ ያከናውናሉ። ይህንንም ተከትሎ እነርሱ “ዴሞክራሲያዊ ነው” ያሉትን አመለካከት ብቻ በሕዝብና በዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ዘንድ ተቀባይነት እንዲያገኝ የተለያዩ ሥራዎች ይሰራሉ። ከዚህ አስተሳሰብ ውጪ የሚንቀሳቀሰውን አገር ወይም መንግሥት (international political legitimacy) ዓለም አቀፍ የፖለቲካ ቅቡልነት እንዳያገኝ የማይፈነቅሉት ድንጋይ የለም። ለዚህም ዋነኛ መሳሪያቸው የተለያዩ እቀባዎች ማድረግና ይፋዊ ግንኙነት እስከማቋረጥ የሚደርስ እርምጃ መውሰድ የተለመዱ ተግባሮቻቸው ሆነው ይታያሉ። ይህም በፖለቲካው ዘንድ ያላቸውን ፍላጎት ለማስፈጸም የሚያስችላቸውን ደጋፊ መንግሥት ለመፍጠር የሚያደርጉት ትንቅንቅ ነው ብሎ መደምደም ይቻላል። ጎን ለጎንም አፍሪካ የራሷን ጉዳይ በራሷ እንዳትፈታና በ”አውቅላችኋለሁ” መርህ አሁንም ምዕራባዊያኑ በዓለም አቀፍ ተቋማት የአፍሪካን ሥፍራ ተቆጣጥረውታል።

ሌላው በማኅበራዊ ዘርፉም በተመሳሳይ በባሕልና በአስተሳሰብ ላይ የበላይነት ለመያዝ የሚያደርጉት

“ድርጅቱ አፍሪካዊያን ነፃነታቸውን መቀዳጀታቸውን ተከትሎ በኢኮኖሚው

መስክም የእርስ በእርስ ትብብርና መደጋገፍ እንዲኖር ለማስቻል አከባቢያዊ

የኢኮኖሚ ማኅበረሰብ እንዲመሰረት አድርጓል። ይህም የእርስ በእርስ ንግድ

እንዲስፋፋ፣ ኢንቨስትመንት እንዲሳለጥና የጋራ ገበያ እንዲፈጠር አሁን ላይ

አገሮች ለሚያደርጉት ጥረት ትልቅ መሰረት የጣለ ክስተት ነው።



17

ጥረትም ዘመናዊ የቅኝ ግዛት ስልታቸው ነው። አብዛኞቹ ዘመናዊ አስተሳሰብ የምንላቸው አካሄዶች ይብዛም ይነስም ምዕራባዊያኑ የሚከተሏቸው መሆኑን ልብ ይሏል። ይህ ዝም ብሎ የመጣ አይደለም። በዓለም አቀፍ ደረጃ እነዚህ አገሮች የኢኮኖሚና የፖለቲካ የበላይነትን መያዛቸውን ተንተርሶ የመጣ ሲሆን፤ መዋቅራዊ ጫናን አሳድሯል። አሁንም ይህንን አስተሳሰብ በበላይነት ይዞ እንዲቀጥል ባሏቸው የመገናኛ ብዙኃንና ቴክኖሎጂ እንዲሁም የትምህርት ስርዓት ጭምር በመጠቀም የተለያዩ ጥረቶች እያደረጉ ነው። ይህም አፍሪካዊ አስተሳሰቦችን ወደ ኋላ በማድረግ የምዕራባዊያኑን አስተሳሰብ ገዥ እንዲሆንና ተናጠላዊ እውነታን ለመገንባት የሚደረግ ግብ ግብ ነው። ይህም የኋላ ኋላ አፍሪካ ማንነቷን እንድታጣና በተለይም የሥነ-ልቦና ነፃነቷ የተገፈፈ አህጉርና ሕዝብ በመፍጠር ረገድ ትልቅ ሚና ይኖረዋል።

የ”በቃ” ንቅናቄ (#NoMore) በኢትዮጵያ በሰሜኑ ክፍል የተቀሰቀሰውን ጦርነት ተከትሎ አሜሪካን ጨምሮ አንዳንድ የዓለም አገሮች በኢትዮጵያ ላይ ያልተገባ ጫና ለማሳረፍ የተለያዩ ሙከራዎች አድርገዋል። ይህንንም ምኞታቸውን ገቢራዊ ለማድረግ በሚዘውሯቸው ዓለም አቀፍ የዜና አውታሮች ተገን አድርገው ለጣልቃ ገብነቱ አመቺ አውድ ለመፍጠር ጥረዋል። እነዚህ ኃይሎች ለኢትዮጵያዊያን ፍላጎት ቆመው ባያቁም ጦርነቱን ምክንያት አድርገው የሰብዓዊ ቀውስ እንዳሳሰባቸው አስመስለው ጣልቃ ለመግባት ያልፈነቀሉት ድንጋይ አልነበረም። በአካሄዳቸውም ወገንተኝነትና በአንድ ወገን ላይ ወቀሳ አዘል ትርክት የተስተዋለበት ነበር። ይህንን አካሄድ የተመለከቱና በትኩረት ጉዳዩን ያጤኑት ሰዎችም እነዚህ አገሮች በኢትዮጵያ የውስጥ ጉዳይ ጣልቃ የመግባት ፍላጎት እንዳላቸው በመረዳት ሂደቱን ከጅምሩ አንስቶ አጥብቀው ተቃወሙ።

በተለይም በማኅበራዊ ሚዲያ የተቀጣጠለው የተቃውሞ ዘመቻ በርካታ ኢትዮጵያዊያን በማሰባሰቡ በአጭር ጊዜ ውስጥ ትርጉም ያለው እንቀስቃሴ ማድረግ ተችሏል። ይህንንም ተከትሎ አዲስ አበባን ጨምሮ የተለያዩ ከተሞች ላይ የተቃውሞ ሰልፎች ተካሂደው የምዕራባዊያኑን አካሄድ በእጅጉ አጣጥለውታል። በተለይም ደግሞ ኑሯቸውን በአሜሪካና በተለያዩ የዓለም አገሮች ያደረጉ አትዮጵያዊያን በፊታውራሪነት የአደባባይ የተቃውሞ

ዘመቻውን መምራት ጀመሩ።

በተለይ በሄርሜላ አረጋዊና ጓደኞቿ የተቀጣጠለው የበቃ “#NoMore” እንቅስቃሴ የተቃውሞ ዘመቻው በአንድ መሥመር እንዲፈስ አስችሎታል። ይህ ሂደት አንዳንድ ምዕራባዊያን አገሮች በኢትዮጵያ ላይ ብቻ ሳይሆን በአፍሪካ ቀንድ አካባቢ የኋላ ኋላም አፍሪካን ለመቆጣጠርና በውስጥ ጉዳይ ጣልቃ ለመግባት የሚያደርጉትን ሙከራ የሚቃወም ንቅናቄ ለመሆን ችሏል። የተቃውሞው እንቅስቃሴ ሕዝቡ ለጣልቃ ገብነት ያለውን ቅሬታ በማስተጋባት በሕዝቡ ውስጥ ያለውን እውነተኛ ስሜት ማመላከት የቻለ እንቅስቃሴም እንደነበር ማስታወስ ይቻላል።

ይህንን ተከትሎም በርካታ የዘመኑ የፓን አፍሪካኒዝም አቀንቃኞችም ሃሳቡን በመጋራትና በማስተጋባት አሁን ላይ የ”በቃ” ንቅናቄ ተቀላቅለዋል። በኢትዮጵያ ላይ የሚደርሰውን ጫናም “ነግ በእኔ” ስሜት በጽኑ አውግዘውታል። ኢትዮጵያ ላይ የተደረጉት ጫናዎች አፍሪካዊያን የምዕራባዊያን ዘመናዊ የቅኝ ግዛት መገለጫ አድርገው ስለተረዱትም ሂደቱን ከኢትዮጵያዊያን ጋር ተዳምረው ነቅፈውታል። ይህንንም ተከትሎ፤ በርካታ አፍሪካዊያንም የአንዳንድ ምዕራባዊያን አገሮች ጫናን በመቃወም በኢትዮጵያዊያን የተጀመረውን የበቃ ዘመቻ መቀላቀላቸውን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ብርቱካን አያና የገለጹትን እዚህ ላይ መጥቀስ ይቻላል።

በተለይም በኢትዮጵያ ላይ የሚደረገውን ያልተገባ ጫና በመቃወም ከኢትዮጵያ ጋር መቆማቸውን ተከትሎ ምስጋናም አቅርበውላቸዋል። አፍሪካዊያንም ይህንን አንድነት አጠናክረው መቀጠል እንዳለባቸው አንስተው “አንድ ከሆንን እናሸንፋለን፤ ከተከፋፈልን ደግሞ እንሸነፋለን” በማለት የፓን አፍሪካኒዝምን ትስስር አጽንኦት በመስጠት ነው የገለጹት።

እንቅስቃሴው የአፍሪካዊያንን ቀልብ መሳቡን ተከትሎ ተጽዕኖ ፈጣሪ ግለሰቦችን ትዊተር አካውንት እስከመዝጋት የደረሰ እርምጃ የተወሰደበትን ሁኔታ ስናጤን ትግሉ ምን ያህል መራር እንደሆን ያመላክተናል። ይህ እንቅስቃሴው አሁን ላይ ምዕራባዊያን በአፍሪካ አገሮች ላይ የሚያሳድሩትን አዲስ ተፅዕኖ በመከላከል ረገድ ትልቅ እምርታ አስመዝግቧል ማለት ይቻላል። በተለይም አፍሪካዊያን በንቅናቄው መቀላቀላቸው የሚያመለክተው ነገር ቢኖር የምዕራባዊያን ጫና አሁንም አፍሪካ ላይ

ኃያል መሆኑን የሚያሳይ ነው። ይህም አፍሪካዊያን በፓን አፍሪካኒዝም እሳቤ መሰባሰብና ለጋራ ዓላማ አሁንም መታገልና በአንድነት መቆም እንደሚገባቸው ያመላከተ ነው። አፍሪካዊያን በአንድም በሌላ መልኩ ለመብትና ለነፃነታቸው ይብዛም ይነስም ትግል ውስጥ እንደሚገቡም ጥቁምታ ሰጥቷል።

እንደ መውጫ

አሁን ላይ አፍሪካ በተለይም በዘመናዊ የቅኝ ግዛት እይታ ውስጥ መውደቋ የማይታበል ነው። ይህንን ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ አስተሳሰብ ለመከላከል አፍሪካ ፖለቲካዊ ውህደቷን ይበልጥ በማጠናከርና ለውጭ ኃይሎች የማይንበረከክ ፖለቲካዊ ሥርዓት መገንባት ያስፈልጋል። በተለይም ደግሞ ጠንካራ መንግሥት ለመፍጠር የሚያስችሉ የተቋም ግንባታና የሰለጠነ የሰው ኃይል ማፍራት ላይ ትኩረት ሊደረግ ይገባል።

ፖለቲካዊ ሥርዓቱ ዴሞክራሲያዊ አሰራርን ማስፈን ይገባል። በተለይም ግልጸኝነትና ተጠያቂነትን ማዕከል ያደረገ ቅቡልነት ያለው መንግሥት እንዲጸና ማድረግም አስፈላጊ ነው። ይህም የሕዝብ ድጋፍ ያለው መንግሥት የተለያዩ ጫናዎችን ለመቋቋምና ውስጣዊ አቅም ለመፍጠር ሁነኛ መፍትሔ ስለሆነም ጭምር ነው። ከዚህ ጋር ተያይዞ የሚነሳው አፍሪካን የሰላም ማዕከል የማድረግ አስፈላጊነት ነው። በአሁኑ ወቅት የሚስተዋለው በአገሮች ላይ የሚከሰተውን ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ምስቅልቅ ትኩረት አግኝቶ መፍትሔ ሊሰጠው ይገባል። ከዚህ በተጨማሪ አፍሪካ በፖለቲካም በኢኮኖሚም ነፃ እንድትሆን የቅስቀሣ /advocacy/ ሥራዎች በአህጉር ደረጃ ተጠናክሮ መቀጠል ይኖርበታል። በዚህ ረገድ የአፍሪካ ልሂቃን ሚናቸው ከፍ ያለ ነው። በተለይም ደግሞ የምዕራባዊያን አገሮች አፍሪካን በተመለከተ የሚከተሉትን ፖሊሲዎች በማስቀየር ረገድ ሚናቸው ከፍተኛ ነው።

በሌላ በኩል ከውጭ ድጋፍና እርዳታ ላይ ጥገኛ የሆኑ የኢኮኖሚ አካሄዶችን በመቀየርና በምትኩም ውስጣዊ የሃብት ማሰባሰብ ላይ ትኩረት ያደረገ የኢኮኖሚ አቅጣጫ መከተል ይገባል። እዚህ ላይ ስመ ጥሩ የሩዋንዳው የፋይናንስ ሚኒስትር ዶናልድ ካብሩካ “ገንዘብ ሳይሆን ልማት የሚያመጣው፤ ትክክለኛ ፖሊሲዎችና የመፈጸም አቅም ነው” የሚለውን ራሱ “ገንዘብ” ማድረግ ሳይበጅ አይቀርም። ይህንንም መሰረት በማድረግ የቴክኖሎጂና ሥራ ፈጠራ ክህሎት ላይ ያተኮረ ኢኮኖሚያዊ እድገትን መቀየስ አማራጭ የሌለው ነው። በተለይም አፍሪካን ከጥገኝነት ሊያላቅቃት የሚችሉ የግብርና፣ የማኑፋክቸርና ሌሎችም ዘርፎች ላይ ኢንቨስትመንት ፈሰስ በማድረግ እድገቷን ማስቀጠል ይገባል። ይህም አፍሪካ የኋላ ኋላ በኢኮኖሚዋ ጠንካራ እንድትሆንና የአህጉሪቷ ፖለቲካ ለውጭ ተጽዕኖ ተጋላጭ እንዳይሆን ሚናው የላቀ ነው። ይህንንም ማድረግ ከተቻለ የአፍሪካ አገሮች አንድም የራሳቸውን ብሔራዊ ትልም ለማሳካትና የጋራ አፍሪካዊ ራዕያቸውንም እውን ለማድረግ የሚቸገሩበት ሁኔታ አይኖርም።



18

አዲስ ገጽ- አዲስ ምዕራፍ

ዓብይ ርዕስ



19

አዲስ ገጽ- አዲስ ምዕራፍ በሙሉጌታ አንበርብር (የመጽሄቱ ተከታታይና ጸሀፊ)

የለውጥ ማዕበል “ዳዎን ዳዎን ወያኔ!” የሚል ድምጽ የኢሬቻ በዓል ለማክበር ከተገኙ ወጣቶች መካከል በአንዱ ሲስተጋባ በአብዛኛው የአገሪቷ ክፍል የተቀጣጠለው ለውጥ የመጨረሻው ምዕራፍ ላይ መድረሱን አመላካች ነበር። የቀጥታ ስርጭት በሚያስተላልፉት የመገናኛ ብዙሃንም ድምጹን አስተጋቡ። የለውጥ ማዕበሉ እየተወነጨፈ ጡዘት ላይ መድረሱን ያወጀ ድምጽ ነበር። ያኔ ህወሓት/ኢህአዴግ የሥልጣን ዘመን መጨረሻው ምዕራፍ ላይ መድረሱን ያልተገነዘበ የለም። በጉልበቱ ተፈርቶ የቆየን ገዥ ፓርቲ በኃይል በአደባባይ “ዳዎን ዳዎን ወያኔ!” ሲባል መልዕክቱ ግልጽ ነው፤ በጉልበቱ ከመፈራት ይልቅ ወደ ለየለት ጥላቻ መድረሱን ያሳያል። ኢህአዴግ የተጀመረውን ሕዝባዊ ተቃውሞ በሚያካሂዳቸው አሰልቺ ስብሰባዎች፣ የተሃድሶ ግምገማዎች ለመቀልበስ ቢሞክርም ያለመቻሉን ያረጋገጠ መልዕክትም ነው።

ሕዝባዊ እንቢተኝነቱን በአማራ ፋኖ፣ በኦሮሚያ ቄሮ፣ በሃዋሳ ኤጀቶ፣ በጉራጌ ዘርማ፣ በአፋር፣ በሶማሌና በሌሎችም ወጣቶች ተደራጅተው ለውጡን አፋጠኑት። የለውጥ ፍላጎታቸውን አደባባይ በመውጣትና ተቃውሞውን በተለያዩ መንገዶች በመግለጥ ህወሓት/ኢህአዴግን “በቃህ፤ ለውጥ እንፈልጋለን” በማለት በቁጣ አስተጋቡ።

በተለይ የአማራ ወጣቶች “የኦሮሞ ደም ደማችን ነው” ብለው ስርዓቱን “በቃህ!” በማለት በተለያዩ ከተሞች ተቃውሟቸውን አሰሙ። ሂደቱ ወደ ለየለት አገራዊ ተቃውሞ ተስፋፍቶ ወደ ማይቀረው ለውጥ አመላከተ።

ኢህአዴግ በውስጡ “ተሃድሶ፣ ዳግም ተሃድሶና ጥልቅ ተሃድሶ” በሚል በተደጋጋሚ አሰልቺና አድካሚ ስብሰባዎች ቢያካሂድም አንዳች መፍትሄ ሳይመጣ ጉዞው ከድጡ ወደ ማጡ ሆነ። ብዙዎች “ኢህአዴግ ከችግሩ መላቀቅ



20

አይቻለውም። አገሪቷን ወደ ከፋ ችግር እየከተታት፣ ለብተና እየዳረጋት ነው” የሚል እምነት መያዝ በጀመሩበት ወቅት ነው የወጣቱ ድምጽ ጎልቶ ያስተጋባው። ይህ ብዙዎችን ያነቃ፤ ህወሓት/ኢህአዴግ በወጣቶች ላይ የከፋ እርምጃ እንዲወስድ ያደረገ ነበር። በጥላቻ ላይ ጥላቻ እያሳደረ መምጣቱም በግልጽ ታየ።

ኢህአዴግም ሆነ መንግሥት ዕለት ተዕለት እያደገ የመጣውን አመጽ ለመግታት በማሰብ ያካሄዱት ለውጦች “ጥገናዊ እንጂ መሰረታዊ ለውጥ አይደለም” በሚል እሳቤ ትግሉ ተፋፋመ። ኢህአዴግ በውስጡ የተቀጣጠለው እሳት አገሪቷን ለለውጥ ቢጋብዝም በስልጣን ላይ የነበረው ኃይል የበላይነቱን ላለመልቀቅ እዚህም እዚያ የሚለኩሳቸው እሳቶች አገሪቷን ወደ ለየለት የእርስ በርስ ጦርነት እንዳያስገባት ስጋት አሳድሮ ቆየ። ዓመጹ እየተጋጋለም የአመራር ሽግግር እያለ ሰዎችን ቢቀያይርም የለውጥ ማዕበሉ እየገፋ ሄደ። አገር እጅግ አሳሳቢ ሁኔታ ውስጥ ወደቀች። ሰዎች ከዛሬ ነገ ምን ይፈጠራል? በማለት ጭንቀት ውስጥ ገቡ። ሰላማዊ የለውጥ እንቅስቃሴ እጅግ ወደ ከፋ እልቂት ቢያመራስ? ወደ የሚል ጭንቀት ወሰደ።

በበርካታ ሰዎች ኢህአዴግ በአገሪቷ የተንሰራፋውን ሌብነትና ኋላቀር አስተሳሰብ ከመታገል ይልቅ ቂም በቀልና ቁርሾ ገዢ አጀንዳ እንዲሆን ማድረጉን አስተዋሉ። በዚህም የህወሃት/ኢህአዴግ የአገሪቷን መሰረታዊ የለውጥ ጉዳይ ወደ ጎን ትቶ መቆየቱ ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ከፍተኛ ዋጋ እንደሚያስከፍል እምነት አሳደረ።

የሰብዓዊ መብት ጥሰት፣ የዴሞክራሲያዊ ሥርዓት እጦት፣ ኢ-ፍትሃዊ አስተዳደር ያንገፈገፋቸው ንጹሃን የሚያካሂዱት ሰላማዊ ትግልን ጠልፎ ወደ ኃይልና ነውጥ ለማሸጋገር የሚሰሩ ሴራዎች መኖራቸው በገሃድ እየታየ መጣ። በህወሓት የሴራ ፖለቲካ በአገሪቷ ኢንቨስትመንት ላይ ያተኮሩ ጥፋቶች ተከሰቱ። ኢንቨስተሮች ላይ ያነጣጠሩ ግድያዎች፣ የግለሰቦች ንብረት መዝረፍና ማውደም የዕለት ተዕለት ዜና ሆነ።

በርካታ ዜጎች ተወልደው ወግ ማዕረግ ካዩበት አካባቢያቸው መፈናቀል፣ በማንነታቸው ብቻ በግፍ መገደል፣ መሰደድ እየተስፋፋ መጣ። አገሪቷ አጣብቂኝ ውስጥ ገባች። የለውጥ ማዕበሉ ወዴት እንደሚያመራ መገመት የማይቻልበት ደረጃ ላይ ደረሰ። ማዕበሉን ለመቋቋም ምን መደረግ ይኖርበት ይሆን? የሚለው ጥያቄ ለብዙዎች ራስምታት ሆነ። በዚህ ወቀት ነበር የመጀመሪያው ምላሽ የካቲት 6 ቀን 2010 ዓ.ም የተሰማው።

የኢፌዴሪ የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ በገዛ ፈቃዳቸው ሥልጣን ለመልቀቅ ጥያቄ ማቅረባቸውን በመገናኛ ብዙሃን በኩል ለመላው ህዝብ ይፋ አደረጉ።

ኢህአዴግና መንግሥት እያካሄዱ ላለው ሪፎርም ስኬት ሲሉ ሥልጣናቸው ለመልቀቅ መወሰናቸው በብዙዎች

ዘንድ ያልታሰበ ነበር። “እኔም በበኩሌ ለእነዚህ ሪፎርሞችና የመፍትሄ አቅጣጫዎች የመፍትሄ አካል ለመሆን በማሰብ በገዛ ፍላጎቴና ፈቃዴ የኢህአዴግ ኃላፊነቴንም ሆነ፣ የመንግሥት ኃላፊነቴን ለመልቀቅ ጥያቄ አቅርቤያለሁ” በማለት ነበር ሥልጣን የመልቀቃቸውን ጉዳይ ያሳወቁት። ነገር ግን በምትካቸው ድርጅቱንም ሆነ አገሪቷን የሚመራ ሰው እስከሚመረጥ ድረስ ኃላፊነታቸውን እየተወጡ እንደሚቆዩ መግለጻቸው እንዲሁ።

የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ስልጣን የመልቀቅ ጉዳይ በርካታ መላምቶችን አስከተለ። በአንድ በኩል በአገር ደረጃ የተፈጠረው የለውጥ ማዕበል አንዳች መልካም ነገር ይዞ እንደሚመጣ፤ በሌላ በኩል ለውጡ ተቀልብሶ ከበፊቱ በባሰ ሁኔታ ውስጥ ሊያስገባ የሚችል ችግር ውስጥ የመክተት እጣ ፈንታ ላይ ሊወድቅ እንደሚችል ስጋት ጫረ።

በ2013 ዓ.ም “የመደመር መንገድ” በሚል ርዕስ የታተመው የጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ አህመድ መጽሀፍ ላይ እንደተገለጸው የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማርያም ሥልጣን የመልቀቅ ጥያቄ ማቅረብ “ከጠቅላይ ሚኒስትሩ የሥልጣን መልቀቂያ ጋር ያልጠበቅነውና ያልገመትነው ታሪካዊና ሰፊ የዕድል በር ከፊታችን ተከፍቷል። ይህንን ልዩ እድል እንደሌላው ጊዜ ከፊታችን በከንቱ ከአባከንነው የሚያስከፍለን ዋጋ ከመቼውም ጊዜ የከፋ ሊሆን ይችላል” በማለት እድልና ተግዳሮት ይዞ መምጣቱን ያመለክታል። ለውጡን በአግባቡ መምራትና ውጤታማ ማድረግ አገሪቷን ከከፋ አደጋ የመታደግ ጉዳይ ነበር።

የለውጥ ማዕበሉ አቅጣጫውን እንዳይስት በጥበብ መምራት አስፈላጊ ብቻ ሳይሆን ለአገሪቷ የህልውና ጥያቄ ምላሽ የያዘ ነበር። በኢህአዴግ ውስጥ ለለውጥ ሲንቀሳቀስ የቆየው ኃይል እድሉን ለመጠቀም የሚያስችለውን አቅጣጫ መከተል ግድ የሚልበት ጊዜ ላይ ደርሷል። የለውጥ አይቀሬነት እውን ቢሆንም “ለውጡ አዲስ አስተሳሰብና መንገድ ይዞ የሚመጣ ነው ወይ?” የሚለው ጥያቄ እስከ መጋቢት 2010 ዓ.ም ድረስ ምላሽ ያላገኘ የብዙዎችን ልብ አስጨንቆ ይዞ የቆየም ነበር።

ኢህአዴግ ውስጣዊ ሽኩቻውና ፍትጊያውን ለማሳረግ በመጋቢት 2010 ዓ.ም የድርጅቱን ሊቀመንበርና ምክትል ሊቀ መንበር ለመምረጥ ስብሰባ ተቀመጠ። ስብሰባው እየተራዘመ የማይቀረው ሰዓት ደርሶ ምርጫውን አካሄደ። የኢህአዴግ ሊቀ መንበርና ምክትል ሊቀመንበር መረጠ። በምርጫው ውጤት አዲስ ነገር ተከሰተ።

በኢህአዴግ ውስጥ ሲንቀሳቀስ የቆየው የለውጥ ሃይል በአሸናፊነት ወደፊት መምጣቱን አረጋገጠ። “ለውጡ ይቀለበሳል” የሚለውን ስጋት ከንቱ ያስቀረ የምርጫ ውጤት ይፋ ሆነ። የለውጥ ማዕበል በአዲሱ ኃይል ሰከነ። በአዲስ አስተሳሰብ ተገራ። ለመጀመሪያ ጊዜ በኃሳብ ትግል ሰላማዊ የሥልጣን ሽግግር ይፋ ተደረገ። አዲስ ገጽ ተገለጠ።

“የኢትዮጵያን የብልጽግና ጉዞ እውን ለማድረግ ገዢ ሀሳብ ይዘን በትጋት መስራት

ይጠበቅብናል” የፓርቲው ፕሬዝዳንት ዶክተር

ዐብይ አህመድ



21

የኢህአዴግ ሊቀ መንበር በመሆን ዶክተር ዐብይ አህመድ ተመረጡ። ኢህአዴግ በአዲስ መልክ አዲስ ምዕራፍ ጀመረ።

አዲስ አተያይና የለውጥ

ማግስት ፈተና ኢትዮጵያ በየጊዜው ልጆቿ በርዕዮተ ዓለም ልዩነት ሕይወታቸውን የሚገብሩባት አገር ነች። አንዱ ሶሻሊዝም፣ ሌላው ካፒታሊዝም፣ ሌላኛው ደግሞ አብዮታዊ ዴሞክራሲ በሚል የርዕዮተ ዓለም ልዩነት እርስ በርሳቸው የሚተላለቁባት አገር ከሆነች ዓመታት ተቆጥረው አልፈዋል። ብዙ ሊሰሩ፣ ከውስብስብ ችግሯ ለማውጣት የሚችሉ የመፍትሄ ኃሳብ ሊያመነጩ የሚችሉ ልጆቿ በጥይት ተመተው በየጉድባው ወድቀዋል። የሀሳብ ልዩነቶችን ማስተናገድ ባለመቻል ውድ ልጆቿ ተሰውተዋል። ይህን አካሄድ የሚሽርና ወደ አዲስ መንገድ የሚያስገባ አተያይ መፈጠሩ የተበሰረው በለውጥ ማዕበል ሲናጥ የነበረው የህወሓት/ኢህአዴግ መንግሥት ሰላማዊ የሥልጣን ሽግግር ባደረገ ማግስት ነው።

አዲስ የተመረጡት የግንባሩ ሊቀ መንበር ዶክተር ዐብይ አህመድ በወቅቱ ኢትዮጵያዊያን በመደመር እሳቤ አገራቸውን ከገባችበት ችግር ለማላቀቅ መትጋት እንዳለባቸው አሳወቁ። “በፍቅር እንደመር፤ በይቅርታ እንሻገር” የሚለው ሀሳብ ከርዕዮተ ዓለም ትንቅንቅ ወደ አገር በቀል አስተሳሰብ የሚያመጣ፣ “የአገሩን በሬ በአገሩ ሰርዶ” የሚሉት ነገር ሆነ። የመደመር እሳቤ ለአገራችን አዲስ አተያይ ሆኖ ተከሰተ። የለውጥ ኃይሉ ማሸነፉ እውን ሆነ።

“ዶ/ር አቢይ አሕመድ የኢህአዴግ ሊቀ መንበር ሆነው ሲመረጡ፣ የለውጡ ኃይል በይፋ የመሪነት ሚናውን ያዘ። ይህ ሂደት የለውጡን አዲስ ጅማሮ የሚያበስር ብቻ ሳይሆን በህወሓትና በለውጡ ኃይል መካከል አዲስ ዓይነት ግንኙነት የመሠረተ ነው” በማለት የፌዴሬሽን ምክር ቤት ህዳር 2013 ዓ.ም ያወጣው ሰነድ ያትታል።

የለውጥ ንቅናቄው ከማዕበልነት ወደ የሃሳብ ልዕልና ተሸጋገረ። ከነውጥ በሀሳብ ልዕልና ያተኮሩ ስራዎች ወደ መከወን ትኩረት ማድረግ ጀመረ። ይህ ሲሆን በየአካባቢው መልካቸውን የቀየሩ ነውጦች፣ የዜጎች መፈናቀልና ግድያዎች ይከሰቱ ነበር። በዚህ ጊዜ ውስጥም ቢሆን በለውጥ ኃይልና ለውጥን በሚቃወም ኋላቀር አስተሳሰብ በተተበተቡ ኃይሎች መካከል የሚደረገው ትንቅንቅ መገለጫ መንገዱን ለውጦ በከፋ መልኩ ቀጥሏል።

በሕዝብና በድርጅቱ ውስጣዊ ትግል የተገኘው ለውጥ የተለያዩ ድሎችን እያስመዘገበ መጣ። አገራዊ አንድነት እንዲሰፍንና ብሔራዊ መግባባት እንዲፈጠር የሚያስችሉ እርምጃዎች ተወሰዱ። እስረኞች ተፈቱ፤ የጥላቻ ትርክት

እንዲቀር ለማድረግ የሚያስችሉ ስራዎች መከናወን ጀመሩ። አዲሱ የድርጅቱ አመራር ከመጣ በኋላ “ፍቅርና ይቅርታ፣ ዕርቅና ሰላም፣ መግባባትና አንድነት” የሚሉ ሀሳቦች የለወጡ ድምጾች ሆኑ።

ከዚህ በኋላም ለሕዝባዊ ተቃውሞ መነሻ የሆኑ ፓለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ማኅበራዊ ችግሮችን ሊፈቱ የሚችሉ ተግባራት መከናወን ጀመሩ። በለውጡ ዋዜማ አገሪቷ ገብታበት የነበረው ከፍተኛ የብድር ጫና፣ በአግባቡ ያልተመሩና ኢኮኖሚውን ሲበሉ የቆዩ ግዙፍ ፕሮጀክቶች፣ የምዝበራና የብክነት ማዕከሎች ሆነው የቆዩ የልማት ተቋማት መፍትሄ እንዲያገኙ እርምጃዎች ተወሰዱ። ከፍተኛ ሥራ አጥነት እና ኢ-ፍትሃዊነት መፍትሄ እንዲያገኙ ሥራዎች መከናወን ጀመሩ። ገደል አፋፍ ላይ የደረሰውን ኢኮኖሚ መፍትሄ ለማስገኘት የሚያስችሉ ስራዎች ተከናወኑ። በፖለቲካ አመለካከታቸው ታስረው ስቃይ ሲያዩ የነበሩ ዜጎች መፈታታቸውም የለውጡ ትሩፋት ነበር። ዜጎች በአስተሳሰብ ልዩነታቸው የማይታሰሩባትና የማይሰቃዩባት፣ ዴሞክራሲያዊ መብታቸው እንዲከበር ሲጠይቁ የጥይት ምላሽ የማይሰጣቸው መሆኑን የሚያረጋግጡ እርምጃዎች ተወሰዱ። የኃሳብ ልዕልና አሸናፊ ሆኖ የሚወጣበት ጊዜ ላይ መድረሱን አመለካች እርምጃዎች መወሰዳቸው ታየ።

የኢትዮጵያ ሕዝብ ናፍቆት የቆየውን የፖለቲካ ምህዳር ማስፋት እና የዴሞክራሲ ሥርዓት ልምምድ እውን የማድረግ ተግባር የለውጡ አንድ ስኬት ተደርጎ ይጠቀሳል። ፓርቲው በመጀመሪያ ከወሰዳቸው ተግባራት መካከል የዴሞክራሲ እና የሰብዓዊ መብት ተቋማት ግንባታ፣ የፍትሕ ሥርዓት ማሻሻያ እና ሕግ ማስከበር ጉዳይ፣ የፀጥታ እና የደህንነት ተቋማት ሪፎርም፣ የፌዴራል ስርዓት ሪፎርም እና የእውነተኛ ፌዴራሊዚም ግንባታ ሊያፋጥኑ የሚችሉ ለውጦች መካሄድ ነበር።

በለወጡ ማግስት ጀምሮ የሚሰሙት ሰበር ዜናዎች ኢህአዴግ በለውጡ አመራር በትክክል መቀየሩን የሚያመለክቱ ነበሩ። ለኢኮኖሚው ዕፎይታ ያስገኙ የዲፕሎማሲ እንቅስቃሴዎች፣ በጥናት ላይ የተመሰረተ ሃገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ እርምጃዎች፣ ግብርናውን የማዘመን ተግባራት የሕዝቡን ልብ በተስፋ የሞሉ ናቸው።

ይህ ብቻ ሳይሆን የአገሪቷን ሉዓላዊነት እና ብሔራዊ ጥቅምን ማስከበር የሚያስችሉ እርምጃዎች መወሰዳቸው ፓርቲው በትክክለኛ መስመር ላይ መሆኑን ያንጸባረቁ ጉዳዮች ነበሩ። አገራዊ እና የዜጎች ክብር ጎልቶ እንዲወጡ ለማድረግ የሚያስችሉ ዲፕሎማሲያዊ እንቅስቃሴዎችና የተገኙ ውጤቶች አገሪቷን በመልካም ያስጠሩ ጉዳዮች ነበሩ።

በጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ አህመድ ጠንካራ አመራር የኢትዮ ኤርትራ ጉዳይ በሰላማዊ መንገድ እንዲፈታ የተወሰደው እርምጃ ድርጅቱ መልካም አቅጣጫ መከተሉን አሳይቷል። በተለይም ከጎረቤት አገሮች ጋር

ወደፊት ሊያካሂዳቸው ያሰባቸውን መልካም ግንኙነቶች በግልጽ የጠቆመ ነበር ማለት ይቻላል። አብሮ የማደግና የመበልጸግ ትልሙንም አሳይቷል።

የለውጡ መንግሥት ስልጣን በመቆጣጠሩ በአገሪቷ ላይ የሚወስዳቸው እርምጃዎች መጪውን ዘመን የሚያመላክቱ መሆናቸው እሙን ነው። ለውጡ በየጊዜው የሚከተሉትን እያየዘ፣ በኋላ ቀር አስተሳሰብ ወደ ኋላ የሚጎትቱን እያለፈ መሄድ መጀመሩ ያላስደሰታቸው ህወሃትና የጥፋት ግብረ አበሮቹ በተለያየ አቅጣጫ ጥቃት ማካሄድ ጀመሩ። በተለያዩ አካባቢዎች መፈናቀል ቀጠለ። በሶማሌና በኦሮሞ ብሔረሰቦች መካከል ግጭት እንዲካሄድ ተደረገ፤ ግጭቱ ከፍተኛ መፈናቀል አስከተለ። የከፍተኛ አመራር አባላት ግድያ ተፈጸመ። በርካታ ችግሮችና ተግዳሮቶች አገሪቷ ተጋፈጠች። እነዚህ ድርጊቶች ለውጡን ለመቀልበስና ዳግም ፍጹም ኢ-ፍትሃዊ ወደ ሆነ አስተዳደር ለመምራት የተሴሩ ሴራዎች መኖራቸውን አጋለጡ። እነዚህን የፖለቲካ ሴራዎች እያለፈ፣ ችግሮቹን እየፈታ ቀደም ብሎ አጋር የሚባሉት አምስት ድርጅቶችን አካቶ ኢህአዴግ ከአራት ብሔራዊ ድርጅትነት ወደ አንድ ውህድ ፓርቲ የማምራት ጉዞውን አሳካ። ብልጽግናም ተወለደ።

“ብልጽግና የዛሬና የነገ ፓርቲ” ሆኖ መጣ።

ብልጽግና በመደመር “ብልጽግና ፓርቲ በመደመር መርህ አገራዊ እሳቤዎችን የያዘ መሆኑ ልዩ ያደርገዋል” ነበር ያሉት የፓርቲው ሊቀ መንበር ዶክተር ዐብይ አህመድ “ከፈተና ወደ ልዕልና” በሚል መሪ ሀሳብ የመጀመሪያው ድርጅታዊ ጉባዔ በተካሄደበት ወቅት።

ብልጽግና ፓርቲ ሲጠነሰስ በመደመር ፍልስፍና ኢትዮጵያዊ እሳቤዎችን ታሳቢ አድርጎ የመጣ ውህድ ፓርቲ መሆኑንም አመላክተዋል። ፓርቲው “ከዚህ በፊት ከነበሩት ከመኢሶን፣ ኢሰፓና ኢህአዴግ በተለየ መደመር መርሃችን ብልጽግና መዳረሻችን የሚል ግልጽ መስመር ስላለው ጭምር ነው” ሲሉ ነው ልዩነቱን ያሳዩት።

የሕዝቦችን ጥያቄ በመያዝ ትግሉን በውስጥና በውጭ በማድረግ አገራዊ ምላሽ ለመስጠት የቆመው ብልጽግና የመደመርን ፍልስፍና ዋናው መንገዱና የችግሮች መፍቻ መሳሪያው አድርጓል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ ባሳተሙት “የመደመር መንገድ” ላይ እንደገለጹት አገሪቷ የጀመረችውን ለውጥ ለመምራት “የመደመር እሴት ትልቅ ተስፋ ተጥሎበታል።”

መደመርን የችግሮች መፍቻ ለማድረግ ዋነኛ መንስኤ ተብለው ከተጠቀሱት መካከል “ብዙዎቹ ችግሮች ከመደመር እሴት መላላት የመነጩ መሆናቸው ነው።” ብልጽግና እነዚህ እሴቶች እየተሟሉ ከመጡ ጠንካራ አገረ መንግሥትና ሕዝብ ለመፍጠር ለሚደረገው ርብርብ ሁነኛ መፍትሄ እንደሚሆን ታምኖበታል። አገራዊ



22

እሳቤዎች ላይ መሠረት የማድረግ ምስጢርም ይሄው ነው።

የብልጽግና ፓርቲ የፖለቲካ ፕሮግራም ሶስት ግቦች የሚያመላክቱትም አንደኛው፣ ጠንካራና ቅቡል ሀገረ መንግሥት በጽኑ መሠረት ላይ ለመገንባት የሚያስችል ሀገራዊ መግባባት መፍጠር ነው። ይህም ሕዝቡ የልማት፣ የእኩልነትና የነፃነት ፍላጎት እንዲሟላለት የሚያስችል ነፃ፣ ገለልተኛና ብቃትን መሠረት ያደረገ ተቋማዊ አደረጃጀት የመገንባት አስፈላጊነት ላይ አፅንኦት ይሰጣል። ሁለተኛ ተቋማዊና ሕዝባዊ ባህል ላይ የቆመ የዴሞክራሲ ስርዓት መገንባት ግቡ አድርጓል። ሶስተኛው ዘላቂና አዎንታዊ ሰላምን ማረጋገጥ ነው። ዘላቂ ሰላም የማረጋገጥ ጉዳይ ሁለንተናዊ ብልጽግና እውን ለማድረግ መሰረታዊ ነውና!

በ“የመደመር መንገድ” ላይ እንደተጠቀሰው መደመር ችግሮችን ለመፍታት መሰረቱን የሚጥለው የጋራ ራዕይ መፍጠር፣ ትክክለኛ መሪ መፍጠር፣ የለውጥ አስፈንጣሪዎች ሚና፣ የሕልሙ ባለቤት ብዙሀኑ ማድረግ ናቸው። በእነዚህ የፍልስፍና መሰረቶች ብልጽግና እውን መሆኑ አገራዊ መፍትሄ ይዞ እንደመጣ ያመለክታል።

ከመጋቢት 2 እስከ 4 ቀን 2014 ዓ.ም ድረስ የመጀመሪያውን ጉባዔ ያካሄደው ብልጽግና “ችግሮችን በማለፍ የተሻለች ኢትዮጵያን ለመፍጠር እየሰራ የሚገኝ ድርጅት ነው” ሲሉ ነበር ምክትል ፕሬዚዳንቱ አቶ አደም ፋራህ ያረጋገጡት። ፓርቲው ከመጀመሪያው የለውጥ ማግስት ጀምሮ ያጋጠሙ ችግሮችን በመፍታት ጉዞውን

በመቀጠሉ አሁን ላይ ደርሷል።

ፓርቲው “በርዕዮተ ዓለም ያልታሰረ፣ አሰላሳይና ፕራግማቲዝም እሳቤን የሚከተል፤ ኢትዮጵያዊያን ሁሉ በእኩልነት የሚሳተፉበት የሁሉም ኢትዮጵያዊ ቤት እንጂ ቅድሚያ የሚሰጠው ቡድንም ሆነ ግለሰብ የለውም” በማለት ከኢህአዴግ ከሚለይበት ባህሪያት አንዱ መሆኑን የሚገልጸው ኃሳብ በተግባር የተተረጎመ መሆኑ ተስተውሏል። ፓርቲው አቃፊ መሆኑም ታይቷል።

“ብልጽግና አጋር ሲባሉ የነበሩትን ድርጅቶች በማሳተፍ፣ ውሳኔ ሰጭ በማድረግና የተፎካካሪ ፓርቲዎችን ከሚንስትር ጀምሮ በየደረጃው በማሳተፍ አካታችና ሁሉን አቀፍ መሆኑን በተግባር አሳይቷል” ሲሉ የፓርቲው ፕሬዝዳንት ዶክተር ዐብይ የገለጹት ሀሳብ እውነታውን ያንጸባርቃል።

ፓርቲው ባለፉት ዓመታት ያጋጠሙትን ተግዳሮቶች ማለፍ የቻለው “አካታችና ሁሉን አቀፍ ህብረ ብሄራዊ ፓርቲ በመሆኑ ነው” በማለት ነበር የአካታችነቱን ሀሳብ አጽንኦት የሰጡት ፕሬዝዳንቱ ዶክተር ዐብይ።

በመደመር እሳቤ እየተመራ የመጣቸው መንገዶች በበርካታ ፈተናዎች የታጀበ ነው። በአንድ በኩል በአሸባሪው ህወሓት የሴራ ፖለቲካ የሚመሩ የጥፋት ድርጊቶች እዚህም እዚያም እየበዙ መምጣታቸው የዜጎችን ሰብዓዊ መብት ለማክበርና ለማስከበር የሚደረገውን ጥረት ተገዳድሯል። በተለይም አገርን አደጋ ላይ የጣለውና በሰሜን እዝ የመከላከያ ሰራዊት

ዶክተር ዐብይ አህመድ፣ ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ አደም ፋራህና ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ ደመቀ መኮንን

(ፍቶ ክሬዲት ጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት)



23

ላይ የተፈጸመው ኢ-ሰብዓዊ ድርጊትና ዘግናኝ ወንጀል የአገር መክዳት አንዱ መገለጫ በመሆኑ መላውን ሕዝብ አስቆጥቶ የሕግ ማስከበር ዘመቻ ከተደረገ በኋላ በአማራና አፋር ክልሎች የደረሱት ጥፋቶች የአገሪቷን መልካም ስምና ዝና ያጎደፉ ነበሩ። እነዚህ ክስተቶች ለብልጽግና እጅግ ፈታኝ እንደነበሩ እሙን ነው። ይህም ሆኖ የመጡትን ፈተናዎች ከሕዝቡ ጋር በመሆን እያለፈ መጥቷል።

ፓርቲው ህብረ ብሔራዊ መሆኑ ለጥንካሬው ምንጭ ተደርጎ ይወሰዳል። የመጀመሪያውን ጉባኤ ባካሄደበት ወቅት የፓርቲው የሕዝብና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ዘርፍ ኃላፊ ዶክተር ቢቂላ ሁሪሳ ኢትዮጵያዊያን በአንድ ጥላስር፣ አንድ ፓርቲ ሆኖ ሕብረ ብሄራዊነት አቅፎ የኢትዮጵያ አንድነት መሰረት በማድረግ ለመጀመሪያ ጊዜ በአንድ ወጥ ፓርቲ ደረጃ ጉባዔ ማካሄዱን በታሪካዊነቱ ነው የገለጹት።

ዛሬ ላይ ፓርቲው ማኅበራዊ መሰረቱ እየተጠናከረ መምጣቱ ነው የተገለጸው። ህብረ ብሔራዊነቱ የሚፈጥረው ወንድማማችነትና እህትማማችነት ኢትዮጵያ የሁሉም መሆኗን ያረጋግጣል የሚለውን እምነት ያጸናል። ለዚህም ነው “ብልጽግና ፓርቲ በአገር ጉዳይ በተለይም በፖለቲካው መስክ ተገልለው የቆዩትን ዜጎች በእኩል ተሳታፊ ያደረገ ነው” ሲሉ የመጀመሪያው ጉባኤ ተሳታፊዎች ያረጋገጡት። ፓርቲው በጉባዔው ያደረጋቸው ተግባራት አሳታፊና አካታች አገር የመምራት

ተሳትፎና እድል የፈጠረ መሆኑን ያረጋግጣል የሚል ምስክርነት ሰጥተዋል።

ከጋምቤላ ክልል በጉባዔው ላይ የተሳተፉ የብልጽግና ፓርቲ አባል አቶ ሙሴ ጋጀታ እንደገለጹት፤ ፓርቲው በፖለቲካው መስክ የተገለሉትን ዜጎች እኩል ተሳታፊ ያደረገ ነው።

የእርሳቸውን ሀሳብ በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል የብልጽግና ፓርቲ አባል ወይዘሮ እናትነሽ ማሩ እና ከደቡብ ምዕራብ ክልል የብልጽግና ፓርቲ አባል አቶ ፀጋዬ ማሞ ይጋሩታል። እንደነርሱ እምነት ጉባዔው “አሳታፊና ልዩ ነው።”

“የፓርቲው መሪዎች ከመላው ኢትዮጵያ በተሰበሰቡ ጉባዔተኞች መመረጣቸው አሳታፊነቱንና ፍትሃዊነቱን ያሳያል” በማለት ነው አቶ ፀጋዬ የገለጹት።

ከሀረሪ ቅርንጫፍ የመጡት የብልጽግና ፓርቲ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባል አምባሳደር ነቢል መኸዲ “ቀድሞ አጋር ተብለው ተመልካች ብቻ የነበሩት ፓርቲዎች አሁን ላይ በአገራቸው ጉዳይ እኩል ተሳትፎ እያደረጉ ነው” ብለዋል።

ብልጽግና በአሳታፊነት፣ በአካታችና በፍትሃዊነት በኩል በልዩነት የመጣ፣ ለኢትዮጵያ የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ትልቅ መሰረት የጣለ ፓርቲ መሆኑን ነው እማኝነት የሰጡት። ይህም የመደመር መንገድን በተግባር መተርጎሙን ያንጸባረቀበት መገለጫው ነው።

በተግባር የሚፀና ቃል ብልጽግና እስካሁን ባደረጋቸው ጉዞዎች የገባቸውን ቃል በተግባር እየፈፀመ መምጣቱን አባላቱ እማኝነት ይሰጣሉ። ምንም እንኳን በፈተናና ተግዳሮት በርካታ ውጣ ውረዶችን ቢያልፍም፣ ዳገትና ቁልቁለቱ ቢበዛበትም ለሕዝቡ ቃል የገባውን ለመፈጸም ሲተጋ የቆየ ፓርቲ መሆኑን ነው ምስክርነት የሚሰጡት። እስከአሁን ያከናወናቸውን መልካም ነገሮች ይዞ በቀጣይ ብዙ ስራዎችን ለማከናወን ዳግም ቃል ገብቷል።

“የኢትዮጵያን የብልጽግና ጉዞ እውን ለማድረግ ገዢ ሀሳብ ይዘን በትጋት መስራት ይጠበቅብናል” በማለት የፓርቲው ፕሬዝዳንት ዶክተር ዐብይ ያስተላለፉት መልዕክት የፓርቲው አባላት መላውን ህዝብ ከጎናቸው አድርገው ገዥ ሃሳብ በማመንጨት ያለምንም እረፍት መስራት እንደሚጠበቅባቸው የሚያሳስብም ነው። ፓርቲው በልዩነት ለመውጣትና ኢትዮጵያ የሚመጥናትን ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ለውጦች ለማስመዝገብ በአዳዲስ አስተሳሰቦች ቀድሞ መገኘት ጊዜው የሚጠይቀው ጉዳይ ነው።

በአሁኑ ወቅት በአገሪቷ የሚታየው የሰላምና ደህንነት እጦት ጉዳይ፣ የኑሮ ውድነት፣ የመልካም አስተዳደር ችግርና አፍጦ የሚታይ ሌብነት በበሰለ መንገድ መፍታት እንደገዥ ፓርቲነቱ የብልጽግና የቤት ስራ ነው። ይህ ደግሞ አባላቱ በአስተሳሰብ ልቀው፣ በመልካም አፈጻጸም

(ፍቶ ክሬዲት ጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት)



24

ጎልተው በመውጣት ግንባር ቀደም የመሆን ጉዳይ ጊዜ የሚሰጠው አይደለም።

“ዘላቂ ሰላምና የዜጎችን መረጋጋት ለማረጋገጥ ከምንም ጊዜ በላይ ፓርቲው 24 ሰዓት ሊሰራበት እንደሚገባ፣ አመራሩም የቅድሚያ ቅድሚያ በመስጠት የዜጎችን ሰላምና መረጋጋት ማረጋገጥ ላይ ያለምንም እረፍት መስራት እንዳለበት ወስኗል። በዚህም በአሁኑ ሰዓት በተለያዩ የአገራችን አካባቢዎች ጽንፈኝነት፣ አክራሪነትን መሰረት በማድረግ እየታዩ ያሉ የዜጎች መፈናቀል መቆም እንዳለበት፣ አመራሩም ለዚህ የሚያስፈልገውን እቅድ አውጥቶ በትኩረት መስራት እንዳለበት ከስምምነት ተደርሷል” በማለት ነው ዶክተር ቢቂላ የመጀመሪያው ጉባዔ ተሳታፊዎች የወሰኑትን የገለጹት።

ዘላቂ ሰላምን ለማረጋገጥ የሁሉም ዜጎች ተሳትፎ ያስፈልጋል። በየአካባቢው የሚደረጉ እንቅስቃሴዎችን በማየት ፈጣን መፍትሄ የመስጠት፣ የዜጎች ሕገ መንግሥታዊ መብቶች እንዳይጣሱ የመስራት፣ የዴሞክራሲና ሰብዓዊ መብቶች ጉዳይ ላይ ትኩረት ሰጥቶ በጥበብ መራመድ ከገዥው ፓርቲ ከፍተኛ አመራር አባላት፣ ከአባላትና ከደጋፊዎች የሚጠበቅ ነው። ፓርቲው በጉባዔው ላይ ይህን ውሳኔ ሲሰጥ ከላይ እስከታች ያሉት አመራር አባላቱ ለዚህ ጉዳይ ተፈጻሚነት መስራት ይጠበቅባቸዋል፤ በዘርና በብሔር ጥላስር ለመደበቅ እድል ፈንታ ሊኖራቸው እንደማይገባ አፅንኦት ተሰጥቶታል።

“በብሔር አጀንዳ ተደብቀው የዜጎችን ሰላምና ደህንነት የማያስጠብቁ አመራሮች ከተጠያቂነት ማምለጥ

አይችሉም” በማለት የብልጽግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዝዳንት ደመቀ መኮንን ጠንከር ያለ መልዕክት ማስተላለፋቸው የፓርቲው ውሳኔ በተግባር የሚተረጎም ቃል መሆኑን ያረጋግጣል።

በኢትዮጵያ ዘላቂ ሰላም ለመፍጠር ህብረ ብሔራዊ አንድነትና ወንድማማችነት የማጎልበቱ ጉዳይ ጊዜ የማይሰጠው መሆኑን የፓርቲው ጉባዔተኞች አጽንኦት የሰጡት ነው። “ዜጎች በማንነታቸው እና በብሄራቸው ተለይተው የሚገደሉበት፣ የሚፈናቀሉበትና ሀብት ንብረታቸው የሚያጡበት ሁኔታ ለመጨረሻ ጊዜ ማስቆም የሚያስችል የፓርቲ አደረጃጀት ተፈጥሯል” በማለት ነው ምክትል ፕሬዝዳንቱ ያስታወቁት።

የዘላቂ ሰላም ጉዳይ መፍትሄ እንዲያገኝ የተደረገውን ትኩረት ያህል የኢኮኖሚ ችግሮችና የኑሮ ውድነትም ዋና መነጋገሪያ አጀንዳ አድርጎታል የመጀመሪያው ጉባዔ።

“የአገር ኢኮኖሚ የሥርዓት ችግር አለበት። ከዚያ የሚመነጭ የዋጋ ንረት ዜጎችን እየፈተነ በመሆኑ ማስተካከል ይገባል። በኢኮኖሚ መዛባት ዜጎችን እየፈተነ ያለውን የኑሮ ጫና መቋቋም በሚያስችል ደረጃ ጥብቅ እርምጃ መውሰድ አለብን” በማለት ዶክተር ቢቂላ የጉባዔተኛውን አቋም ገልጸዋል።

ብልጽግና ፓርቲ በኢትዮጵያ አዲስ መንገድ ጀምሯል። እውነተኛ መከባበር እንዲኖር፣ ዜጎች በእውቀትና በምክንያት የሚያምኑ እንዲሆኑ፣ ተቃውሟቸውን በበሰለና በአመክኖይ ላይ እንዲመሰረት የመደመር እሴት መሰረት እየጣለ ነው። ወንድማማችነትና እህትማማችነት

እንዲጎለብት፣ የጥላቻ ትርክት ቀርቶ በመከባበር ላይ የተመሰረተ ግንኙነት እንዲፈጠር፣ አብሮ የመኖር እሴት ተመልሶ እንዲጎለብት የበኩሉን ድርሻ እንደሚወጣ በተግባር የታየ እንቅስቃሴ እያደረገ ይገኛል። ለዚህ ግን የፓርቲው ከፍተኛ አመራሮች እና አባላት ድርሻቸው ላቅ ያለ ነው።

ዶክተር ቢቂላ እንደሚሉት፤ ፓርቲው ጠንካራ አመራር መገንባት ዋነኛው ጉዳይ ነው። የሀሳብ አንድነት ያለው፣ የተግባር አንድነት ያለው፤ በጋራ ሊራመድ የሚችል፣ የጋራ አገራዊ ራዕይ የሚጋራ ማንኛውንም መስዋዕትነት ከፍሎ የሚታዩትን ችግሮች ብቻ ሳይሆን ወደፊት የሚጠብቀውን ሁለንተናዊ ብልጽግና የማሳካት ኃላፊነት እውን ሊያደርግ የሚችል ጠንካራ አመራር መፍጠር የፓርቲው መለያ ሊሆን እንደሚችል ነው ያረጋገጡት።

ገዥው ፓርቲ የመጀመሪያውን ጉባዔ ሲያካሂድ በአገር ደረጃ በመሰረታዊ ጉዳዮች ላይ ቃል የገባባቸውን ጉዳዮች በተግባር የመተርጎም ኃላፊነት አለበት። በተለይም የዴሞክራሲ ስርዓቱን የማስፋት፣ የሕዝቡን መሰረታዊ ችግሮች የማቃለል፣ የዲፕሎማሲ ስራዎችን በማዘመንና በመለወጥ የኢትዮጵያን ክብርና ጥቅም በተግባር የማስጠበቅ ጉዳይ ላይ ሰፋፊ ተግባራት ለማከናወን የገባውን ቃል በፍጥነት ማከናወን ይጠበቅበታል።

ሌብነትን የማይሸከም ሥርዓት መገንባት፣ ዜጎችን ለእንግልት የሚዳርጉ አገልግሎት አሰጣጦችን መቀየር፣ በአቋራጭ መክበር የሚፈልጉትን መታገል የብልጽግና ቀዳሚ ተግባር ነው።



25

“ዜጎች የሁለንተናዊ ብልጽግና ተጠቃሚ ለማድረግ የፓርቲው አመራር አባላትና አባላት በቁርጠኝነት እንዲሰሩ አቅጣጫ ተቀምጧል” በማለት ዶክተር ቢቂላ ለመገናኛ ብዙሃን በሰጡት መግለጫ ያነሱት ሀሳብ ለሁሉም ከፍተኛ አደራና የቤት ስራ እንደተጣለባቸው ያረጋግጣል።

ከብልጽግና ፓርቲ ሕዝብ ብዙ ይጠብቃል። ለዚህም በመጀመሪያው ጉባኤ ላይ ቃል የገባውን በተግባር መቀየር ግድ ይላል። በኢትዮጵያዊ መልክ 225 አባላት የተመረጠለት ማዕከላዊ ኮሚቴም ሆነ ከዚህ መካከል የተመረጡት 45 ሥራ አስፈጻሚዎች ጉባዔው የሰጣቸውን ኃላፊነት በጠንካራ አመራር በብቃት መወጣትና የብልጽግናን ጉዞ የተሳካ እንዲሆን የማድረግ ግዴታ ተጥሎባቸዋል።

“የአገር አንድነትን ለማስጠበቅና የማኅበረሰቡን ሰላም ለማረጋገጥ እስከ መስዋዕትነት ለመውስድ የታየው

አቋም ከጉባዔው ሲጠበቅ የቆየ በመሆኑ ለተግባራዊነቱ የፓርቲው አመራሮችና አባላት እንዲሁም ማህበረሰቡ ተገቢ ድርሻቸውን ሊወጡ ይገባል” ሲሉ አንጋፋው ፖለቲከኛ አቶ ሌንጮ ለታ ሰሞኑን የገለጹት ሀሳብ ከፍ ያለ ትርጉም አለው።

ብልጽግና የመጀመሪያ ጉባዔ የወሰነውንና ቀጣይ አቅጣጫዎች ላይ በዚህ ወር ሕዝቡ መወያየቱ ማኅበረሰቡ የበኩሉን ድርሻ ለመወጣት እንዲችል ያደርገዋል። ፓርቲው ወደ ህዝቡ በመውረድ ጉድለቶችንና ችግሮችን ሰምቶ መፍትሄ ለመስጠት ይቻላል። በአንዳንድ አካባቢ የሚታየውን ለማህበረሰባዊ ትስስር አሉታዊ የሆኑ አስተሳሰቦችን ለመግታት ያስችላል። “የአግላይነት፣ ጽንፈኝነትና መገፋፋት ሃሳቦችን በማስወገድ ለኢትዮጵያ ሁለንተናዊ እድገት በትብብር መስራት ያስፈልጋል” የሚለውን የፓርቲውን ሀሳብ ያጸናል።

ብልጽግና ፓርቲ “ከፈተና ወደ ልዕልና” የሚለውን መርህ በተግባር የመተርጎምና ውጤት የማስመዝገብ ጉዞውን ጀምሯል። በርካታ ፈተናዎች ከፊቱ አሉ። በህብረ ብሔራዊ አንድነትና ጥበብ በተሞላ አካሄድ ፈተናዎቹን በማለፍ ልዕልና ለማግኘት “አሁን ነገ ነው” በሚል የጊዜ የለንም አስተሳሰብ መንቀሳቀስ ግድ ይለዋል።

ብልጽግና ፓርቲ በአገራችን ከአሉ ተፎካካሪ ፓርቲዎችም ጋር ግንኙነት በመፍጠር እንደአገር ያሸነፈበትና ህዝቡ

የመረጠው ፖሊሲ እውን እንዲሆን በአዲስ አጋርነት አዲስ ባህል መፍጠር ይጠበቅበታል። ስልጣን ማገልገያ መሆኑን በተጨባጭ በማሳየት ኢትዮጵያዊ ህብረ ብሄራዊ አንድነት እንዲጠናከር በማድረግ የአገራችን ህዝቦች ተስፋ በፓርቲዎችና መንግስታት መለዋወጥ የማይጨልም፣ ይልቁንም ወደ ብርሃንና ብልጽግና የሚወስድ እንዲሆን ለማድረግም ከፍተኛ ኃላፊነት አለበት።

ብልጽግና ፓርቲ “ከፈተና ወደ ልዕልና”

የሚለውን መርህ በተግባር የመተርጎምና ውጤት

የማስመዝገብ ጉዞውን ጀምሯል።

(ፍቶ ክሬዲት ጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት)



26

ማህበራዊ

አርበኝነት በዕይታዊ ጥበብ መነጽር



27

በአየለ ያረጋል

መንደርደሪያ

ዕይታዊ ጥበብ ይሰኛል- ስዕል። ስዕል ‘ተናግሮ አናጋሪ’ ጥበብ ነው። የሰው ልጅ ሰዋዊ ክዋኔው፤ ኑባሬ፣ ታሪኩና ተስፋ በዕይታዊ ጥበብ ይተረጎማል። ታሪክ እንደሙዚቃ፣ እንደ ስነ ጽሑፍ ሁሉ በዕይታዊ ጥበብም ይሰነዳል። ታላቁ ሊቅ አለቃ ኪዳነወልድ ክፍሌ ስዕል ሲፈቱት ‘ካለመኖር ወደ መኖር ማምጣት፣ መተርጎም፣ ማተት” ይሉታል። ዕውቁ ሰዓሊ አለ ፈለገሰላም “ስዕል ትምህርት ስነ-ፍጥረትን አጥኚ ሆኖ የራሱን ስሜት እየፈጠረ በቀለምና በልዩ ልዩ መሳሪያዎች ከጠፍጣፋ ቁስ ላይ ሰርቶ ማውጣት… በሐውልት ደግሞ ሀሳቡን ከጠፍጣፋ ነገር ፈንታ ጠንካራ አካል ላይ በድንጋይ፣ እንጨት፣ ነሀስ… ቅርጽና መልክ ለይቶ ማውጣት” በማለት ያትቱታል። ሌላው የስዕል ጠቢብ ገብረ-ክርስቶስ ደስታ ደግሞ “ስዕል ሀሳብ ነው። የአንድ ነገርና ሁኔታ ትርጉምና ስሜት ነው። ዓለማዊና ዘላለማዊ ነገሮችን መተረጎም፣ በዐይን የሚታይ፣ የቀለም፣ የመስመርና ቅርጽ ሙዚቃ ለመፍጠር ይጥራል” ሲል ይገልጸዋል። ለዕይታዊ ጥበብ ሃሳብ፣ ቁስና ጠቢብ እንዳለ በሁሉም ሊቃውንት ሀሳብ ውስጥ ይንጸባረቃል። ስዕል እንደ ሙያዊ ጠባዩ፣ በከያኒው ምርጫ ወይም የአሳሳል ጥበብ ይተረጎማል።

በእርግጥም ስዕል የሰዓሊውን የምናብ ከፍታ፣ የተመስጦ ጥልቀት፣ ሙታንን ሕያው አድርጎ የማሳየት አቅም ያጎላል። ለዚህም ይሆናል ገጣሚና ጸሐፊ ተውኔት አያልነህ ሙላቱ ከመሬት ወደ ጨረቃ ዝና እና ስራቸው

አርበኝነት በዕይታዊ ጥበብ መነጽር



28

የናኘውን ርዕሰ ጠበብት ‘እጅግ የተከበሩ የዓለም ሎሬት ሜትር አርቲስት አፈወርቅ ተክሌ’ን የጠቢብነት ጥግ ለማሳየት አድናቆቱን እንዲህ የገለጸው።

“እግዚአብሔር አርቲስቱን ፈጠረ፤ አርቲስቱ ቀለማትን ቀመረ

ከዚያም ሸራውን ወጠረ፤ ተፈጥሮን ደግሞ ፈጠረ

ሰውን ደግሞ ፈጠረ፤ ኩራተ ርዕሱንም ፈጠረ

እውነትም አፈወርቅ ትንሽ ፈጣሪ ነበረ፤ አልፋ ኦሜጋም ነበረ”

የስዕል የት-መጣነት/Origin/

የኪነት ፅንሰትና ፍልቀት ከሰዋዊ የሕይወት መስተጋብርና አምልኮ ጋር ይቆራኛል። የኪነት ፅንሰት ጅማሮ ሰው የሕይወቱን ኑባሬ፣ ጸሎቱና ረቂቅ አማልክቱን በተመስጦና በውበት ለመግለጽ፣ በተዳሳሽ ምስሎች ለመወከል በመሻቱ ይመሰላል።

በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የአለ ፈለገ-ሰላም የሥነ-ጥበብና ዲዛይን ትምህርት ቤት ዳይሬክተር አገኘሁ አዳነ ፍኖተ- ስዕልን ከሰው ልጅ ዕድገት ጋር ያዛምደዋል። ዕይታዊ ጥበብን ከሰው ‘ሰውነት’/ሕልውናው ጋር ያቆራኘዋል። ‘ከዚህ እስከ እዚህ‘ ተብሎ በ‘እስከ’ አጥር የማይከለል ‘እስከ አልባ’ ያደርገዋል።

የስዕል ጥበብ የትመጣነት በጥንተ ነገር ሰው ታሪኩን ከመሰነዱ፣ በቋንቋ ከመግባባቱ ቀደም የተግባቦቱ መሳሪያ ነው። የቋንቋ ኪነ-ጽሕፈት ሲጀመር፤ ፊደል ሲፈጠር እርሾው ስዕል ነበር። ሰው ጎጆ ሳይቀልስ፣ ለእርሻ ሥራ በሬን ሳያጭ፣ ማረሻውን ሳያሾል ገና ዋሻ ለዋሻ ሲሽሎከሎክ እርስ በርስ ለመግባባት ቋጥኝ ላይ ሲስል ነበር።

ስዕል ውስብስቡን ለመግለጽና ለመተርጎም ተመራጭ ጥበብ ነው። የፊደላት ፍጥረት ተፈጥሯዊ ቅርጾች/ ፎርሞችን መሰረት ያደረገ ነው። ከዚህ ጽሑፍ ገጣጥመው በማንበብ መልዕክት እንዲረዱ ያስቻልዎ ፊደላት ምንጫቸው ተፈጥሯዊ ጉዳዮች ናቸው። እናም የኪነ- ጽሕፈት ምንጩ ስዕል ነው። በማኅበራዊ ብያኔው በሰው ልጅ ማኅበራዊ ሕይወት የዘመን ዑደት እይታዊ ጥበብ አለ። ስዕል እውቀት ሆኖ እየዳበረ፤ ሰውን እያስተማረ፤ ዓለምን እየሄሰ ተራምዷል።

ስዕል በሃይማኖታዊ ዐውዱ በቤተ-አምልኮ መድረክ ጉልበቱ ኃያል ነው። የህቡዕ ወይም ስዉር እና ዲበ አካላዊ ዓለማትን ወደ ተጨባጭነት አምጥቷል። በዲበ አካላዊ ዓለም ስዕል ለግሪክ፣ ግብጽ፣ አክሱማዊያንም ሆነ

ለሌሎች ጥንተ ስልጣኔዎች አስኳል ነው። በጥንታዊ ቤተ መቅደሶች ከቅርስነት ባሻገር የዕይታዊ ጥበብ ውጤት ናቸው። ምዕመኑን ለማስተማር፣ ምዕናባዊ ዓለምን በገሃድ በመወከል ተኪ-አልባ ነው። ጥንታዊያኑ የቤተ- እምነት ስዕሎች ቁሳዊ፣ ባሕላዊ ዓለምን በመግለጥ፣ በማስተማር፣ በእውቀት ዘርፍ በመጠናት ለአዕምሯዊ ልማት አስተዋጽኦው ጉልህ ነው። በአገኘሁ ትንታኔ ጥንታዊያን ቤተ መቅደስ ስዕሎች ከዲበ- አካላዊነት ባሻገር ሴኩላርነትንም/ዓለማዊ አንድምታ/ አንጸባራቂ ናቸው። የሰው ልጅ ፍላጎቶች፤ የእምነት ተቋማቱ ተጠየቅ በቤተ መቅደሶቹ ግድግዳ ላይ ተንጸባርቀዋል። ለዚህ አስረጂ የሚሆን አንድ ምሳሌ ማንሳት ይቻላል። በዘመነ መሳፍንት መገባደጃ ቋረኛው ካሳ/ዓፄ ቴዎድሮስ ድል አድርጎ ካስገበራቸው አካባቢዎች አንዱ የጎጃም መስፍን የነበሩት ደጃዝማች ጎሹ ዘውዴ ከተማ ደንበጫ ሚካኤል በደረሰ ጊዜ የመላዕክት እና የመስፍኑ ስዕል ጎን ለጎን ተስሎ በማየቱ ክፉኛ መንቀፉን ሰዓሊው አለቃ ተክለየሱስ ዋቅጅራ በታሪክ መጽሐፋቸው አስፍረዋል። ይህ ታሪካዊ ሁነት በቤተ ክርስቲያን ስዕላት ከመለኮታዊ ትዕምርትነት ባለፈ ወደ ዓለማዊ ፍላጎቶችም እንደተንጸባረቁ በጥቂቱ ያሳያል።

በዘመናዊነትና ቴክኖሎጂ ረገድም የስዕል ጥበብ ሚና በቀላሉ አይገለጽም። ስዕል የሰው ልጅ የዕለት ተዕለት ሕይወት ጉዳይ ሆኖ እስከዛሬ ዘልቋልና ከቤተ-አምልኮ እና ቤተ መንግሥት ተሻግሮ የሰዋዊ ፍላጎት ማንጸባረቂያም ነው። ፈተናዎችን ጥሶ፣ ዳፋዎችን አራግፎ የስልጣኔው ዓምድ ሆኖ ቀጥሏል። ኪነ-ጥበብ አምላክ ሰውን ከአፈር፣ ከውሃ፣ ከእሳትና ከነፋስ ሲፈጥር ገና ከዘ-ፍጥረት የጀመረ እንደሆነ የሚገልጸው አገኘሁ፤ “በሳይንስና ቴክኖሎጂ ዐውድም ኪነ-ጥበብ የሌለበት አጋጣሚ የለም” ባይ ነው።

ሰው ራሱ የጥበብ ውጤት ሲሆን የሰው ፈጠራዎችም ያው የጥበብ ውጤቶች ናቸው። ኪነ ጥበብ እና ሳይንስ ኢ-ተነጣጣይነት የስልጣኔ ውጤት የሆኑ ቴክኖሎጂዎች የኪነ ጥበብ አሻራ ያረፈባቸው እንዲሆኑ ያስገድዳል። ረቂቅ የቴክኖሎጂ ውጤቶች ከሰው ልጅ እንቅስቃሴና ተፈጥሮ የተቀዱ በመሆናቸው ከሰው ልጅ አፈጣጠር ጋር ያገናኛቸዋል። እነ ሊዮናርዶ ዳቪንቺ መሰል የዓለማችን ስመ-ጥር ሊቃውንት ሳይንቲስትም፤ ጠቢባንም ነበሩ። ዘመን አይሽሬዋ ዓለም ያደነቃት፣ የገሃድ ልዕልት መሳይዋ ‘ሞናሊዛ’ ፈጣሪው ዳቪንቺ፤ መሃንዲስም፤ የሂሳብ ሊቅም መሆኑ ደግሞ ይህንኑ አመክንዮውን ያረጋግጣል። እናም የሒሳብ፣ የፊዚክስና ኬሚስትሪ ሳይንሳዊ ቀመሮች



29

ከሥዕል ምናባዊ እሳቤ መንጭተዋል፤ የዛሬ ረቂቅ የቴክኖሎጂ ውጤቶች መሰረት ሆኗል። ኦልቬርና ዊልቨር ራይት አውሮፕላንን በይፋ ከማብረራቸው በፊት ዳቬንቼ የአውሮፕላን ቅርጽ ያለው ባለክንፍ ስለመሳሉ ታሪክ ያስረዳል። ዛሬ ላይ ከየብስ እስከ ሰማይ ዘመን አፈራሽ ተንቀሳቃሽ የቴክኖሎጂ ምርቶች (በሞተር ተንቀሳቃሾች) ሁሉ መነሻቸው ንድፍ/ስዕል ጥበብ በመሆኑ ሳይንስና ጥበብ ኢ-ተነጣጣይ ጉዳዮች ናቸው።

በጥቅሉ በሳይንስም ሆነ በሃይማኖት አንድምታው የጥበብ መጀመሪያ ስዕል መሆኑ ይሆን እንዴ ያሰኛል?

አርበኝነት በዕይታዊ ጥበብ

ኢትዮጵያ በሰው ዘር መገኛነቷ፣ ምድረ ቀደምትነቷ ከታወቀ፤ ዕይታዊ ጥበብ ደግሞ ከሰው ልጅ ሕልውና ጋር ከተሳሰረ ቀደምት ሰዓሊት ናት ማለት ይቻላል። የዋሻ ውስጥ፣ የቤተ ክርስቲያን ግድግዳ ስዕሎቿም አስረጂ ናቸው። በአፍሪካ ብቸኛ ፊደል ባለቤትነቷ (ፊደል የስዕል ውጤት ነውና) ሕያው ምስክር ነው። የሥልጣኔ መጀመሪያና መገለጫ ሥዕልና ቅርፃ ቅርፆች ሲሆኑ፤ ኢትዮጵያም በዕደ ጥበብ ሙያ ፋና ወጊ ናት።

ኢትዮጵያ በሶስት ሺህ ረጅም ዘመኗ አያሌ መከራ እና ጦርነቶች አስተናግዳለች። የመቅደላ ጦርነትና የዓፄ ቴዎድሮስ መስዋዕትነት፤ በዓፄ ዮሐንስ ዘመን የኩፊት፣ የጉራ፣ የጉንደት፣ የዶጋሌ በስተመጨረሻ የሕይወታቸው ፍፃሜ የሆነው የመተማ ጦርነት፣ በዓፄ ምኒልክ የተመራው የአድዋ ጦርነት፣ የጣሊያን ወረራ፣ የኢትዮ - ሶማሊያ ጦርነት፣ ኢትዮ - ኤርትራ ጦርነት፣ የዛሬው የአገር ሕልውና ጦርነት… እልፍ ጀግኖች ለአገር መስዋዕትነት ከፍለዋል።

ስዕል እንደተባለው ታሪክ ሰናጅ መዝገብ ነው። ኢትዮጵያ ጥንታዊትና ባለታሪክ አገር ናት። ለዚያውም የአገር ህልውናና ሉዓላዊነት የማስጠበቅ የጦር አርበኝነት ታሪኳ የገዘፈባት። እናም ኢትዮጵያ እንደ ሌሎች ኪነ-ጥበብ መስኮች የታሪክ ማህደር በመሆኑ የዕይታ ጥበብ መነጽር ማጉላቷ አልቀረም።

ከቅድመ ልደተ ክርስቶስ የንግስተ-ሳባ ወይም የንግስት አዜብ ከአክሱም ወደ ኢየሩሳሌም ጉዞ፣ ላልይበላን መሰል የዛግዌ ነገስታት ጥበብ ከፍታ፣ ከዓፄ ዓምደጺዮን ጀምሮ ያለው የመካከለኛው ዘመን ዓፄዎች ታጋድሎ እንዲሁም ከዓፄ ቴዎድሮስ ጀምሮ ያለው የዘመናዊት ኢትዮጵያ

መልክና ታሪክ በዚህ ዕይታዊ ጥበብ ተንጸባርቋል። ስዕል የሺ ዓመታትን የኢትዮጵያ ጉዞ በመሰነድ፤ በመተርጎም፤ የጥናትና ምርምር ምንጭ በመሆን ሚናውን ተወጥቷል።

በሰው ልጅ ታሪካዊ ኹነቶች አዲስ ምዕራፍ ከፋችነቱ በጉልህ የሚጠቀሰው የአድዋ ድል በፊልም፣ በተውኔት፣ በሥነ ግጥም፣ በቅኔ ወዘተ. እንደተገለጸው ሁሉ ሥነ- ሥዕልም አልዘነጋውም። የድኅረ አድዋ ዕይታዊ ጥበብ ሥራዎች ታሪክ የመተረክ፣ የጀግንነት መልክና ልክ የማሳየት አቅም እንዳላቸው ባለሙያዎች ይገልጻሉ።

ሰዓሊ ተስፋዬ ንጉሴ በአንድ ወቅት ለመገናኛ ብዙሃን በሰጡት ማብራሪያ አድዋ የኢትዮጵያን የስነ ስዕል ታሪክ ከቤተ ክርስቲያንና ክብር መንግሥት መንፈሳዊ ትረካ (spiritual narrative) ወደ ዓለማዊ ትረካ (secular narrative) አሸጋግሮታል። ‘ሥነ መለኮትንና መንፈሳዊነትን ብቻ የሚመረኮዙ ስዕላት ከአድዋ ድል ማግስት የጦርነቱን ገድል የሚዘክሩ፣ ትረካዊ አሳሳል ዘይቤ የቀረቡ ዓለማዊ ስዕላት በቅለዋል’ ይላል።

የቤተ ክርስቲያን ሰዓሊያን አድዋን በመግለጽ ረገድ ጉልህ ሚና እንደነበራቸው የዘርፉ አጥኚዎች ይስማማሉ።



30

ትውፊታዊ ሰዓልያኑ የአድዋውን ድል በሥዕላቸው የዘከሩበት መንገድ ለኢትዮጵያ ባሕላዊ አሳሳል ዕድገት አስተዋጽኦ አድርጓል። በአውሮፓዊያኑ ዘመን አቆጣጠር በ1905 ገደማ ሰዓሊዎች መካከል አለቃ ኤሊያስ፣ አለቃ ኅሩይና ፍሬ ሕይወት ይገኙበታል። ከዘመኑ ስዕሎች መካከል በዓፄ ምኒልክ አማካሪ በነበሩት አልፍሬድ ኢልግ ስብስብ ውስጥ በስዊዘርላንድ፣ የሆልትዝ ስብስብ በበርሊንና የሆፍማን ስብስብ በዋሽንግተን ይገኛሉ። በስዕሉ ከጠቅላይ ጦር አዛዦች ከዳግማዊ ምኒልክና እቴጌ ጣይቱ በተጨማሪ ፊታውራሪ ገበየሁ፣ ራስ መንገሻ፣ ራስ አሉላ፣ ራስ አባተ፣ ደጃዝማች ባልቻ ጎልተው ይታያሉ። የአዝማሪ ፃዲቄ ሽለላና ፉከራ የሚዘክረው ሥዕልም ሌላው ዘመነኛ የጥበብ ትሩፋት ነው።

የዘመናዊት ኢትዮጵያ ስልጣኔ ፈር ቀዳጁ ዳግማዊ ዓፄ ምኒልክ ለኢትዮጵያ ዘመናዊ ስነ ጥበብም በር ከፋች ነበሩ። በኢትዮጵያ የሥነ ስዕል ታሪክ የጎላ አሻራ ባይኖራቸውም አፈወርቅ ገብረ ኢየሱስ (ፕሮፌሰር) ወደ ጣሊያን፣ ተሰማ እሸቴን (ነጋድራስ) ወደ ጀርመን ሥነ ጥበብ እንዲማሩ ልከዋችው ነበር። በቀዳማዊ ኃይለሥላሴም ወቅት አገኘሁ እንግዳ፣ ዘሪሁን ዶሚኒክ፣ ታደገ ደፈርሳ፣ አበበ ወልደጊዮርጊስ የተባሉ ኢትዮጵያዊያንን ለሥነ ጥበብ ትምህርት ፈረንሳይ ልከዋል። ከነዚህም መካከል ዘመናዊ ሥነ-ጥበብ በኢትዮጵያ እንዲስፋፋ የታገለውና

ተከታዮቹን ያፈራው ሰዓሊ አገኘሁ እንግዳ ነው። አገኘሁና ቀደ መዛሙርቱ መንፈሳዊና ዓለማዊውንም ስዕላት አጣምረው ስለዋል። በ1950ዎቹ ደግሞ ገብረክርስቶስ፣ ዘርይሁን የትምጌታ፣ እስክንድር ቦጋሲያን፣ ወርቁ ጎሹ፣ አፈወርቅ ተክሌ፣ ግርማይ ሕይወት እና መሰሎቹ በኢትዮጵያ የሥነ ጥበብ አብዮት አምጥተዋል።

ጀግንነትና አርበኝነት እንደየዘመኑ ዐውድ ተስሏል- ለምሳሌ አድዋ። በአገኘሁ አዳነ ትንታኔ በዘመነ ኃይለስላሴ ስዕሎች ሃይማኖታዊ ጠባይ የተጠናወታቸው፤ በቴክኒክና ይዘት ረገድም ቀደምት ኢትዮጵያዊ አሳሳል /ቤተ መቅደሳዊ/ ፈለግ ያላቸው ናቸው። ስዕላቱ በይዘት ሲፈተሹም አርበኝነት ተጋድሎ ያለመለኮታዊ ተራዳኢነት ድል እንደሌለው ነው። አርበኝነትና መለኮታዊነት ዝምድና ይንጸባረቅባቸዋል።

በደርግ የሶሻሊስት ስርዓተ መንግሥት ዘመን የአርበኝነት ድል ለማግኘት መለኮታዊ ተራዳኢነት የለም። በዓፄ ኃይለሥላሴ ዘመን ሲንጸባረቅ የነበረው መለኮታዊ ተራዳኢነት/ልዕለ ኃይል ተረት አድርጎታል። አድዋም፣ ማይጨው፣ መቅደላም በዕውነታዊነት አሳሳል ዘዬ ተስለዋል። ከሃይማኖታዊ አሳሳል ይልቅ የአውሮፓን እውነታዊ አሳሳል የተከተለ፣ ለማርኪስዝም ርዕዮተ ዓለም ያቀነቀነ፣ የሠራተኛውን መደብ ገናናነትና አሸናፊነት

የሰበከ ነበር። በ1960ዎቹ እና 1970ዎቹም የሰዓሊያኑ አብዛኛው ጭብጥ አድዋ ነበር። በተለይም የአለ ፈለገ- ሰላም የሥነ ጥበብ ትምህርት ቤት ተመራቂ ተማሪዎች በአብዛኛው የምረቃ ስራዎቻቸው በአርበኝነት ላይ ያጠነጠነ ነበር። በዘመኑ አድዋ፣ የማይጨው እና የመቅደላ ታሪኮች ቢሳሉም በአሳሳል ረገድ የስዕል ሥራዎቹ ዘመናዊ የሚሰኘውን የእውነታዊነት /ሪያሊዝም/ አሳሳል ጥበብ የመረጡ ነበሩ።

በዘመነ ኢህአዴግ ስዕሎች በነፃ ገበያ ስርዓት ውስጥ በማለፋቸው ዕለታዊና ዘወትራዊ ሕይወት ላይ ያጠነጥናሉ። በ1980ዎቹ በብሔር ፌዴራሊዝም የአርበኝነት (patriotism) ትረካ ጭብጥ ያላቸው ስራዎች ተመናምነዋል። በዘመነ ኢህአዴግ የአርበኝነት ታሪክ በስዕሎች ቢዘከርም ትኩረቱ የላላ ነበር። በዘመኑ ከአንድነት ይልቅ በሚለያዩ ጉዳዮች ላይ ሲተኮር ከያኒያን አንድነት መንፈስ ለማምጣት ወደኋላ አስታራቂ ሰው ፈልገዋል፤ የአባቶቻችን ልጆች ነን ለማለትም ምኒልክን፣ ቴዎድሮስን ስለዋል። የዘመኑን ከፋፋይ እሳቤ እየተቹ ትናንትን ዋጅተዋል። በብሔር መደራጀትና መከፋፈል ለአገር አንድነት አደጋነቱን ተንብየው ቀደምት አርበኞችን በሸራቸው ላይ አጉልተው ያሳዩ ጠቢባን አሉ።

ዛሬም ኢትዮጵያ እንደ ጠቢባን ተመስጦና መረዳት



31

በዕይታዊ ጥበብ መነጽር መቃኘቷ አልቀረም። በቅርቡ በአዲስ አበባ ባሕል ቱሪዝምና ኪነ ጥበብ አመቻችነት በአዲስ አበባ ሙዝየም ለአንድ ወር የቆየ የስዕል ዐውደ ርዕይ ተከፍቶ ነበር። በዐውደ ርዕዩ ለዕይታ የቀረቡ በርካታ ስዕላት መካከል የአብዛኞቹ ይዘት ትኩረታቸው ጀግንነት እና አርበኝነት ነበር። መልዕክቱም የአገርን ሕልውና ከመታደግ ጀግንነትንና የወገን አለኝታነትን ታሳቢ ያደረጉ ነበሩ። በተለይም ኢትዮጵያ ለገጠማት አሁናዊ የሕልውና ስጋትንና ተጋድሎውን ያጎሉ ጥበባዊ ስራዎች ጎልተው ለተመልካች ቀርበዋል። ይህም የሚያሳየው ኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነት በዕይታዊ ጥበብ የሚገለጽበት የቀደመ የአርበኝነትና ጀግንነት ልክና መልክ በወጣት ሰዓሊያን ዘንድ የተወረሰና የቀጠለ እሴት ስለመሆኑ ነው። አሁናዊ አገራዊ ሁኔታን ያስተሳሰረው ዓውደ ርዕዩ የትናንት ጦርነቶችን ማለትም የአድዋ፣ መቅደላ፣ የመተማ፣ ማይጨው፣ የካራማራ… የአርበኝነት ውሎዎችን ዘክሯል። ስዕሎቹ ዓፄ ቴዎድሮስ ከጎራዴያቸው፣ ምኒልክ ከአባ ዳኘው፣ የነገሥታቱ ጋሻ ጃግሬዎቹ ከነጋሻና ጦራቸው፣ ሴቶች ከነአገልግላቸው ተስለዋል። በጥቅሉ በየዘመኑ አርበኝነትና ጀግንነትን በየዘመኑ ዐውድና ነባራዊ ሁኔታ ተሰንዷል፤ የዘመናቱ መልክና ልክ በዕይታዊ ጥበብ ተዋጅቷል።

መውጫ

ዕይታዊ ጥበብ ለአዕምሯዊ ልማት ይበጃል። ስዕል መልከ ብዙ፤ ፈርጀ ብዙ ጥበብ ነው። ሰዓሊው ከስዕሉ ጋር ለዘላለም አይኖርምና ለትርጉም ይጋለጣል። ለዘርፉ ዕድገት፣ ልምምድና ትምህርት ግን መሪ፣ አራቂና ሃያሲ ያሻዋል። በትምህርት ቤት በስርዓተ ትምህርት ቢካተት ልጆችን ማስተማር ያግዛል። ለሥዕል ብቻ ሳይሆን ለሁሉም የኪነ-ጥበብ ዘርፍ ለማነቃቃት የሥርዓተ ትምህርት ድጋፍ ይሻል። ዕይታዊ ጥበብም በስርዓት ትምህርት ይዘቱ መቃኘት፣ ከመጀመሪያ እስከ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ክበባትን ማቋቋም፤ ምሩቃኑ ውሳኔ ሰጭ አካላት ማካተት፣ ዘርፉን ባለቤት እንዲኖረው ማድረግ ይገባል። የዕይታዊ ጥበብ ባለሙያ በመንግሥት ተቋማት መዋቅር ውስጥ ቢካተት ለከተማ ፕላንና ውበት ስራው ስኬት ቀና የመፍትሄ አካል ይሆናል። የጥበብ ሰዎች የሚፈለጉት የተቃናች አገር ለመገንባት ነው። የተጣመመች አገር ከለማች ግን ዳፋው ብዙ ነው- በአገኘሁ አዳነ እምነት።

ስዕል ጥበብ አይቶ የሚተረጉመው፣ የሚፈታው፣ የሚተነትነው፣ በጊዜው የሚያርቀው ጥበቡን የተካነ በሀሳብ የበለጸገ ሃያሲ ይሻል። ሰዓሊው በፈጠራው ሲያስደምም የነፍሱን መቃተት ለመረዳት ከወደ ሀያሲው የእውቀት ትርጓሜን እንሻለን። ያን የጥበብ ፍልቃቂ የህብረ

ቀለማቱንና የመስመር አጣጣሉን ትርጓሜ የሚነግረን ጉምቱ የጥበብ ሊቅ ፍለጋ ነፍሳችን ትቃትታለች። ኢትዮጵያ እኒህ የጥበብ ሰዎች እንዲበዙላት በትምህር ቤት የመሰጠቱ ጉዳይ የምር ሊሆን ግድ ነው።

በሌላ በኩል ኢትዮጵያ የጥቁር ሕዝቦች ነፃ አውጪነቷ፣ የፓን አፍሪካዊነት አስኳልነቷ፣ የአፍሪካ ሕብረት ራስነቷ… ከምድረ ቀደምትነቷ ጋር ሲጣመር የታሪክ ሰናጅ ጥበብ ማዕከል ያስፈልጋታል። ከታሪክ ማስተማሪያና መዘከሪያ ኪነ-ጥብብ ዘርፎች አንዱ የሆነው በዕይታዊ ጥበብም መስክም ታሪኳን ዘካሪ የስዕል ክምችት ማዕከል መገንባት ታላቅ ጉዳይ ነው። ካልሆነ ግን የኢትዮጵያ ትናንታዊ የሥልጣኔ አብነትነት ዋቢ ጥበብ ሥራዎች ይዳከማሉ። የአገር ትናንታዊ መልኳ፣ የዛሬ ኹነቷና የነገ ትንቢቷ በልክ አይነጸርም።



32

የኢኮኖሚ ለውጡ አንዱ ተስፋ

ዓለም አቀፍ



33

የኢኮኖሚ ለውጡ አንዱ ተስፋ

ኢንዱስትሪ . . .

የምጣኔ ሀብት እድገትን በማፋጠንና ልማትን በማረጋገጥ ለዜጎች የተሻለ ዓለም ለመፍጠር አስፈላጊውን ግብዓት በአንድ ቦታ አሟልቶ የሚመሰረቱ የኢንዱስትሪ መንደሮች ተጠቃሽ ናቸው። ኢትዮጵያም ከጥቂት ዓመታት በፊት ከጀመረችው ሁሉን አቀፍ የእድገት ጉዞ ውስጥ የአምራች ኢንዱስትሪው ድርሻ በምጣኔ ኃብቱ ላይ ያለውን አስተዋጽኦ ማሳደግ ትልቁ ትኩረት አድርጋ እየሰራች ነው። ይህን ለማሳካት በተለያዩ ክልሎች የኢንዱስትሪ ፓርኮች ተገንብተው ወደ ስራ ገብተዋል። ከእነዚህ መካከል የሃዋሳ፣ ቂሊንጦ፣ ድሬዳዋ፣ ደብረብርሃን፣ ጂማ፣ባህርዳር ወደ ስራ ከገቡ 13 የመንግሥት ኢንዱስትሪ ፓርኮች ተጠቃሽ ናቸው።

የኢንዱስትሪ ፓርኮች ግንባታ የኢንዱስትሪ ዘርፉን እድገት በመደገፍ ረገድ ትልቅ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው ይታመናል። በልማት ከፍተኛ ደረጃ የደረሱ የበለጸጉ አገሮች ተሞክሮ የሚያሳየውም ይህንኑ ነው። የኢንዱስትሪ አብዮት ዘመን ዋነኛ መለያ የማምረቻ ኢንዱስትሪ በምጣኔ ሀብት ውስጥ ከፍተኛ ድርሻ መያዝ መቻሉ ብቻ ሳይሆን ለዓመታት መሪ ሆኖ መዝለቁ እሙን ነው።

ኢትዮጵያ ለዘመናት የምጣኔ ሀብት መሰረቷን በግብርና ላይ አድርጋ ቆይታለች። ነገር ግን ለዘላቂ የምጣኔ ሀብት እድገትና ልማት ለማፋጠን ኢንዱስትሪ ዘርፉን ከግብርናው ጋር አጣጥሞ ማስኬድ አስፈላጊ በመሆኑን፣ የግብርና

በጥሩወርቅ አያሌው



34

ምርቶችን እሴት ጨምሮ ለዓለም ገበያ በማቅረብ ገቢን ማሳደግ ልዩ ትኩረት የሚሻ ጉዳይ ሆነ።

ኢትዮጵያ የአምራች ኢንዱስትሪ ውጤቶችን በጥራትና በብዛት በማምረት በምጣኔ ሀብት እድገት ውስጥ ያለውን ሚና ለማሳደግ በማቀድ ለኢንዱስትሪ መንደሮች ልማት መዋለ ንዋይ ማፍሰስ ከጀመረች ዓመታት ተቆጥረዋል። የኢንዱስትሪ ፓርኮች፣ ምርት ለማምረትና ወደ ገበያ ለመግባት የሚያስፈልጓቸውን መሰረተ ልማቶች ያሟሉ ናቸው። መንገድ፣ የኤሌክትሪክ ኃይል፣ ቴሌኮም፣ የፍሳሽ ማስወገጃ ስርዓትና ገንዘብ ተቋማት አገልግሎት፣ የመኖሪያ ቤት፣ መጋዘንና ሌሎች የሠራተኞች አገልግሎቶችን አሟልቶ የያዘ ሰፊ መንደር ነው።

በኢንዱስትሪ ፓርኮች በአምራች ዘርፍ መሰማራት የሚፈልጉ የውጭም ሆኑ የአገር ውስጥ ባለሀብቶች፣ በተናጠል በራሳቸው አቅም ፋብሪካ ለመገንባት የሚጋጥማቸውን እንግልትና ውጣ ውረድ የሚያስቀርና ጊዜ የሚቆጥብ ነው። ይህም የኢንዱስትሪ መር ምጣኔ ሀብት ለማሳካት ሚናቸውን የጎላ ያደርገዋል። ከላይ የተጠቀሱትን አገልግሎቶች በአንድ ቦታ አሟልቶ አለመገኘት የአገሪቷን የማምረቻ ኢንዱስትሪ በሚፈለገው መጠን እንዳያድግ አድርጎት መቆየቱ ለዚህ ዓብይ ምስክር ነው።

የኢንዱስትሪ ፓርኮች እየተስፋፋ መምጣት የአገሪቷ ኢንዱስትሪ ዘርፍ እድገት መሰናክል የሆኑትን ችግሮች የሚያቃልሉ ናቸው። የኢንዱስትሪ ፓርኮች ኢትዮጵያ ለጀመረችው የሕብረተሰብ ምጣኔ ሀብት እድገትና የብልጽግና ጉዞ ስኬት መሰረቶችም ናቸው።

በአሁኑ ወቅት የበለጸገ የምጣኔ ሀብት አቅም ባለቤት በመሆን ዓለምን በፈለጉት አቅጣጫ የሚዘውሩት የአውሮፓ አገሮች የማምረቻ ኢንዱስትሪ በምጣኔ ሀብታቸው ውስጥ የበላይነት መያዝ የጀመሩት ከሁለት መቶ ዓመት በፊት ነበር። እ.ኤ.አ በ1850ዎቹ የእንፋሎት ኃይል ለፋብሪካ ሞተር ከመዋል ባለፈ ለትራንስፖርት፣ ለመርከብና ባቡር ትራንስፖርት፣ ለኤሌክትሪክ ኃይል ምንጭ ጥቅም ላይ መዋሉ የኢንዱስትሪ እድገት እንዲያሳይ አስተዋጽኦ አድርጓል።

ጃፓን በ19ኛው ክፍለ ዘመን የማምረቻ ኢንዱስትሪን በመጀመር ቀዳሚ የእስያ አገር በመሆን ተጠቃሽ ናት። ይህም ሆኖ በ20ኛው ክፍለ ዘመን የማምረቻ ኢንዱስትሪ ወደ ተቀሩት አህጉሮች መስፋፋት ጀመረ። ለአብነት ደቡብ አሜሪካ፣ እስያ፣ አፍሪካ ሊጠቀሱ ይችላሉ። በርግጥ በዚህ ወቅት የደቡብ ምስራቅ እስያ አገሮች የራሳቸውን የኢንዱስትሪ አብዮት አካሂደዋል። አሁን የዓለም ሁለተኛ ግዙፍ ምጣኔ ሀብት ባለቤት የሆነችው ቻይና እና ደቡብ

ኮሪያ በዚህ ወቅት የተፈጠሩ ኢንዱስትሪ መር ሥራዎችን ያከናወኑ ናቸው።

እነዚህን ጅምሮች ስናስተውል የምጣኔ ሀብት እድገትና ልማት ዋነኛ ግብ ለሆነው የኑሮ ደረጃ መሻሻል የኢንዱስትሪ አብዮት ትልቅ አሻራ በማሳረፍ የሕዝብ ገቢ እንዲያድግ አድርጓል።

የኢንዱስትሪ ፓርኮች - በኢትዮጵያ

የኢንዱስትሪ ንቅናቄ ወደ አፍሪካ የመጣው እጅግ ዘግይቶ ነው። አፍሪካን በቅኝ ግዛት ይዘው የነበሩ በኢንዱስትሪ የበለጸጉ የአውሮፓ አገሮችም የአፍሪካን አንጡራ ሀብት መበዝበዝ እንጂ ኢንዱስትሪያቸውን ወደ አህጉሪቷ ለማምጣት አልሞከሩም። ከዚያ ይልቅ አገራቸው ይገኙ ለነበሩ ፋብሪካዎች ጥሬ እቃ ለሚያቀርቡላቸው ድንበር ተሻጋሪ ኩባንያዎች ማዕድን በማውጣት ሥራ የተጠመዱ፤ ሰፋፊ የእርሻ ሥራዎችን በማካሄድ ምርቱን ወደ ተቀረው ዓለም የሚያሻገሩ ናቸው።

እስከአሁን ድረስ “አፍሪካ አሁንም የኢንዱስትሪ አብዮቷን አላካሄደችም” የሚሉ አስተያየቶች ጎልተው ይሰማሉ። አፍሪካዊያን አሁንም ትግላቸው መሰረታዊ ፍላጎታቸውን



35

ከማሟላትጋር እንጂ በዘላቂነት ፍላጎታቸውን የሚሞላ ዘላቂ ምጣኔ ሀብትን በኢንዱስትሪ አብዮት ማምጣት አይደለም። ለዚህም “አካሄዳቸውን መቀየር አለባቸው” የሚሉ የመፍትሔ ሃሳቦችም ይንሸራሸራሉ። ኢትዮጵያም የኢንዱስትሪ አብዮት ከላካሄዱ አገሮች አንዷ ሆና ለዓመታት ቆይታለች።

አፍሪካን ጨምሮ በ1970 እና 1980ዎቹ የተለያዩ አገሮች የኢንዱስትሪ ፓርክ ጽንሰ ሃሳብን መተግበር ጀምረዋል። በኢትዮጵያ ግን የፓርክ ጽንሰ ሀሳብ ገብቶ ገቢራዊ መደረግ ከጀመረ ከሰባት ዓመት አይበልጥም። ለዚህም ነው የኢንዱስትሪ ፓርክ ስኬቶች ከተፈተሹ በእነዚህ ዓመታት የተከናወኑትን በማጤን የሚሆነው።

የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ሳንዶካን ደበበ እንደሚሉት ባለፉት ስድስት ዓመታት ትልቁ ስኬት ተደርጎ የሚወሰደው የኢንዱስትሪ ፓርኮች የፕሮጀክት አፈጻጸም ነው። እ.ኤ.አ በ2015 አብዛኞች የኢንዱስትሪ ፓርኮች ጽንሰ ሃሳብ የተጀመረባቸው ሲሆኑ፤ በ2016 ተጀምሮ ከአንድ ዓመት በኋላ ወደ ስራ የገባው የሃዋሳ ኢንዱስትሪ ፓርክ በሞዴልነት ይጠቀሳል። ከዚህ በኋላ በርካታ ኢንዱስትሪ ፓርኮች ወደ ስራ ገብተዋል።

የኢንዱስትሪ ፓርኮች እንዲያመጡ ከሚጠበቀው ተልዕኮና ግብ አኳያ በርካታ ስኬቶች መመዝገባቸውን ነው የሚጠቅሱት። በከተሞችና በክልሎች ኢንዱስትሪ ፓርኮችን ተከትሎ የሚዘረጉ መሰረተ ልማቶችና የሚፈጠሩ የሥራ እድሎች ተጠቃሽ ናቸው። ኢንዱስትሪ ፓርኮች ዋነኛ ዓላማ አድርገው ከተቋቋሙባቸው መካከል የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት፣ የውጭ ምንዛሬ ግኝት፣ የሥራ እድል ፈጠራ፣ የቴክኖሎጂ ሽግግር ይገኙበታል። በእነዚህ ዓላማዎች ባለፉት ስድስት ዓመታት የኢንዱስትሪ ፓርኮች ከፍተኛ የሚባሉ ግቦችን ማሳካት መቻላቸው ተስተውሏል።

የኢትዮጵያን ምጣኔ ሀብት እድገትና ሽግግር ሊያፋጥኑ የሚችሉ የኢንዱስትሪ ፓርኮች በተመረጡ አካባቢዎች በማቋቋም ውጤታማ የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት በመሳብ ኢንዱስትሪዎችን የማሳደግ ጉዳይ ትኩረት ተሰጥቶት እንቅስቃሴ ተጀመረ። ከዚህ ጎን ለጎን የሥራ እድል መፍጠር፣ የወጭ ንግድ ልማት ማሳደግ፣ የአካባቢና የሰው ደህንነትን መጠበቅንና በቁጠባ መሬትን መጠቀም እንዲሁም የከተሞች እድገት በእቅድና በሥርዓት የመምራትን አስፈላጊነት በመገንዘብ፣ የኢንዱስትሪ ፓርኮችን ለማቋቋም የአሰራር፣ የልማት፣ የአስተዳደርና የቁጥጥር ሥርዓትን ማረጋገጥ የሚያስችሉ የኢንዱስትሪ ፓርኮች የሚመለከት የሕግ ማዕቀፍ ያለውን ጠቀሜታ በመረዳት የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን ከሰባት ዓመታት በፊት ተቋቁሟል።

የኢንዱስትሪ ፓርኮችን መገንባት የኢንዱስትሪ እድገትን ለማፋጠን፣ የአየር ብክለት በአካባቢና በሰው ላይ

የሚያደርሰውን ተጽዕኖ ለመቀነስና የከተሞች እድገት በእቅድና በስርዓት መምራት ማስቻሉ ቀዳሚ ስፍራ ያሰጣቸዋል። እቅድን መሰረት አድርጎ እንደ መንገድ፣ የኤሌክትሪክ ኃይል፣ ውሃ በቀላሉ እንዲያገኙ ለማስቻል፤ የአንድ ማዕከል አገልግሎት እና አስፈላጊ መሰረተ ልማቶች ለማሟላትና ልዩ የማበረታቻ እቅድ ኖሮት ሁሉን አቀፍ የተቀናጀ ፈርጀ ብዙ ወይንም ተመሳሳይነት ያላቸው ኢንዱስትሪዎች በተመጋጋቢነት ለማልማት የተቋቋሙ ናቸው። ልዩ የምጣኔ ሀብት ቀጣና፣ የቴክኖሎጂ ፓርክን፣ ለወጪ ንግድ የሚሆኑ ምርቶች ማቀነባበሪያ፤ የግብርና ምርቶች ማቀነባባሪያ፣ ነፃ የንግድ ቀጣናን እና ሌሎች ተመሳሳይ በኢንቨስትመንት ቦርድ የሚሰየሙትን እንደሚጨምር በኢንዱስትሪ ፓርክ ማቋቋሚያ አዋጁ ላይ ተቀምጧል።

በኢትዮጵያም ከሚገኙት 13 ኢንዱስትሪ ፓርኮች መካከል አስሩ ጨርቃ ጨርቅና አልባሳት ላይ ትኩረት አድርገው እየሰሩ ይገኛሉ። እነዚህ አምራች ኩባንያዎች የስራ እድል ከመፍጠርና የወጪ ንግድ ገቢ ከማስገኘት አኳያ ባለፉት ዓመታት ውጤታማ ስራ ማከናወናቸውን መረጃዎች ያመለክታሉ።

የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ ሳንዶካን እንደሚሉት፤ በአሁኑ ወቅት የመንግሥት፣ የግልና የክልሎች መንግሥታትን ጨምሮ 24 ኢንዱስትሪ ፓርኮች ይገኛሉ። በፌዴራል መንግሥት የተገነቡና የሚተዳደሩ 13 ኢንዱስትሪ ፓርኮች እንዲሁም በክልሎች መንግሥታት የሚተዳደሩና የሚገነቡ ትኩረታቸውን የግብርና ማቀናባበሪያ ላይ ያደረጉ አራት ኢንዱስትሪ ፓርኮች ይገኛሉ። እንዲሁም በባለሀብቶች ተገንብተው ወደ ሥራ የገቡና ግንባታ እያካሄዱ ያሉ መኖራቸው ነው የተገለጸው። በተጨማሪም ኢንዱስትሪ ፓርክ ለመገንባት ጥያቄ ያቀሩቡ ባለሀብቶች አሉ።

በደቡብ አፍሪካ ፕሪቶሪያ ዩኒቨርሲቲ የኢኮኖሚክስ ትምህርት ክፍል ኃላፊና የምጣኔ ሀብት ተመራማሪ ፕሮፌሰር ሙላቱ ፍቃዱ፤ የኢንዱስትሪ ፓርኮች ዋነኛ ዓላማ ምርቶቻቸውን ለአገር ቤት ፍጆታ ከማቅረብ አልፈው ለውጭ ገበያዎች እንዲያቀርቡ የገበያ ትስስር መፍጠር እንደሚገባ ነው አጽንኦት የሚሰጡት።

ፕሮፌሰር ሙላቱ፤ አንድ ፓርክ ሲቋቋም በግብዓት ወይንም በምርት ሽያጭ ከአገር ውስጥና ከውጭ አገር ኢንዱስትሪ ፓርኮች ጋር መተሳሰር ይኖርበታል። ይህም በኢንዱስትሪ አስተዳዳሪዎች አማካኝነት ወይንም በመንግሥት ሊፈጠር ይችላል። የዚህ ዓይነቱ አሰራር “የውጭ ኃይሎች በሚሰጡትና በሚነፍጉት እድል ችግር ውስጥ ከመግባት ይታደጋል” ይላሉ።

የኢንዱስትሪ ፓርኮች አሁናዊ ሁኔታ

በኢትዮጵያ እስካሁን 60 በመቶ መሰረተ ልማቶችን



36

በመገንባትና የኢንዱስትሪ መንደር በመፍጠር ኢንቨስተሮች መዋለ ንዋያቸውን እንዲያፈሱ ተደርጓል። በቀጣይም ባለሀብቶች መምጣት እስከፈለጉና ገበያው እስካለ ድረስ ኢንዱስትሪ ፓርኮች እየተስፋፉ እንደሚቀጥሉ ነው ዋና ስራ አስፈጻሚው አቶ ሳንዶካን የሚናገሩት።

እንደዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ ሳንዶካን ገለጻ፤ ለውጭ ገበያ ከ850 ሚሊዮን ዶላር በላይ ምርቶችን ማቅረብ ተችሏል። ኢትዮጵያ ከውጭም ከውስጥም ጫና ውስጥ በነበረችበት በ2014 በጀት ዓመት የመጀመሪያ ስድስት ወራት በገቢ ደረጃ ከፍተኛ ስኬት ተመዝግቧል። በግማሽ ዓመት ውስጥ 125 ሚሊዮን ዶላር ለማግኘት ታቅዶ ከ104 ሚሊዮን ዶላር በላይ ገቢ መገኘቱን አቶ ሳንዶካን ይናገራሉ። ይህ ውጤት ከባለፈው ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የ25 በመቶ ጭማሪ አሳይቷል። ምርቶችን ለውጭ ገበያ በማቅረብ ገቢ ከማስገኘት ጎን ለጎን ከ80 ሚሊዮን ዶላር በላይ ግምት ያላቸው ከውጪ የሚገቡ ምርቶችን መተካት ተችሏል። ለዚህ ስኬት አንዱ መንስኤ ተደርጎ የሚጠቀሰው በኮቪድ ምክንያት ተቀዛቅዘው የነበሩና በማሽን ተከላ ላይ የቆዩ ባለሀብቶች ስራ መጀመራቸው ነው። በዚህ ወቅት ኮርፖሬሽኑ የማይተካ ሚናውን ተጫውቷል።

በዚህ ዓመት የመጀመሪያው አጋማሽ ለመጀመሪያ ጊዜ ከባለፉት አምስት እና ስድስት ዓመታት ታይቶ በማይታወቅ ሁኔታ ኮርፖሬሽኑ ከፍተኛ ወጪ በመቀነስ ገቢ ለማስገኘት ባደረገው ጥረት ከድጎማ ወጥቶ አትራፊ ሆኗል። በቀጣይ የተፈጠሩ አገራዊ መነቃቃትን በመጠቀም አዳዲስ ባለሀብቶች እንዲመጡ ማድረግ ከተቻለ ኮርፖሬሽኑም እያደገና እየሰፋ እንዲሄድ ቀጥተኛ አስተዋጽኦ ይኖረዋል። ለዚህም የውስጥ የለውጥ ስራዎችን ጨምሮ የተለያዩ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን ነው ዋና

ስራ አስፈጻሚው የሚገልጹት።

የኮርፖሬሽኑ ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ ሳንዶካን እንደሚሉት ከሆነ፤ ለኢትዮጵያ የአግዋ እድል ከመነሳቱ በፊት በ2014 በጀት ዓመት ወደ ውጭ የሚላኩ ምርቶች መጠን ለአጭር ጊዜም ቢሆን እንዲጨምር ሁኔታዎች አስገድደዋል። ለዚህም አግዋ ከመነሳቱ በፊት የገቡ ጥሬ እቃዎች ወደ ምርት ተቀይረው ለአሜሪካ ገበያ እንዲቀርቡ ርብርብ መደረጉ የምርት አቅርቦቱ ለመጨመሩ አንዱ ምክንያት ነው። በቀጣይ ዓመታትም አሁን የተገኘውን ውጤት በማስጠበቅና የምርት መዳረሻዎችን በማስፋት የተሻለ ገቢ ለማምጣት ርብርብ እንደሚያስፈልግ ነው አጽንኦት የሰጡት።

በርግጥም በአጭር ጊዜ ውስጥ ርብርብ ተደርጎ ውጤት ማስመዝገብ ከተቻለ በዘርፉ አስደናቂ ለውጥ ለማስመዝገብ የሚያስችል እምቅ አቅም መኖሩን በግልጽ አመላካች ነው። ይህን አቅም ለመጠቀም እንዲቻል የዘርፉ ባለድርሻ አካላት የሚጠበቅባቸውን አስተዋጽኦ በማድረግ መስራት ይኖርባቸዋል፤ ይጠበቅባቸዋልም።

በአሁኑ ወቅት ለባለሀብቶች ዝግጁ በሆኑ ኢንዱስትሪ ፓርኮች ውስጥ በሚገኙ ያልተያዙ ሼዶች፣ ማንኛውም ባለሀብት በሚፈልገው ዲዛይን ገንብቶ ምርት መጀመር የሚችልበት ከ500 ሔክታር በላይ መሬት ዝግጁ ተደርጓል። “ለም መሬት” በሚባል መሬት ማንኛውም ባለሀብት ወደ ኢንዱስትሪ ፓርኮች በመግባት በሚፈለገው ደረጃ ምርት ማምረት መጀመር ይችላል። ይህም ባለሀብቶች መሬት ለማግኘት ጊዜ ማጥፋት ሳይኖርባቸው በኢንዱስትሪ ፓርኮች መስራት እንዲችሉ ሁኔታዎች መመቻቸታቸው ተረጋግጧል። በተመሳሳይ ለቢሮ የሚውል ከ40 ሺ ካሬ በላይ ቦታ ዝግጁ ሆኗል። እነዚህን ከፍተኛ እድሎች በመጠቀም የአገር ውስጥና የውጭ ባለሀብቶች ሙሉ ለሙሉ ወደ ስራ ሲገቡ ወደ

ውጭ የሚላኩ ምርቶች መጠንና ስብጥር እያደገ፣ የወጪ ንግድ መዳረሻዎች እየሰፉ የአምራች ዘርፉ ምጣኔ ሃብቱን በዋናነት ለመምራት የሚያስችል አቅም ይይዛል ማለት ነው።

የኢንዱስትሪ ፓርኮች የእስካሁን ስኬቶችና ያጋጠሙ ፈተናዎች በቀጣይ ይገመገማሉ ተብሎ ይጠበቃል። አሁን ባለው ሁኔታ ውጤታቸውንም ሆነ ድክመታቸውን ለመገምገም ጊዜው ገና መሆኑን ነው ዋና ስራ አስፈጻሚው የሚያመለክቱት።

በአሁኑ ወቅት ኢንዱስትሪ ፓርኮች ትክክለኛው መንገድ ላይ ይገኛሉ። በዘላቂነት ስኬታማ የሚሆኑበት እድል እንዳለ ማሳያ ውጤቶችን ማየት የተጀመረበት ነው በማለት ዋና ስራ አስፈጻሚው ይናገራሉ።

እንደ ዋና ስራ አስፈጻሚው ገለጻ፤ የኢትዮጵያ ኢንዱስትሪ ፓርኮች ከጊዜ፣ ከመሰረተ ልማትና ከውጤት አኳያ ሲታዩ ተወዳዳሪ እየሆኑ መጥተዋል። የኢትዮጵያ ኢንዱስትሪ ፓርኮች ከፈጠሩት የስራ እድል አኳያ ሲታይ የተሻለ አቅም አላቸው።

በመሰረቱ አንድ የውጭ ባለሀብት በአንድ አገር መዋዕለ ንዋዩን እንዲያፈስ ሳቢ ምክንያቶች መኖር አለባቸው። ከዚህ አኳያ ከታየ በኢትዮጵያ የአገልግሎት ተደራሽነት፣ መሰረተ ልማት፤ ለአሰራር ምቹ የሕግ ማዕቀፎች መኖርና የመንግስት የሕግ ድጋፎች ማመቻቸት ባለሀብቶች እንዲሳቡ አስቻይ ሁኔታዎችን መፍጠሩን ነው አቶ ሳንዶካን ያረጋገጡት።

የእነዚህ ባለሀብቶች አስተዋጽኦ ምርቶችን ወደ ውጪ በመላክ ገቢ እንዲያገኙ ብቻ ሳይሆን የአገር ውስጥ አምራቾችንም እንዲያነቃቁ ይረዳል። በተጨማሪም ባለሀብቶቹ ይዘውት የሚመጡት እውቀትና ቴክኖሎጂን ስለሚያሻግሩ የሚፈጥሩት የሥራ እድል ተደምረው



37

አገራዊ የማክሮ ኢኮኖሚ ግብ ላይ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ይኖራቸዋል። እስከአሁን በኢትዮጵያ የተገነቡ ኢንዱስትሪ ፓርኮች ከላይ የተጠቀሱትን በማሳካት ረገድ መልካም ጅምር ተስተውሏል። በርካታ የሥራ እድል ተፈጥሯል፤ ምርቶችም ወደ ውጭ መላክ ተችሏል።

የሥራ ፈጠራና ኢንዱስትሪ ፓርኮች

ለዜጎች የሥራ እድል ከመፍጠር ጀምሮ አሁን ባለው ሁኔታ የኢንዱስትሪ ፓርኮች ለታዳጊ አገሮች አስፈላጊነታቸው ከፍተኛ ነው። ለዚህም ምክንያቱ ደግሞ አስፈላጊ መሰረተ ልማቶችና አገልግሎቶችን በአንድ ማዕከል በማቅረብ ሀብትን በአግባቡ ለመጠቀም ያስችላሉ።

በአሁኑ ወቅት ለዜጎች የስራ እድል ከመፍጠር አኳያ በቋሚና ጊዜዊነት ከ80 ሺ በላይ የሥራ እድል የተፈጠረ ሲሆን፤ ከ100 በላይ ዓለም አቀፍ ኢንቨስተሮች በኢንዱስትሪ ፓርኮች ውስጥ እንዲያመርቱ አስቻይ ሁኔታ መፈጠሩ ሌላኛው ስኬት ተደርጎ ይወሰዳል።

የሃዋሳ ኢንዱስትሪ ፓርክ በአጠቃላይ ከ60 ሺ በላይ የሥራ እድል ይፈጥራል ተብሎ ይጠበቃል። አሁን ባለው ደረጃ ከ95 በመቶ በላይ ሼዶች በባለሀብቶች ተይዘዋል። በአንድ ፈረቃ ብቻ 35 ሺ ሰራተኞች በመስራት ላይ ይገኛሉ። የፈረቃ ቁጥሩ ቢጨምር ከ60 ሺ በላይ ሰራተኞች መስራት የሚችሉበት እድል መኖሩን ያመለክታል። በሌሎች ኢንዱስትሪ ፓርኮች ያለው ተመክሮም የሚያረጋግጠው ይህንኑ እውነት ነው። አጠቃላይ በኢንዱስትሪ ፓርኮች ደረጃ ከ85 በመቶ በላይ ሼዶች በባለሀብቶች የተያዙ ሲሆን፤ ሙሉ ለሙሉ ማምረት ሲጀምሩ ውጤቱም በዚያው ደረጃ እያደገ ይመጣል።

የገበያ ተደራሽነትና ስፋት

በደቡብ አፍሪካ ፕሪቶሪያ ዩኒቨርሲቲ የኢኮኖሚክስ ትምህርት ክፍል ኃላፊና የምጣኔ ሀብት ተመራማሪ ፕሮፌሰር ሙላቱ እንደሚሉት፤ ኢንዱስትሪ ፓርኮች ለምጣኔ ሀብት እድገት ያላቸውን ፋይዳ ከፍተኛ ነው። ለዘላቂ ምጣኔ ሀብት እድገትና ልማት ፓርኮች ከመቋቋም ባለፈ የንግድና የምርት ትስስራቸውን በዓለም አቀፍ ደረጃ ሊያሰፉ ይገባል። ይህም በዘላቂነት የውጭ ንግድ መዳረሻዎችን ለማስፋትና ኢንዱስትሪ መር ምጣኔ ሀብት ለመገንባት ዓይነተኛ ሚና ይጫወታል።

ኢንዱስትሪ ፓርኮች በአሜሪካ ገበያ የተገኘውን ልምድና ተመክሮ ሌሎች የገበያ መዳረሻዎችን ለማፈላለግ መጠቀም ይገባቸዋል። ለዚህ የእስያ አገሮች ልምድን መቅሰም አስፈላጊ መሆኑን ነው ባለሙያው የገለጹት። ባንግላዲሽ ከኢትዮጵያ የተሻለ ምጣኔ ሀብት ያላት አገር አለመሆኗን በመጥቀስ የምታመርታቸው የሸሚዝ ምርቶች ግን አሜሪካ ውስጥ በጣም ተፈላጊ መሆናቸውን ያወሳሉ። ይህ ብቻ ሳይሆን ደቡብ አፍሪካ ውስጥም በኦልማርትና ሌሎች ግዙፍ የገበያ ማዕከላት ውስጥ ይሸጣሉ።

እንደ ተመራማሪው ገለጻ፤ እነዚህ አገሮች ለውጭ ገበያ የሚያቀርቧቸው ምርቶች ጥራታቸውን የጠበቁ መሆን የዓለም ገበያን ሰብረው ለመግባት ስማቸውንና ተፈላጊነታቸውን አስጠብቀው ለመቀጠል ችለዋል። በተመጣጣኝ ዋጋ አምራች የሰው ኃይልን በመጠቀም ያመረቱትን ምርት በተመጣጣኝ ዋጋ ይሸጣሉ። ይህም ዋጋ በቀነሰ ቁጥር ፍላጎት እንዲጨምር አድርጎላቸዋል። ኢትዮጵያ ከዚህ ልምድ በመውሰድ የጨርቃ ጨርቅና አልባሳት፣ የፋብሪካ ጥሬ እቃዎች፣ ማዕድናትና ሌሎች ጥራታቸውን በጠበቀ መንገድ በማምረት በዓለም ተወዳዳሪ ሆኖ መዝለቅ እንደሚቻል ነው በአጽንኦት ያነሱት።

ኢትዮጵያ ያላትን ምርት በማስተዋወቅ በኩል

የሚጠበቀውን ያህል እየሰራች አይደለም። አገሪቷ ያላትን ተፈጥሯዊ ቡና እንኳን በአግባቡ ማስተዋወቅ ባለመቻሏ የኢትዮጵያ አርሶ አደር ማግኘት የነበረበትን ከፍተኛ ገቢ ማሳጣቱን በቁጭት ያነሳሉ። የኢንዱስትሪ ምርቶችን ጨምሮ ለዓለም በማስተዋወቅ የራሷን ስምና ዝና፣ የተቋም ልዩ መገለጫ የሆነውን መለያ (ብራንድ) መገንባት ያስፈልጋል።

የኮርፖሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ሳንዶካን እንደሚናገሩት፤ ኢንዱስትሪ ፓርኮች ውስጥ ያሉ ኩባንያዎች ገበያቸውን የሚፈልጉት ራሳቸው ናቸው። ይሁን እንጂ ኮርፖሬሽኑ ከኢትዮጵያ እንዲገዙ ገዥዎችን የማሳመንና እምነት የመፍጠር ስራ ያከናውናል።

በአሁኑ ወቅትም የኢትዮጵያን ገጽታ በመገንባት ገዥዎችን በማነጋገር የሚያነሷቸውን ስጋቶች መነሻ በማድረግ የተወሰኑ ማሻሻያዎችን ሲያከናውን መቆየቱን ነው የሚገልጹት። ባለሀብቶች የሚያነሷቸውን ጉዳዮች በመሰብሰብ እስከ ሕግ ማሻሻል የሚያደርሱ ተግባራት እየተከናወኑ ናቸው። የሎጅስቲክስ፤ የኤሌክትሪክ ኃይልና ውሃ መቆራረጥ እንዳያጋጥምና ለተጨማሪ ወጪ ሳይዳረጉ ተወዳዳሪ ዋጋ የሚያቀርቡበትን መንገድ መፍጠር የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ ናቸው። ሌሎች ከወጭ ንግድ ገቢ፣ ግብርናን ለማሻሻል የተጀመሩ ጥረቶች መኖራቸውን ነው የገለጹት።

እንደዋና ሥራ አስፈጻሚው ገለጻ፤ ዘርፉን ቀጣይነት ባለው መንገድ ውጤታማ ለማድረግ ጉምሩክ ላይ ያሉ ለአገርም ለባለሀብቱም እሴት የማይጨምሩና ቀጥተኛ አስተዋጽኦ የሌላቸው አሰራሮችን ለማሻሻል ለውሳኔ ቀርቧል። በባንክ ዘርፍም በተመሳሳይ ውሳኔ የተሰጠባቸውም አሉ።

የተለያዩ አሰራሮች የዘርፉን ትክክለኛ ባህሪ የማያሳዩና ያልተረዱ ሆነው ሲገኙ ማሻሻያ እንዲደረግባቸው



38

ማሰራጨት ተገቢ ነው።

ለዚህም በየዓመቱ ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት በኢንፎርሜሽንና ቴክኖሎጂ ሰልጥነው የሚወጡ ሙያተኞችን በዘርፉ ማሰማራት አንድም የስራ እድል መፍጠር፤ አንድም ከዓለም ጋር እኩል በመሄድ የኢንዱስትሪ መር ግዙፍ ምጣኔ ሀብትን ማፋጠን እንደሚቻል የምጣኔ ሀብት ተመራማሪው አክለዋል።

የምጣኔ ሀብት ባለሙያው አቶ ደረጄ ደጀኔ፤ አገሮች በምጣኔ ሀብት ማደግና ልማት ማምጣት እንዲሁም የዜጎችን ብልጽግና ማምጣት የሚችሉት የማምረት አቅማቸውን በማሳደግ ነው። ምርት ሲያድግ ከአገር ውስጥ ፍጆታ በላይ ለወጭ ንግድም ይተርፋል።

በኢትዮጵያ ሲቪል ሰርቪስ ዩኒቨርሲቲ የኢኮኖሚክስ መምህር አቶ መዚድ ናስር እንደሚናገሩት፤ ኢትዮጵያ በዓለም ገበያ ልታቀርባቸው የምትችላቸው እና ያልተጠቀመችባቸው የግብርና እና ኢንዱስትሪ ውጤቶች አሏት። በዚህም ወደ ውጭ የሚላኩ ምርቶችን በማሳደግ በአውሮፓ፣ በእስያ እና በአፍሪካ አገሮች ያሉ የገበያ አማራጮችን ማስፋት ይገባል። የግብርና መር ወደ ኢንዱስትሪ መር ኢኮኖሚ ለማሸጋገር የሚያስችሉ ስራዎችን በተጠናከረ ሁኔታ የመስራት አስፈላጊነትን ይገልጻሉ። “የምርቶችን የጥራት ደረጃ በመጠበቅ በዓለም ገበያ ተወዳዳሪ ሆነው እንዲወጡ ማድረግ ይገባል” ብለዋል።

ሌላኛው መንገድ

የአፍሪካ እድገት እና ዕድል ድንጋጌ ወይም አግዋ በአሜሪካ የተቀመጠውን መስፈርት የሚያሟሉና ከሰሃራ በታች ለሚገኙ አገሮች ምርቶቻቸውን ከቀረጥ ነጻ ለአሜሪካ ገበያ እንዲያቀርቡ የሚያስችል ዕድል ነው።

አግዋ እንደ አውሮፓዊያኑ በግንቦት18 ቀን 2000 በአሜሪካ ኮንግረንስ የጸደቀ ሲሆን፤ በ2025 ክለሳ ይደረግበታል። ይህ የንግድ እድል ሥርዓት እንደአውሮፓዊያኑ ከ2000 እስከ 2008 እንዲተገበር ታስቦ የተጀመረ ቢሆንም፣ በወቅቱ የአሜሪካ ፕሬዝዳንት የነበሩት ጆርጅ ቡሽ እስከ 2015 እንዲራዘም ፈቅደዋል። በ2015 ላይ ደግሞ ዕድሉ እስከ 2025 እንዲራዘም የያኔው የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ባራክ ኦባማ በፊርማቸው አጽድቀዋል።

በአሜሪካ መንግሥት ችሮታ የቀረበውና አፍሪካን በሚመለከት የአገሪቷየንግድ ፖሊስ አካል የሆነው አግዋ ከሰሃራ በታች ባሉ አገሮች እና በአሜሪካ መካከል የንግድና ኢንቨስትመንት ትስስርን ማበረታታት፤ በአገሮቹ ውስጥ

ያሉ ንግዶችን ለአሜሪካ ኢንቨስተሮች ክፍት ማድረግ እንዲሁም ከሰሃራ በታች ባሉ አገሮች ኢኮኖሚያዊ ማሻሻያን እና እድገትን መደገፍ ቀዳሚ ግቦቹ ናቸው። ኢትዮጵያ ለዓመታት የአጎዋ ተጠቃሚ ሆና ቆይታ ነበር። ምንም እንኳን አጎዋ በመኖሩ የሚጠበቀውን ያህል ተጠቃሚ መሆን ባይቻልም እንቅስቃሴዎች ተደርገው የተወሰነ ውጤት ሲገኝ መቆየቱ አይካድም። በቅርቡ ግን የዚህ እድል መቋረጥ መሰማቱ ሌሎችን እድሎች በማስፋትና ጠንክሮ በመስራት ሌላውን መንገድ የመሞከር አስፈላጊነት በጉልህ ታይቷል። ሲፈልጉ የሚወሰድ ሳይሆን በገበያ መርህ የሚመራ አሰራርን መሰረት ያደረገ የገበያ አማራጭ መፈለግ ግድ የሚልበት ወቅት ነው።

የምጣኔ ሀብት ተመራማሪው ፕሮፌሰር ሙላቱ፤ የኢንዱስትሪ ምርት ውጤቶች የሆኑትን የጨርቃ ጨርቅና አልባሳት ምርቶች መዳረሻ በማስፋት ሌሎች የገበያ አማራጮችን መጠቀም ወሳኝ መሆኑን ያስረዳሉ።

ከቻይና፣ ህንድና ሌሎች እየመጡ ካሉ ኃያላን ጋር የንግድ ልውውጥን ማስፋት እንደ አማራጭ አቅርበዋል። ይህ ብቻም ሳይሆን የአፍሪካ አገሮችን መጠቀም ቁልፍ ጉዳይ ነው። ለዚህም የአፍሪካ ነጻ የንግድ ቀጣናን መጠቀም ሌላኛው አማራጭ ጉዳዮች ናቸው። ለአብነትም ኬንያን በመጥቀስ በአገሪቷ ያለውን የገበያ ክፍተት አጥንቶ ኢትዮጵያ የምታመርታቸውን የተለያዩ የኢንዱስትሪ ውጤቶች ወደ አፍሪካ ገበያ ማቅረብ ይቻላል።

ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ ሳንዶካን እንደሚሉት፤ የአግዋ እድል ከፍተኛ እንደነበር ይታመናል። በተለይም የኢትዮጵያ ኢንዱስትሪ ፓርኮች የሚያመርቱትን ለአሜሪካ ገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ ስለነበሩ የእድሉ መነሳት አሉታዊ ተጽዕኖ እንደሚያሳርፍ አይካድም። ይህም አብዛኛዎቹ ኢንዱስትሪ ፓርኮች በተመሳሳይ ዘርፍ የተሰማሩበት ምክንያት በቀጥታ ከአግዋ እድል ጋር የተያያዘ በመሆኑ የሚከሰት ጉዳይ ነው።

ኢንዱስትሪ ፓርኮች ባለፉት አምስት ዓመታት ባስመዘገቡት ውጤት የአግዋ ተጠቃሚነት ላይ ወደ 70 በመቶ ማምጣት ተችሎ ነበር። በኢንዱስትሪ ፓርኮች ከሚገኙ ግዙፍ አምራቾች ውስጥ ከ80 በመቶ በላይ የሚሆነው ምርታቸውን ለአሜሪካ ገበያ ያቀርቡ ነበር። የአግዋ መነሳት ታክስ ከፍለው እንዲያቀርቡ ስለሚያስገድዳቸው ተወዳዳሪ ዋጋ ለማቅረብ ተጽዕኖ ቢኖረውም “እነዚህ ተግዳሮቶች የሚያስቆሙን አይደሉም” በማለት ነው ዋና ሥራ አስፈጻሚው እምነታቸውን የገለጹት። ኢንዱስትሪ ፓርኮች ውስጥ ያሉ

ሃሳብ የተሰጠባቸው አሉ። መንግስት ጣልቃ እንዲገባ የሚያስፈልግባቸው ነጥቦች በመለየት የሕግ ማሻሻያዎችን፣ ጊዜያዊ ውሳኔዎች በመስጠትና የአሰራር ማሻሻያዎችን በማድረግ የሚመለከታቸው ተቋማት ማድረግ የሚጠበቅባቸውን በብቃት እንዲወጡ ለማስቻል መፈጸም ያለባቸው ጉዳዮች ተለይተዋል። ይህም ኢንዱስትሪ ፓርኮች በውጭ ምንዛሬ ግኝት ተነቃቅተው ሥራቸውን በአግባቡ ለማከናወን ያስችላቸዋል።

የዘርፉን አቅም ለማሳደግ መነሻ ከሚሆኑ መሰረታዊ ነገሮች መካከል መልካም ስምና ዝና፤የተቋም ልዩ መገለጫ (ብራንድ) ልክ እንደ ተሽከርካሪ፣ ቤትና ሌሎች ንብረቶች እሴት ከፍተኛ ሚና አለው። ጥሩ ስም ለማግኘት ጥሩ ስራ መስራት መሰረቱ ነው።

በአሁኑ ወቅት የዓለምን ገበያ የተቆጣጠሩ ምርቶች መለያ (brand) እንደ ኤልጂ፣ ሳምሰንግ፣ ፒሊፕስና ሌሎች ምርቶች ዘንድ የተፈጠረው መልካም ስምና ለበርካታ ዓመታት ይዘውት የቀጠሉት የምርት ጥራት የዓለም ሸማቾች ያለምንም ጥርጣሬ እንዲገዙ አድርጓቸዋል፤ እያደረጋቸው ነው።

የኢትዮጵያን ምርቶች ማስተዋወቅና ጥራት ላይ ትኩረት በማድረግ በዓለም ለበርካታ ዓመታት በገበያ ውስጥ ተፈላጊነታቸውን አስጠብቀው እንደዘለቁ መስራት የማይቻልበት ምንም ምክንያት እንደሌለ የምጣኔ ሀብት ተመራማሪው አጽንኦት ሰጥተውታል።

የገበያ መዳረሻዎች ከጎረቤት አገሮች በመጀመር የአፍሪካ የእርስ በእርስ ንግድን ለማጠናከር የተመሰረተውን ነጻ የንግድ ቀጣናን መጠቀም ይቻላል። አምራች ዘርፉ ምርትን በጥራት፣ በብዛት፣ በተመጣጣኝ ዋጋ ማቅረብ ከቻሉ ኢትዮጵያ የምታመርታቸው ምርቶች ጥራትን ያሟሉ ስለመሆናቸው በምስራቅ አፍሪካና በአፍሪካ በስፋት የሚነገሩ እንዲሁም በዓለም ተደራሽነታቸው ሰፊ የሆኑ ቋንቋዎችን በመጠቀም በማስተዋወቅ መገናኛ ብዙኃን ሚናቸውን ሊወጡ ይገባል።

ባለሀብቶች ማምረት ብቻ ሳይሆን ምርቱ ተጠቃሚው ዘንድ እንዲደርስ ማስተዋወቅም ወሳኝ ነው። ሌላኛው የእድገት ማፋጠን መሰረት የሆነውን ቴክኖሎጂ ዘመን እንደ መልካም አጋጣሚ በመጠቀም በኦንላይን ማርኬቲንግና ግብይትን በስፋት መተግበር ተገቢ ነው። በቀጣዮቹ ዓመታት ዲጂታል ምጣኔ ሀብት የዓለም ትኩረት ነው። ኢትዮጵያም ወደ አሰራሩ መግባት ግድ የሚላት ጊዜ በመሆኑ ኢንዱስትሪ ፓርኮች ያመረቱትን ምርት የሚገልጽ መረጃ ዲጂታል ማርኬትን በመጠቀም



39

ትላልቅ ዓለም አቀፍ ኩባንያዎች ጨርቃጨርቅና አልባሳት ላይ ትኩረት ማድረጋቸው፣ ተቀባዮችም ተመሳሳይ ምርት የሚገዙ መሆናቸው ጊዜያዊ ተጽዕኖ አለው።

ኩባንያዎች ላይ ጫና የሚፈጥሩና ማሻሻያ የሚጠይቁት አሰራሮችን ለመንግሥት በማቅረብ ውሳኔ እየተጠበቀ ሲሆን፤ የአግዋ እድል መቋረጥ በወጪ ንግድ ላይ ለጊዜው የፈጠረው አሉታዊ ጫና እንደ ትልቅና ብቸኛ አማራጭ መወሰዱ ነበር። ቀደም ብሎ የምርት ስብጥር አለመኖር፤ የምርት መዳረሻ አለመስፋት ጫናውን የከፋ ማድረጉን አልሸሸጉም። ነገር ግን በመንግሥት በኩል ስትራቴጂ ለመፈተሽ፤ የፓርኮችን ልዩነት ለማየት፤ የምርት ተለያይነትን ለመፍጠር፤ የአገር ውስጥ ባለሀብቶች ወደ ፓርኮች እንዲገቡ እድል ለመፍጠርና ተያያዥ ጉዳዮችን በቀጣይ ትኩረት እንዲያገኙ ለማድረግ እድል ፈጥሯል።

ኩባንያዎቹ ከመንግሥት የሚጠብቁትን ድጋፍ በማሻሻል፤ ላልተገባ ወጪ የሚዳርጉ ጉዳዮችን በመቀነስ ምርታቸውን ማስቀጠል ይገባል። ለዚህም ኮርፖሬሽኑ ጥናት አካሂዷል። ሌሎች የመንግሥት ተቋማትም በተመሳሳይ በሰፊው አጥንተው ለመንግሥት በማቅረብ ውጤት እየተጠበቀ ነው። ተጽዕኖውን ለመሻገር በምርት ላይ የሚገኙ ኩባንያዎች እንዲዘልቁ አዳዲሶችም ወደ ኢንዱስትሪ ፓርክ እንዲገቡ አስቻይ ሁኔታዎችን ለመፍጠር አሰራርና የሕግ ማሻሻያዎች ይደረጋሉ።

የምጣኔ ሀብት ምሁሩ ዶክተር ስሜነህ በሴ እንደሚናገሩት፤ ኢትዮጵያ በአግዋ ታገኘው የነበረውን የኢኮኖሚ ተጠቃሚነት ለማካካስ ምርትና ምርታማነትን ማብዛትና አማራጭ የገበያ መዳረሻዎችን ማስፋት ይኖርባታል። በአገር ውስጥ ምርትን በስፋት ለገበያ ማቅረብ እንዲሁም በአፍሪካ ነጻ የንግድ እድሎች በስፋት ተጠቃሚ ለመሆን መስራት ይገባል።

በሌላ በኩል በየጊዜው እያደገ የመጣው የቻይና አፍሪካ የንግድ ትብብር ለአፍሪካዊያን የገበያ አማራጭን በማስፋት ይበልጥ ተጠቃሚ ያደርጋል። አንዳንድ የምዕራቡ ዓለም አገሮች ከአፍሪካ ጋር ያላቸው የንግድ ግንኙነት የራሳቸውን የኢኮኖሚና የፖለቲካ የበላይነት ብቻ ባስጠበቀ መልኩ እንዲቀጥል ይሻሉ። ለዘመናት የዘለቀው ይህ እሳቤያቸው በተለይም በማደግ ላይ ላሉት የአፍሪካ አገሮች የእድገታቸው ማነቆ ሲሆን ይስተዋላል። የአህጉሪቷን ሰፊ የተፈጥሮ ሀብትና የሰው ኃይል እነርሱ በሚፈልጉት መልኩ ብቻ አልምተው ለመጠቀም ስለሚሹ የፍትሃዊ ተጠቃሚነት ጉዳይ ጥያቄ ውስጥ ይገባል።

ከዚህ በተቃራኒው ቻይና በዓለም የግዙፍ ኢኮኖሚ

ባለቤት በመሆኗ ከአፍሪካ አገሮች ጋር እየተጠናከረ የመጣው የንግድ ትብብር የሁለትዮሽ ጥቅሙም እያደገ መጥቷል።

የአፍሪካ ንግድ ምክር ቤቶች ዋና አስተዳዳሪ ክቡር ገና እንደሚሉትም፤ ቻይና በስፋት በአፍሪካ አገሮች ላይ የጀመረችው የንግድ ትስስር ለአህጉሪቷ ዘርፈ ብዙ ፋይዳ አለው። በተለይም የቻይና መንግሥት ከአፍሪካ ጋር ለመጀመር ያሰበው የግብርና ምርቶችን ከቀረጥ ነፃ ወደ ቻይና የማስገባት ዕድል የቻይና- አፍሪካን ትብብርና ተጠቃሚነት ይበልጥ የሚያጠናክር ነው።

ቻይና በአፍሪካ ያላት የንግድ ግንኙነት መርህ ሁሉንም ተጠቃሚ ሊያደርግ የሚችል መሆኑንም አቶ ክቡር ይናገራሉ። በየጊዜው እያደገ የመጣው የቻይና አፍሪካ የንግድ ትብብር ለአፍሪካዊያን የገበያ አማራጭን በማስፋት ይበልጥ ተጠቃሚ የማድረግ እድል አለው።

የኮርፖሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ሳንዶካን እንደሚሉት፤ ቻይና ከአፍሪካ አገሮች ምርቶችን ከኮታና ታክስ ነጻ ለማስገባት የፈቀደችው 300 ቢሊዮን ዶላር እድል ከፍተኛ ነው። ስለዚህ ይህን እድል በሙሉ አቅም ለመጠቀም በትጋት ይሰራል።

ኢትዮጵያ በዚህ ከፍተኛ እድል ተጠቃሚ ለመሆን ተዘጋጅታ መጠበቅ ይኖርባታል። በተለይ ለዚህ እድል መሳካት አምራች የሰው ኃይል ከፍተኛ ግምት ይሰጠዋል። ሌላው የግብርና መር ኢኮኖሚ መኖሩና የቻይና መንግሥት የሰጠው እድል በግብርና ምርቶች ላይ ትኩረት ማድረጉ እድሉን ለመጠቀም መልካም አጋጣሚ ነው። ምጣኔ ሃብታቸው የተፈጥሮ ሀብት ላይ መሰረት ካደረገ አገሮች ኢትዮጵያ የተሻለ እድል አላት። በተጨማሪም የግብርና ውጤቶችን እሴት ጨምሮ ለመላክ የተገነባ የግብርና ማቀነባባሪያ ኢንዱስትሪ ፓርኮች መኖር ሌላው እድል ነው። በአሁኑ ወቅት አራት የግብርና ማቀነባባሪያ ኢንዱስትሪ ፓርኮች እድሉን ለመጠቀም እና የተለያዩ ምርቶችን በዓለም ገበያ ለማቅረብ አስቻይ ሁኔታ ይዞ መጥቷል።

መፍትሔ የሚያሻቸው ችግሮችና የቀጣይ ትኩረት

በኢትዮጵያ የውሃ፤ የኤሌክትሪክ ኃይል፤ ቴሌኮምና ሌሎች መሰረተ ልማቶች ቢሟሉም ባለሀብቶች ወደ ስራ ከገቡ በኋላ መቆራረጥ ሲያጋጥም አገልግሎት ሰጪ ተቋማት ፈጣን ምላሽ የመስጠት ኃላፊነት አለባቸው። ይሁን እንጂ አሁን ባለው ሁኔታ በተለያየ ቦታ የሚገኙ ኢንዱስትሪ ፓርኮቸ የኤሌክትሪክ ኃይልና የውሃ

መቆራረጥ ችግር እያጋጠማቸው ይገኛል። ለአብነትም በአዲስ አበባ የሚገኙ ኢንዱስትሪ ፓርኮች በተደጋጋሚ ለሚያጋጥማቸው የኤሌክትሪክ ኃይል መቆራረጥ በፍጥነት እንዲፈታ ጥያቄ ቢቀርብም ዘላቂ መፍትሄ አለመገኘቱን ነው የሚገልጹት። በተመሳሳይም የውሃ አቅርቦት ጉዳይም ችግር ሆኖ በመቀጠሉ አፋጣኝ ምላሽ የሚፈልግ ጉዳይ ነው።

ኢትዮጵያ በቀጣይ አስር ዓመታት ልማት በማምጣት የዜጎችን ብልጽግና እውን ለማድረግ የምትከውናቸውን ዋና ዋና የልማት እቅዶች የሚመራ በአገር በቀል ምጣኔ ሀብት ላይ መሰረት ያደረገ የ10 ዓመት መሪ የልማት እቅድ አውጥታ በትግበራ ላይ ትገኛለች። ይህን እቅድ ለማሳካት ቀዳሚ ሚና ከሚጫወቱት መካከል የማምረቻው ዘርፍ ተጠቃሽ ነው። ለዚህም በኢንዱስትሪ ፓርኮች በቀጣይ 5 እና 10 ዓመታት ለማሳካት በተዘጋጀው ስትራቴጂክ እቅድ ላይ እ.ኤ.አ በ2030 በፓርኮች ውስጥ ከ720 ሺህ በላይ የሥራ እድል ለመፍጠር እቅድ ተይዟል። የኢንዱስትሪ ፓርኮችን የምርትና ገበያ ስብጥር በማስፋት ጥራትን መሰረት አድርገው እንዲያመርቱ ቅድሚያ እንደሚሰጥ ነው ዋና ሥራ አስፈጻሚው በአጽንኦት የገለጹት።

ዋና ስራ አስፈጻሚው አቶ ሳንዶካን እንደሚሉት፤ ኢንዱስትሪ ፓርኮች በመንግሥትና በግል አጋርነት እንዲገነቡ በተለያዩ ክልሎች መሬት ተዘጋጅቷል። በሱማሌ ክልል ሊገነባ የታሰበና የፋይናንስ ምንጭ እየተፈለገለት የሚገኘው አንዱ ተጠቃሽ ነው። በቢሾፍቱ ኢንዱስትሪ ፓርኮች በባለሀብቶች ወይንም በመንግሥት እንዲለሙ 180 ሄክታር መሬት ዝግጁ ሆኖ ይገኛል፤ በጋምቤላ ክልልም በተመሳሳይ ቦታ ተለይቶ ተዘጋጅቷል።

የኢንዱስትሪ ፓርኮች በልማት የዜጎችን ሕይወት ለማሻሻል የተያዘውን እቅድ ለማሳካት ትልቁን ድርሻ እንዲይዙ የኢንዱስትሪ ልማት ኮርፖሬሽን የ20 ዓመት የኢንዱስትሪ ፓርኮች ስፓሻል ፕላን በ2013 ጥናት አድርጎ ለመንግሥት አቅርቧል። ጥናቱ በተለያዩ ክልሎች የሚገኙ ሀብቶችን ከግምት በማስገባት ኢንዱስትሪ ፓርኮችን ለመገንባት ያላትን አቅም የለየ ነው። በዚህም ከ100 በላይ ኢንዱስትሪ ፓርኮችን በሚቀጥሉት 20 ዓመታት የመገንባት አቅም እንዳለ ማመላከቱን ዋና ስራ አስፈጻሚው ያመለከቱት። በምጣኔ ሀብት እድገት፣ በፈጠራ፣ በፖለቲካና ሌሎችጉዳዮች ዓለም ውድድር ውስጥ በሆነችበት በዚህ ወቅት በምርትና ገበያ ተለያይነት፣ በጥራት፣ በብራንድ ተወዳዳሪ ሆኖ በመገኘት የዓለምን ገበያ ሰብሮ መግባት ግድ የሚልበት ወቅት ነው።



40

የአፍሪካ ጉዳይ

አፍሪካ - 21ኛውን ክፍለ ዘመን በአድዋ የድል መንፈስ



41

አፍሪካ - 21ኛውን ክፍለ ዘመን በአድዋ የድል መንፈስ

አድዋ የመቀስቀሻ ደወል አፍሪካዊያን ከተፈጥሮ ጋር ባላቸው የሕይወት መስተጋብር ምክንያት ብዙም ለውጥ ሳያመጡ ዘመናትን አሳልፈዋል። በተፈጥሯዊና በቀላል መንገድ በማምረት፣ ምርትን ለዕለት ፍጆታ መጠቀም እንጂ መሰረታዊ ለውጥ ሊያመጣ በሚችል ደረጃ ሳያከናውኑ፣ ንቃተ ህሊናቸው ብዙም ሳይለወጥ ዘመናት መቆየታቸው አህጉሪቷን ጨለማ ሲያስብላት ቆይቷል። “ነጭ የተሻለ ነው” የሚለውን የምዕራባዊያን ፍልስፍናን ለማረጋገጥ ማጣቀሻ የሚሆነውን የአኗኗር ዘይቤያቸውን ሳይቀይሩና ዘመናቸውን እውቀት መሰረት ባደረገ መልኩ ሳይዋጁ መቆየታቸው በኋላ ላይ ብዙ ዋጋ አስከፍሏቸዋል።

አፍሪካዊያን በአንድ በተደራጀና ህብረቱን በጠበቀ መንግስት ሳይሆን በየአካባቢው ባሉ መሪዎች የሚተዳደሩ ሆነው መቆየታቸው የተፈጥሮ ሀብቶቻቸውንና ጉልበታቸውን ለመቀራመት አሰፍስፈው ለቆዩ ኃይሎች እጃቸውን ለመስጠት ሁኔታዎቹ አስገድዷቸዋል። “አፍሪካዊያን የብረት ማዕድንን ከመሬት ቆፍሮ በማውጣትና የባሩድ ውህድ አሰራርን ከአውሮፓውያን ቀድመው የፈጠሩ ቢሆኑም ለጠብመንጃና ለጥይት ሥራ ባለማዋላቸው ይህ አበርክቷቸው ራሳቸውን ዛሬ ላሉበት ነባራዊ የተጠቂነት እውነት ዳርጓቸው አልፏል” በማለት እኤአ በ2018 ግርምተ ሳይንስ የሚለውን መጽሀፍ ያሳተመው ሰለሞን ሙሉጌታ ሁኔታውን በግልጽ ያሳያል።

ለዚህም ነው የአፍሪካ አገሮች ራሳቸውን የመከላከል ሥነ ልቦና ዝግጅት ሳይኖራቸው አገራቸውን ለቅኝ ገዥ ሰጥተው የተፈጥሮ ሀብታቸው ሲበዘበዝ፣ መሬታቸውን ሌሎች ወርሰው ሀብት አልባ ሲያደርጓቸው የተስተዋለው።

በጌታቸው ሠናይ



42

አፍሪካዊያን በራሳቸው መንገድና ጥበብ ለዘመናት የገነቡት ማህበራዊ መዋቅራቸው ተደርምሶ፣ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነታቸው ለሌላው ተላልፎ፣ በገዛ አገራቸው ፖለቲካዊ ሥልጣናቸው ተቀምቶ በአስተሳሰብ ደረጃ “ነጭ ልዩ ፍጡር ነው” የሚለውን አመለካከት ተቀብለውና ለእነርሱ እየታዘዙ “በሰላም” መኖር የጀመሩት ውስጣዊ ዝግጅታቸውና ትግላቸው ክፍለዘመኑን የሚመጥን ባለመሆኑ ነበር። የዚህን የተሸናፊነት ሥነ ልቦና ሰብሮ “ማሸነፍ ይቻላል” የሚል የመቀስቀሻ ደወል ያስተጋባው አድዋ ላይ በጀግኖች ኢትዮጵያውያን የተመዘገበው ታሪካዊ ድል ነው።

አፍሪካ በቅኝ ገዠዎች እጅ በወደቀችበት ወቅት “ኢትዮጵያዊያን በአሸናፊነት የወጡበት ነበር። በምዕራባዊያን ዘንድ የወቅቱ ትኩሳት ሆኖ ተወራ፤ ጥቁሮች ነጮችን አሸነፉ ዋናዋ ነገር ይቺ ናት። በአፍሪካዊያን ደረጃ ትልቅ ስሜትን ፈጠረ፤ ማሸነፍ እንችላለን የሚለው በአጭር ጊዜ በሰፊው ተሰራጨ” በማለት የታሪክ ምሁሩ ፕሮፌሰር አደም ካሊም ለሪፖርተራችን አስቴር ታደሰ የተናገሩት ሀሳብ ጥቁሮች “ማሸነፍ እንችላለን” በሚል ለነጻነታቸው እንዲታገሉ ጥርጊያ መንገድ መክፈቱን ይመሰክራል።

በወቅቱ ግን ጣሊያኖች ለኢትዮጵያዊያን የሰጡት ግምት በጣም ዝቀተኛ ነበር። ተከፋፍለዋል፣ ምንም ዓይነት ዝግጅት የላቸውም፣ በመሳሪያም ሆነ “ከእኛ አይሻሉም” በሚል በቅኝ ግዛት ውስጥ ለመክተት ቆርጠው ተነስተው እነደነበር የታሪክ ድርሳናት ዋቢ ናቸው። ደራሲ ዲን ደብልዩ አርኖልድ “UNKNOWN EMPIRE” በሚለው መጽሀፋቸው ላይ ኢትዮጵያዊያን ከጣሊያን ጋር ጦርነት ሲገጥሙ በጠላታቸው በኩል የነበረው አተያይ “በቁጥር አነስተኛ፣ ያልሰለጠነ የሰው ሃይል” የሚል እምነት እንደነበረው ያረጋግጣል። ጣሊያኖች በወቅቱ በደረሳቸው የስለላ መረጃ መሰረት የኢትዮጵያ መሪዎች (በወቅቱ ንጉሶች) እርስ በርሳቸው የተከፋፈሉና መግባባት የማይችሉ፣ በጠላትነት የሚተያዩ ስለሆኑ “በቀላሉ እናሸንፋለን” የሚል እምነት እንደነበራቸው በመጽሀፋቸው አስፍረዋል። ነገር ግን ኢትዮጵያዊያን የነበራቸውን ልዩነት ወደ ጎን በመተው ባላቸው አቅምና መሳሪያ ጠላታቸውን ተጋፍጠው የአድዋ ድል ተበሰረ። ይህ ታላቅ ድል ባይገኝ ኖሮ ምናልባት የኢትዮጵያም ሆነ የአፍሪካ ሁኔታ አሁን ያለውን መልክ ላይዝ ይችላል።

ያም ሆነ የአድዋን የድል መንፈስ ተላብሰው ንቅናቄ በማድረግ አፍሪካን ከቅኝ ግዛት ለማላቀቅ ከሰባት አስርታት በላይ ትግል አስፈልጓል። አፍሪካ ለነጻነቷ ልጆቿን ሰውታለች፤ እጅግ ከባድ የሆነ መስዋዕትነትም ከፍላለች።

ኢትዮጵያዊያን በጀግንነት የከፈሉት መስዋዕትነትና ያስመዘገቡትን አንጸባራቂ ድል ለማግኘት ሌሎች ከግማሽ ክፍለ ዘመን ያህል ለመታገል ተገደዋል። አፍሪካዊያን በገዛ

አገራቸው የፖለቲካና የኢኮኖሚ ነጻነት ማግኘት ፈተና ሆኖባቸው ዓመታትን ዘልቀዋል። ለተዛነፈው ማህበራዊ መዋቅራቸው ምላሽ ማግኘት አቅቷቸዋል።

“የአድዋ ድል እንደሰደድ እሳት እየተሰራጨ የጥቁሮችን መብት የማስከበር ሁኔታ ሀሁ ብሎ ጀመረ” በማለት ፕሮፌሰር አደም የተናገሩት አባቶቻችን በባዶ እግራቸው ገስግሰው ጦር ሜዳ በመግባት ያላቸውን የነፍስ ወከፍ መሳሪያ ታጥቀው ያስመዘገቡት የአድዋ ድል ለአፍሪካውያንም ሆነ በሌላው ዓለም ለሚኖሩ ጥቁር ህዝቦች የነጻነት ትግል ቀስቃሽ መሆኑን ያረጋግጣል።

በአድዋ ጦርነት ኢትዮጵያዊያን ወታደሮች በያዙት መሳሪያ፣ አካፋም፣ አንካሴም፣ መጥረቢያም ጣሊያኖች ላይ ዘመቱባቸው። ጦርነቱ “በጣሊያኖች ዘንድ ከፍተኛ እልቂት አስከተለ፤ ሶስት ጄኔራሎችና በሺ የሚቆጠሩ ወታደሮች አለቁ” በማለት ፕሮፌሰሩ የሰነዘሩት ሀሳብ

በተሻለ አቅምና ወታደራዊ ዝግጁነት የመጣው የጣሊያን ሀይል በወታደራዊ ስልትና በስለላ ጥበብ አንድ እርምጃ ተቀድሞ በመገኘቱ ሽንፈቱን መከናነቡ ያረጋግጣል።

አፍሪካዊያን ከተፈጥሮ ጋር ያላቸው መስተጋብር ባለመለወጡ አውሮፓውያን ቅኝ ለመግዛት ሲወስኑ “የትኛውም አገር ተገዳዳሪ ይሆናል” የሚል እምነት እንዳልነበራቸው ያሳያል። የአድዋ ድል ይህን አስተሳሰብ የሰበረ የኢትዮጵያዊያንን አትንኩ ባይነት ያረጋገጠ እውነት ነው። ለዚህ ነው ከቀኝ ግዛት ራሳቸውን ነጻ ለማውጣት የትግል መሳሪያ ላነሱ ሃይሎች ሁሉ “አድዋ” የራሱ ታላቅ ትርጉም እንዳለው የሚታመነው። አፄ ምኒሊክ ለህዝባቸው ያስተላለፉትን የክተት ጥሪ ተቀብሎ ሁሉም በተባለበት ቦታ ለመገኘት በጥበብ ተዋግቶ ድልን በአጭር ጊዜ ውስጥ መቀዳጀታቸው ታላቅ መሆኑን ማጤን ጥበብ ነው። ሌሎች የተወሰደባቸውን ነጻነት



43

ለማስመለስ የፈጀባቸው የትግል ዓመታትና የከፈሉት መስዋዕትነት ሲታይ አባቶቻችን ለአገራቸውና ከእነርሱ በኋላ ለሚመጣው ተከታታይ ትውልድ ያስቀሩትን መርገም ጥልቀትና ግዝፈት መረዳት ይችላል።

“አፍሪካዊያን ከጭንቀታቸው፣ ከፍርሃታቸው ወጥተው ለመዋጋት ተነሱ። ማሸነፍ እንችላለን የሚል ስሜት ተፈጠረ። በእያንዳንዱ የአፍሪካ አገሮች እንቅስቃሴ ነበር ማለት ይቻላል። የእነ ኡመር አልሙክታር በሊቢያ ውስጥ እንቅስቃሴ የተጀመረው ከአድዋ ውጤት በኋላ ነው። አልጀርስም ፈረንሳዊያን ግፍ እየፈጸሙ ንብረታቸውን እየቀሙ እንደባሪያ ነበር የሚቆጥሯቸው። አልጀርሶች በሚሊዮን የሚቆጠሩ ዜጎቻቸውን አጥተው ነው አገራቸውን ነፃ ያወጡት” በማለት ፕሮፌሰር አደም የገለጹት አፍሪካዊያን ከቅኝ ግዛት ለመላቀቅ ያደረጉት ትግል ብዙ ዋጋ እንዳስከፈላቸው ያረጋግጣል።

አፍሪካዊያን ከዚህ ተነስተው ከቅኝ ገዥዎቻቸው ለመላቀቅ መራር የነጻነት ትግል አካሂደዋል። በዚህ መራራ ትግላቸው የፖለቲካ ነጻነታቸውን ቢቀዳጁም ኢኮኖሚያዊ መዋቅራቸውና ማህበራዊ ትስስራቸው በቀኝ ግዛት ዘመን በተቀየሰው መንገድ የሚጓዝ ነው። እስከአሁንም ሙሉ ነጻነት ማግኘት አልቻሉም።

የአድዋ ድል አፍሪካውያንን ለትግል ቀስቅሶ ነጻነታቸውን ቢያውጁም እስካዛሬ ድረስ ዋጋ የሚያስከፍል ሥርዓት ውስጥ ገብተዋል። አፍሪካዊያን ከቅኝ ግዛት ተላቀው በአካል በራሳቸው ልጆች እንዲተዳደሩ መንገዱ ቢከፈትም ለምዕራባዊያን ያልተመቹ መሪዎች በመፈንቅ ለመንግስት እየተወገዱ ሌላ እየተተካ የአፍሪካን መጻዒ ዕድል በጨለማ ጉዞ ውስጥ እንዲሆን መንገድ ከፍቷል። የአፍሪካ የቁርጥ ጊዜ ልጆች በቅጥረኞች እየተገደሉ ለአገራቸው የነበራቸው ራዕይ ሲጨናገፍ ተስተውሏል።

“አውሮፓዊያን የወታደራዊ አገዛዝ ተሸንፈው ወጡ እንጂ በኢኮኖሚ ከአፍሪካ ለቀው አልወጡም። በሁለት መልኩ እናየዋለን፤ አንደኛ እነርሱ ያሰለጠኗቸው የእነርሱ ጉዳይ አስፈጻሚ የሆኑ የእነርሱን አርአያ የሚከተሉ መሪዎች በስልጣን ላይ እንዲውሉ አደረጉ። መካከለኛው ምስራቅ ብናይ በመሪነት ደረጃ ተመድበው የነበሩት በሙሉ ከፈረንሳይ፣ ከጣሊያን፣ ከእንግሊዝ ጋር ግንኙነት ያላቸው እነርሱ ጋር ሄደው ስኮላርሺፕ የወሰዱ የእነርሱ አስፈጻሚ አካል ሆነው የተመደቡ ነበሩ። እነዚህ መሪዎች በፈረንሳይ አሊያም በእንግሊዞች በኩል በርዕዮተ ዓለም ይይዟቸዋል። ለእነርሱ አገልጋይ እንዲሆኑ ተደርጎ ነው የተመደቡት። ስለዚህ ምዕራባዊያን የአፍሪካን ያልተነካ ጥሬ ዕቃ ድንግል የሆነ መሬት ነው የሚፈልጉት። አፍሪካ በኢኮኖሚ እንድትጠነክር አይፈልጉም ሁሉም የእነርሱ ታዛዥ እንድትሆን ይፈልጋሉ” በማለት ፕሮፌሰር አደም የሚገልጹት ሃሳብ በነጻነት ትግሉ የተፈለገው ውጤት ሳይገኝ መቅረቱን ያመላክታል።

የአፍሪካ አገሮች ነጻነታቸውን ባገኙ ማግስት በመፈንቅ ለመንግስት እርስ በርሳቸው የሚጠፋፉ ሆነዋል። በአህጉር ደረጃ በማሰብ አስራ ዘጠነኛውን፣ ሃያኛውን ክፍለ ዘመን ታላቅ ስራዎችን አከናውነው “የአድዋን ድል መንፈስ” በሌሎች መስኮችም እውን ያደርጋሉ ቢባልም የተፈለገው ውጤት ሳይገኝ ሃያ አንደኛው ክፍለዘመን ተጀመረ። ሃያ አንደኛው ክፍለ ዘመንም ብዙም ካለፉት ክፍለ ዘመኖች ባልተለየ መልኩ እየገሰገሰ ዓመታት ተቆጠረ፤ ዓመታቱ ይገሰግሳሉ። አፍሪካስ?

21ኛው ክፍለ ዘመንና አፍሪካ አፍሪካ በሃያ አንደኛው ክፍለዘመን በተስፋና በተግዳሮት መካከል ተወጥራለች። አፍሪካዊያ ለተሻለ መቀራረብና በአገር ደረጃ ትስስር ለመፍጠር ከመቼውም ጊዜ በላይ የአድዋ ድል የፈጠረው የመነቃቃት መንፈስ አሁን የግድ ያስፈልጋቸዋል።

በአሁኑ ወቅት አገሮች እርስ በርስ የመቀራረብ፣ የነጻ የንግድ ቀጣና መፍጠራቸው መልካም ጅምር ተደርጎ ይወሰዳል። አንዳንዶቹ አፍሪካ አገሮች የተሻለ ኢኮኖሚያዊ እድገት ማስመዝገብም ጀምረዋል። የዓለምን ትኩረት ሊስቡ የሚችሉ ተግባራትም በማከናወን የተሻለ እንቅስቃሴ እያደረጉም ናቸው።

አፍሪካ እያካሄደችው ባለው ለውጥ የኢንቨስተሮችን ትኩረት እየሳበች ትገኛለች። የሰላምና ደህንነት ጉዳይ አሳሳቢ ተደርጎ ቢወሰድም የአፍሪካ መሪዎች የፓን አፍሪካ አስተሳሰብን ገዥ ለማድረግ እየወሰዱት ያለው አቋምና የተግባር እንቅስቃሴ በመልካም ጅምርነቱ ሊጠቀስ ይችላል። አፍሪካ የኢንቨስተሮችን ቀልብ ከመግዛት አኳያ ካሉት አህጉራት ሁለተኛውን ደረጃ መያዟ በአንድ ወቅት “ኢርነስት ኤንድ ያንግ” የተባለ ተቋም ያወጣው መረጃ ብዙም ሊያስገርመን አይችልም። በተፈጥሮ ሀብት



44

የበለጸገች አህጉር ነችና። ሰፊ የእርሻ መሬት አላት፣ በከርሰ ምድሯ ውድ የሆኑ ማዕድናት ታቅፋለች፣ ለኤሌትሪክ ሃይል ማመንጨት የሚችሉ ወንዞችና ከንፋስ ሃይል ለማገኘት የሚያስችል በቂ አቅም አላት። የአህጉሪቷ ከአንድ ቢሊዮን በላይ የሆነው ህዝብ ሰፊ የገበያ እድል የሚሰጥ ነው።

አፍሪካ በተለይም ከሰሀራ በታች ባለፉት አስር ዓመታት ለውጦች ማስመዝገቧ እውነት ነው። በኢኮኖሚ እድገት የተገኘው ውጤት ብዙ ቢቀረውም ለበርካታ ዓመታት ከነበረው አኳያ የተሻለ መሆኑን መረጃዎች ያረጋግጣሉ። የንግድ ቀጣና ትስስር መፈጠሩ፣ የተለያዩ ኢኮኖሚዊ ትስስሮች እየተደረጉ መምጣታቸው፣ ከውስጥ ወደ ውጭ የማየት አዝማሚያ መኖሩ፣ የትምህርት ስርዓቱን ደረጃውን የጠበቀ ለማድረግ የሚካሄድ ትግል መመልከት ለአፍርካ መልካም እድል እየተፈጠረ መሆኑን ያረጋግጣልና።

አፍሪካ የተፈጥሮ ሀብቷን በአግባቡ ተጠቅማ የኢኮኖሚ እድገት ማስመዝገብ፣ ሰው ሰራሽና የተፈጥሮ መስህቦቿን ለቱሪዝም ክፍት በማድረግ ዓለምን ማስደመም የሚጠበቅ ጉዳይ ነው። ለዘመናት የበለጸገውን የዳበረ ባህሏን፣ የስነ ጥበብ ስራዎቿን ወደፊት በማምጣት አሁን ካለችበት ነባራዊ ሁኔታ ለመወጣት የምታደርገው ጥረት በመልካም የሚታይ ነው።

አፍሪካ በሳይንስና ቴክኖሎጂ ከፍተኛ ደረጃ ላይ ለመድረስ ከተቀረው ዓለም ጋር ፉክክር ውስጥ መግባት ሲገባት እዚያው ባለችበት መሆኗ ብዙዎችን የሚያስደነግጥ ጉዳይ ነው። ዛሬ ላይ አፍሪካ “መሬትና ርካሽ የሰው ጉልበት አለኝ” በሚል የኢኮኖሚ አስተሳብ ምን ያህል እርቀት ትሄዳለች? የሚለው ጥያቄ በቀላሉ የሚታይ ብቻ ሊሆን አይችልም። “የድኝች ችብስ ከኮምፒውተር ችብስ ጋር” ሊታይ አይችልም።

የአፍሪካን ጥሬ ሀብት ወደ ውጭ በማሻገርና የውጭ ምንዛሪ በማግኘት ምን ያህል እርቀት ይዘለቃል? በምን ያህል ደረጃ የወጣቱን የስራ ፍላጎት ማሟላት ይቻላል? ሃያ አንደኛው ክፍለ ዘመን ላይ እየመጣያለው አስተሳሰብና የቴክኖሎጂ ውጤት አፍሪካውያንን አገራቸው ውስጥ ሆነው አገር ሊያሳጣቸው አይችልም ወይ? በአዲሱ ዘመን የቅኝ ግዛት ዘዬ ስር ላለመውደቅ ምን ዋስትና አላቸው? ምንስ እያደረጉ ነው? የምድር ሉዓላዊነት ሲያስጠብቁ የሃያ አንደኛው ክፍለዘመን ሉዓላዊነታቸው እንዳይደፈር ምን ሰርተዋል? አፍሪካ በአዲስ መልክ የአድዋን ድል ለማስመዝገብ ምን ዝግጅት አላት? የሚለው ጥያቄ የብዙዎች ራስምታት ሆኗል።

አፍሪካ የቴክኖሎጂ ተጠቃሚ በመሆን እድገቷን ለማፋጠን የምታደርገውም እንቅስቃሴ ቀላል ግምት የሚሰጠው አይደለም። ይህም ሆኖ ግን አፍሪካ ሃያልና ሀብታም ሆና ወደፊት ለመምጣት አልቻለችም። “በምድር ላይ እጅግ ሀብታም የሆነው አህጉር ህዝቦቿ በድህነትና

በችግር ይማቅቃሉ” የሚል የምዕራባዊያን ዘገባና የኢኮኖሚስቶች ትንታኔ መስማት የተለመደ ሆኗል።

አብዛኛዎቹ የአፍሪካ መሪዎች በሙስና መዘፈቅ፣ በአመራር ብቃት ማነስና የምዕራባዊያን ጉዳይ አስፈጻሚ መሆን ለአፍሪካ ወደፊት መጓዝ እንቅፋት ተደርጎ ይወሰዳል።

“በፖለቲካው መስክ ያሉ ችግሮች የአፍሪካ አገሮችን ክብር የሚያሳንስና የአህጉሪቷን ልማት ወደ ኋላ የሚያስቀር ድርጊት በመሆኑ ከወዲሁ መገታት ይገባዋል” ሲሉ የሴኔጋል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትርና የአፍሪካ ህብረት የሥራ አስፈጻሚ ምክር ቤት ምክትል ሰብሳቢ ታል ሳል በቅርቡ የገለጹት ሀሳብ አፍሪካ በሃያ አንደኛው ክፍለ ዘመን ያለችበት ሁኔታ አህጉሪቷን የማይመጥን እንደሆነ ያመላክታል።

ለዚህ ነው አፍሪካ በሃያ አንደኛው ክፍለ ዘመን በእርስ በእርስ ግጭት፣ በሽብርተኞች የምትናጥ፣ አገሮች በመፈንቅ ለመንግስት የሚተራመሱባት የሆነችው። ለምንድን ነው አፍሪካ እንደዚህ ዓይነት ወጥመድ ውስጥ የገባችው? በቅኝ ግዛት ዘመን የተሸረበውን ሴራ አልፎ መሄድ ያለመቻለ አንዱ ተጠቃሽ ነው። በርካታ የአፍሪካ ፖለቲከኞችና ምሁራን ትልቁን ምስል ከማይት ይልቅ በጥቃቅን ጉዳዮች መጠመዳቸው በአህጉሪቷ የሚለኮሱ የለውጥ እንቅስቃሴዎች ከግብ ሳይደርሱ ይከስማሉ።

በቱኒዚያ፣ በግብጽና በሊቢያ የተጀመረው የለውጥ እንቅስቃሴ በየራሱ መልኩን ቀይሮ አገሮቹን ከምን እንዳደረሳቸው በግልጽ የሚታይ ጉዳይ ሆኗል።

የአፍሪካ ሰላምና ደህንነት 21ኛ ክፍለ ዘመን

አፍሪካ የሰላምና ጸጥታ ችግር አደጋዎችን በየዕለቱ እየተጋፈጠች ነው። በአህጉሪቷ ዘላቂ ሰላምና ደህንነትን ለማረጋገጥ እንዳይቻል ተግዳሮት የሆኑት ፖለቲካዊ ቀውስ፣ የሃይማኖት አክራሪነት፣ ኢ - ፍትሃዊ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት፣ ማህበራዊ ትስስር እየላላ መምጣት ይጠቀሳሉ። በየአካባቢው ጽንፈኛ ብሄረተኝነት እያደገ መምጣት፣ የፍትህ መዛባት፣ የህግ የበላይነት መጥፋት ሌሎች ተጠቃሽ ጉዳዮች ናቸው። በአፍሪካ አገሮች የሰብዓዊ መብት ጥሰት መግዘፍ፣ ሕገወጥ ስደት፣ የመሰረታዊ አገልግሎቶች ጥራት ማነስና የአገልግሎቶቹ እጥረት ማጋጠም ከፍተኛውን ድርሻ መያዙ እውነት ነው።

በአፍሪካ አገሮች የመሰረታዊ አገልግሎቶች አቅርቦት በሚፈለገው ደረጃ ያለመሆን፣ የተፈጥሮ ሀብቶችን ፍትሃዊ በሆነ መልኩ ለመጠቀም ያለመቻል፣ የመንግስት አገልግሎት መስጫ ተቋማት ደካማ መሆን ለአፍሪካዊያን የ21ኛው ክፍለዘመን ግዙፍ ችግር ሆኗል። ይህ ብቻ ሳይሆን ከእለት እለት እየተስፋፋ የመጣው የህገወጥ የጦር



45

መሳሪዎችና ጥይቶች ሽያጭ አሳሳቢ ደረጃ ላይ መድረስ በዜጎች ላይ ያሳደረው ስጋት ተስፋን የሚያጨልም ነው።

የአፍሪካ ህብረት “የጥይት ድምጽ የማይሰማበት፣ ለልማት ምቹ ሁኔታዎች አፍሪካን መፍጠር” የሚል እኤአ 2020 መሪ ሀሳብ ይዞ ቢንቀሳቀስም፤ እውን ለማድረግ እጅግ ብዙ ርቀት ላይ ነው። በተለያዩ አካባቢዎች ግጭቶች ይስተዋላሉ፤ ኢ- ህገመንግስታዊ ለውጦች ይካሄዳሉ። ይባስ ብሎ በ1960 እና 70 ዎቹ ውስጥ የነበረ የመፈንቅ ለመንግስት ተግባራት መስተዋል ጀምረዋል። በናይጄሪያ ያለው የቦካሃራም እንቅንቃሴ፣ ሊቢያ ያለችበት ተጨባጭ ሁኔታ፣ የየመን ጉዳይ እና ሌሎች አካባቢዎች የሚስተዋሉ ችግሮች የአፍሪካን መጻኢ ዘመን አሳሳቢ መሆኑን ያንጸባርቃሉ።

በአፍሪካ አገሮች የውስጥ ጉዳይ የውጭ ጫና እየበዛ መምጣትም ሌላው ችግር ተደርጎ ይወሰዳል። የውስጥ ችግሮቻቸውን በራሳቸው መንገድ እንዳይፈቱ ለማድረግ እጅ የመጠምዘዝ ስራ ሲከናወን ያስተዋለ ማንኛውም ግለሰብ 21ኛው ክፍለዘመን ለአፍሪካዊያን ፈታኝ መሆኑን መረዳት አያቅተውም። እንደውም አፍሪካ አሁን ባለችበት ተጨባጭ ሁኔታ 21ኛ ክፍለ ዘመንን ዋጅታ 22ኛውን ለመቀበል ትችላለች ወይ? የሚያስብል ጥያቄ ያስነሳል።

የአየር ንብረት ለውጥ፣ ድርቅና የተፈጥሮ አደጋዎች የሚፈታተኗት አፍሪካ ሰላምና ደህንነቷን አጥታ መከራዋን እያየች መሆኑ ጉዳዩን ውስጠ ወይራ የሚሉት ዓይነት ያደርገዋል። በአንድ በኩል የለውጥ ንፋስ፤ በሌላ በኩል የሰላምና ደህንነት እጦት የወጠራት አህጉር ሆናለች።

ለዚህም ነው የወቅቱ የአፍሪካ ህብረት ሊቀ መንበርና የሴኔጋሉ ፕሬዚዳንት በ35ኛ የመሪዎች ጉባዔ ላይ በአንድ ዓመት የስልጣን ዘመናቸው ለሰላምና ደህንነት ትኩረት እንደሚሰጡ ይፋ ያደረጉት። ተግዳሮቶቻችን አሁንም እጅግ በጣም ብዙ እና አንገብጋቢ ናቸው ከሰላምም ይሁን ከደህንነት፣ ከህገ መንግስታዊ ለውጦች፣ ከአካባቢ ጥበቃ፣ ከጤና እንዲሁም ከኢኮኖሚያዊ እና ማህበራዊ ልማት አኳያ መታየት አለበት። በአሁኑ ወቅት ቤተሰቦች በሀዘን ላይ ናቸው። በጦርነት ምክንያት ህይወት ጠፍቷል፣ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ተፈናቃዮችን ወይም ስደተኞችን ዓይተን እንዳላየን ዓይናችንን ልንሸፍን እንችላለን። . . . በአፍሪካ የግጭት አፈታት ዘዴዎች ጠብመንጃን ዝም እንዲል ማድረግ ያስፈልጋል። አስተዋይ አእምሮ ያለው የውይይት እና የሽምግልና ባህል መንገንባት ያስፈልጋል” ያልኩት ምልከታ አፍሪካ በ21ኛው ክፍለዘመን የገጠማት ፈተና እጅግ ከባድ እንደሆነ ያሳያል።

ለአፍሪካ ትልቁ ስጋት በውስጥ ሰላምና ደህንነቷን ማጣቷ፣ የተፈጥሮ ሀብታን በአግባቡ መጠቀም ያለመቻሏ አንዱ ሲሆን፤ ሌላው ዓለም እጅግ በሚያስደንቅ ፍጥነት በኢኖቬሽን ቴክኖሎጂ እየገሰገሰች በመሄድ ርቀቷን በእጅጉ አስፍታለች፤ ይህም የአህጉሪቷን ወደ ኋላ መቅረት

በግልጽ እያንጸባረቀ መጥቷል።

አፍሪካዊያን ልንክደው የማንችለው እውነት በአጭር ጊዜ ውስጥ እየተለዋወጠ ባለው ዓለም አቀፍ ሁኔታ ውስጥ እራሳችን ተወዳዳሪ አድርጎ በማቅረብ አሊያም ባለንበት እየረገጥን ለአዲሱ የቅኝ ግዛት ስርዓት እጃችንን ያለምንም ማንገራገር መስጠት ምርጫ ውስጥ እየወደቅን መምጣታችንን ነው። ለዚህ ጥያቄ ምላሽ ለመስጠት ዓይናችንን ከፍተን ዙሪያችንን ማስተዋል ይገባል።

ፒተር ኤፍ ዴሩከር እኤአ በ1994 “post- capitalist So- ciety” በሚል ርዕስ ባሳተሙት መጽሀፍ ላይ እንደገለጹት፤ ዓለም አቀፍ ሁኔታውና የማህበረሰቡ አወቃቀር ከጊዜ ወደ ጊዜ በፍጥነት እየተቀየረ መምጣት መልካም ነገርና ተግዳሮት ይዟል። “ቀደም ብሎ ከሚታወቁት የሀብት ምንጮች ጉልበት፣ መሬትና ካፒታል የሚገኘው ውጤት እየቀነሰ . . . እየቀነሰ መጥቷል። አሁን ላይ ዋነኛ የሀብት ምንጭ መረጃና እውቅት ነው” ያሉት ሀሳብ ከሀያ አምስት ዓመታት በኋላ መልኩን መቀየሩን መረዳት ይቻላል። 21ኛውን ክፍለዘመን ሳናገባድድ ኢንፎቴክና ባዮቴክ

ተዋህደው በሚፈጥሩት ውጤት በቢሊዮን የሚቆጠሩ ሰራተኞች ከስራ ገበታቸው እንዲባረሩ ምክንያት ሊሆኑ ይችላሉ የሚለውን የፕሮፌሰር ዩቫ ኖሃ ሃራሪ ሀሳብ ያስተዋለ አፍሪካዊ ጉዳይ ሊያስደነግጠው ግድ ነው።

አፍሪካዊያን ሰላምና ደህንነትን የማረጋገጥ፣ በየአገሮቹ ያሉ ችግሮችን የመፍታት፣ መልካም አስተዳደርና ዴሞክራሲን የማስፈን “አሁናዊ ሃላፊነት አለባቸው” ሲባል ከፊታቸው እየመጣ ያለውን የቴክኖሎጂ ዘመን ማዕበል ከኋላ የሚከተልን ስራ የውስጣዊ ችግር ናዳን ለመቋቋም የሚያስችል አቅም የመገንባት ጉዳይ ላይ ጥቁምታ መስጠት ነው። ይህ ብቻ ሳይሆን ዘመኑን ሊመጥን የሚችል እጅግ ፈጣን ለውጥ የሚያመጣ ተሀድሶ ማድረግም ይጠበቅባቸዋል። ሳይንስ፣ ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂን ማስፋፋት፣ ስራ ፈጣሪነትን ማጎልበት የህዝቡን እለታዊ ገቢ ማሳደግ ግድ የሚልበት ወቅት ነው።

አፍሪካዊያን በመቀራረብና መወያየት እንደአንደ አገር መስራት ካልቻሉ ከፊትና ከኋላ እየመጣ ያለው አደጋ ለማለፍ መቸገራችን አይቀሬ ነው። ለዘመናዊ ቅኝ ተገዥነት እጃቸውን እንደማይሰጡ እርግጠኞች መሆንም አይቻልም። ዘመናዊ የቅኝ አገዛዝ ለመዋጋት ብዝሃ ግንባር መፍጠርም ያስፈልጋል።

“የአፍሪካ ችግሮችን ለመፍታት በፓን አፍሪካኒዝም መንፈስ መሰባሰብና ለጋራ መስራት ያስፈልጋል። ፓን አፍሪካኒዝም አፍሪካዊያኖች አንድ መገኛ ያላቸው መሆናቸውን፣ እጣፈንታቸው በጋራ ሊወሰን የሚችል መሆኑን ያሳያል” በማለት የዛምቢያ ዲፕሎማት ዶክተር አንድሪው ሱሊሜሲ የገለጹትን ሀሳብ ማጤን ተገቢ ነው። አህጉሩን በአንድ መንፈስ አስተባብሮ አሸንፎ ለመውጣት ካልተቻለ 21ኛውን አልፎ 22ኛ ክፍለ ዘመን የመድረሱ ጉዳይ ህልም መሆኑ አይቀርም።

ዳሮን አሴሞግሉ እና ጄምስ ኤ.ሮቢንሰን እኤአ 2012 “Why Nation Fail” በሚል ርዕስ ባሳተሙት መጽሀፍ ላይ የፖለቲካ ኃይሉ የኢኮኖሚ ተቋማትን ጠንካራ በማድረግ ድህነትን ለማጥፋት ካልሰራ፣ ጠንካራ ማህበረሰብ ካልተገነባ ከድህነት መውጣት አይቻልም። ከድህነት ለመውጣት የመልካም አስተዳደር ማስፈን፣ አገልጋይ ተቋማት መገንባት ተገቢ ነው። አንድ አገር የበለጸገ እንዲሆን ለማድረግ ጠንካራ ህዝብና ጠንካራ ተቋማት ሊኖሩት ግድ ይላል። ሀሳቡ የሚያጠነጥነው አገር የበለጸገ ለማድረግ ከፖለቲካ ሃይል በሚመነጨው ፖሊሲ ጠንካራ የኢኮኖሚ ተቋማት መፍጠርን ይጠይቃል። ከዚህ ነጥብ መገንዘብ የምንችለው ይህን ለመፍጠር የአፍሪካ አገሮች እንደአንድ አገር ሆና ለመስራት የሚያስችላቸውን አቅጣጫ መከተል እንደሚጠበቅባቸው ነው።

በ35ኛ የአፍሪካ መሪዎች ጉባኤ ላይ የተገኙት የደቡብ ሱዳን ዲፕሎማት ጆን ዩሄንስ “ፓን አፍሪካኒዝም

አፍሪካዊያን በመቀራረብና

መወያየት እንደአንደ አገር መስራት

ካልቻሉ ከፊትና ከኋላ እየመጣ

ያለው አደጋ ለማለፍ መቸገራችን

አይቀሬ ነው። ለዘመናዊ ቅኝ

ተገዥነት እጃቸውን እንደማይሰጡ

እርግጠኞች መሆንም አይቻልም።

ዘመናዊ የቅኝ አገዛዝ ለመዋጋት

ብዝሃ ግንባር መፍጠርም

ያስፈልጋል።



46

የአፍሪካ ሕዝቦች በተለያዩ አህጉራዊ ጉዳዮች ላይ በጋራ እንዲቆሙና ትብብራቸውን እንዲያጠናክሩ የሚያደርግ ነው” በማለት ፓን አፍሪካኒዝም አፍሪካ የተጋፈጠችውን የ21ኛ ክፍለዘመን ተግዳሮት ልትረታ የምትችልበት የመፍትሄ መስመር መሆኑን አመላክተዋል። አፍሪካ የገጠማትን ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ መፍትሄ ለማበጀት በጋራ መረባረብ ወቅቱ የሚጠይቀው ጉዳይ ነው። ለዚህ አፍሪካዊያን መሪዎችና ህዝቦቿ ምን ያህል ቁርጠኞች ናቸው?

ዛሬም አብዛኛዎቹ አፍሪካዊያን ከሚያቀራርባቸው ይልቅ በሚያለያያቸው ጉዳይ ላይ ማተኮራቸው እየተስተዋለ ነው። አህጉሪቷ ከገጠማት ታላቅ ፈተና ይልቅ በውስጥ ጉዳያቸው ተጠምደዋል። እዚህም እዚያም ጦርነት ይታወጃል። አንዱ “ለነጻነት ነው” ይላል። ሌላው የሃይማኖት ጉዳይ ዋና መነሻዬ ነው በማለት ይታኮሳል።

“ይችን ዓለም የሚገዟት የመሳሪያ ነጋዴዎች አምራቾች ናቸው። እኛ ያልተገነዘብነው ይህንን ነው። የመሳሪያ ነጋዴዎች ማርኬት ይፈልጋሉ አንዱ ከአንዱ ጋር ካልተጋጨ መሳሪያው ለሽያጭ አይቀርብም ማንም ስለማይገዛው ይከስራል” በማለት ፕሮፌሰር አደም የተናገሩት በአፍሪካ ላይ የሚፈጠረው ችግር በአንድ አቅጣጫ ብቻ የሚመጣ ያለመሆኑን ያረጋግጣል። ለዚህም ፈጣን ምላሽ ሊሰጥ የሚችል አቅጣጫ መከተል ያስፈልጋል።

ከሰላምና ደህንነት ይልቅ ሁከትና ግጭት ይሰማል። ለዚህም ነው በዘንድሮ የአፍሪካ መሪዎች ላይ “የአፍሪካ ሕብረት በቀጣይ በአህጉሪቷ ሰላምና ጸጥታን በማስፈንና ሽብርተኛን በመከላከል ረገድ ትኩረት አድርጎ ይሰራል” የሚል ሀሳብ ጎልቶ የተሰማው።

የአፍሪካ ህብረት ሊቀ መንበርና የሴኔጋል ፕሬዚዳንት ማኪ ሳል 35ኛው የአፍሪካ ሕብረት ጉባኤ ሲጠናቀቅ ባሰሙት ንግግር “ወታደራዊ መፈንቅ ለመንግስት መከላከል ትኩረት ይደረጋል። አህጉሪቷ መረጋጋትና ሁለንተናዊ እድገት ሰላም መጠበቅ አስፈላጊ ነው። ሰላምና ደህንነት በሌለበት የሚፈለገው አህጉራዊ እድገት ሊሳካ አይችልም” በማለት የችግሩን አንኳር ጉዳይ አሳይተዋል። አገሮች ፖለቲካዊ፣ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ትስስሮችን መፍጠር እንዳለባቸው ነው ያመላከቱት።

የአፍሪካ ህብረት ሊቀ መንበር ማኪ ሳል ያነሱት ነጥብ፤ ሀሳብ ዘመኑን ለመዋጀት መነሻ ነው። የአፍሪካ አገሮች ከተናጥላዊ ጉዟቸው ይልቅ አንድነታቸውን ማጠናከር፣ ህብረታቸውን ማጎልበት ግድ የሚላቸው ጊዜ ነው። ሀሳባዊ የሆነውን መልከዓ ምድራዊ ድንበር ጉዳይ ላይ በማተኮር፣ በብሄርና ሃይማኖት ጽንፈኝነት መሳሪያ በማንሳት፣ በጠረጴዛ ዙሪያ ተወያይቶ ዴሞክራሲን ማሳለጥ ከመሻት ይልቅ ጦርነትን በመቀስቀስ ቀጣዩን ዘመን ማለፍ እንደማይቻል ከዓለም ነባራዊ ሁኔታ መገንዘብ አስፈላጊ ነው።

የዓለም ኃያላን በአገሮች የውስጥ ጉዳይ በቀጥታና በተዘዋዋሪ መንገድ እየገቡ ማተራመስ የሚችሉት ህብረት ባለመኖሩ ነው። “ዴሞክራሲ እንዲሰፍን፣የሰብዓዊ መብት እንዲረጋገጥ፣ ዜጎች የመምረጥ መብታቸው እንዲረጋገጥ፤ መልካም አስተዳደር እንዲሰፍን” በሚል በአገሮች የውስጥ ጉዳይ በመግባት የሚያስከትሉትን ጥፋት ከሊቢያ፣ ከየመን፣ ከሶሪያ፣ ከአፍጋኒስታ አለመማር የአሁኑንና መጪውን ዘመን ጠንቅቆ ያለመረዳት አሊያም ከግል ጥቅም ያለፈ ሃላፊነት ያለመሰማት ነው። አገሮችን ወደ ድንጋይ ዘመን በሚቀይር ጥፋት ውስጥ በመክተት ድጋፍና እርዳታ መስጠት ትርጉሙን ለተገነዘበው የማንቂያ ደውል አድርጎ መውሰድ ይችላል። እውን ዛሬ “ሉዓላዊነታችንን እንጠብቃለን” በማለት የምንዋደቅለት ነገ ላይ ሊኖር ይችላልን? የሚሉ ጥያቄዎችን ማንሳትና መልሱን መፈለግ ይሻል።

አፍሪካ ሰላምና ደህንነቷን ለማረጋገጥ አንደኛው መፍትሄ ወጣቶችን ተጠቃሚነት ማዕከል ያደረገ ተግባር የማከናወን አስፈላጊነት ትኩረት ተሰጥቶታል። የወጣቶች ተጠቃሚነት ለዘላቂ ሰላም አንደኛው የመፍትሄ አካል ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል። በርግጥ ከአንድ ቢሊዮን በላይ ከሆነው ህዝብ ውስጥ ግማሹ ከ25 ዓመት የማይበልጥ ከሆነ ይህን ሃይል በአግባቡ ማስተዳደርና መምራት አማራጭ የለውም። ጥያቄው ግን አፍሪካ ወጣቶቿን በትምህርትና በክህሎት ስልጠና ዓለምአቀፍ ተወዳዳሪ አድርጋ እያወጣች ነው? የሚለው ነው።

በአፍሪካ አሁን ያለው የትምህርትና ስልጠና አሰጣጥ ወጣቶቹን ዓለምአቀፍ ተወዳዳሪ የሚያደርጋቸው አይደለም። በቅርቡ የወጡ ጥናቶች እንደሚያሳዩት በአንድ ሙያ የሰለጠነ ሰው በዚያ ሙያ ለመስራት ገና ሲሰማራ ሙያው ከአገልግሎትና ከገበያ ውጭ የሚሆንበት እድል እየሰፋ መጥቷል። ይህም ለአፍሪካ ብቻ ሳይሆን ለዓለምም አሳሳቢ ነው።

ፕሮፌሰር ኖሃ ሃራሪ “ስታድግ ምናልባት ስራ ላይኖርህ ይችላል። . . . ከ2050 ዓመት በኋላ የስራ ገበያ ምን ዓይነት ሊሆን እንደሚችል አናውቅም” በማለት መጪዎቹ ዓመታት ባህሪ ምን ሊሆን እንደሚችል ያመላከቱትን ሀሳብ የተመለከተ ዜጋ የአፍሪካ ህጻናትና ወጣቶች የተጋረጠባቸውን ፈተና መረዳት ይችላል። አልፎም አፍሪካ ለዚህ ፈጣንና በቂ ምላሽ ካልሰጠች ሊገጥማት የሚችለው አደጋ መገንዘብ ያስፈልጋል።

“ይህ ለአህጉሪቷ ሰላምና ደህንነት ከፍተኛ ስጋት ነው። ከዚህ አኳያ በአፍሪካ ያለውን የሰላም እጦት በዘላቂነት ለመፍታት በወጣቶች ጥቅምና ፍላጎት ላይ ማተኮር ተገቢ ነው” በማለት በአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን የትምህርት፣ የሳይንስ፣ የቴክኖሎጂና ፈጠራ ዘርፍ የሚዲያና ትምህርት ጥምረት የአፍሪካ ልማት ዋና ዳይሬክተር ዶክተር ላዎል ኮል ገልጸውታል። አፍሪካ የትኩረት አቅጣጫዋ ተገቢ ቢሆንም በምን ያህል ጥራትና ብቃት የሚለውን ጥያቄ



47

የመፈተሽ ተገቢነት ሊያነጋግር አይችልም።

የለውጥ ንፋስ ለአፍሪካ

አድዋ በቅኝ ግዛት መንፈስ እየተመሩ የመጡትን ወራሪ ሃይሎች መርታት እንደተቻለ ያሳየ የድል ብስራት ነው። አፍሪካዊያን ባላቸው መሳሪያ በመታገል ከቅኝ ግዛት ቀንበር መውጣት እንደሚችሉ ፋና ወጊ የሆነ የድል ብርሃን ነው። አፍሪካዊያን ከቅኝ ግዛት ተላቀው ሁሉም ነጻነታቸውን ሲያውጁ ለዜጎቻቸው ኩራትና ደስታ ምንጭ ሆነዋል።

የDead AiD መጽሀፍ ጸሀፊ ዳቢሳ ሞዮ “በ1970 አፍሪካዊ መሆን ደስታ የሚሰጥ ነበር። ብዙዎቹ አገሮች ነጻነታቸውን መቀዳጀታቸው ጥልቅ የሆነ የክብር ስሜት፣ ለራስ ክብር መስጠትና ለቀጣዩ ተስፋ መሰነቅ አስችሎናል” ስትል የገለጸችው ከቅኝ ግዛት መላቀቅ መቻል አፍሪካዊያን በመጀመሪያው ወሳኝ የለውጥ ማዕበል ሀሴትን የተቀዳጁበት አድርገን መውሰድ እንችላለን።

አፍሪካ አሁንም 21ኛውን ክፍለዘመን የሚመጥን ለውጥ ትሻለች። ፖለቲካዊ፣ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ለውጥ ያስፈልጋታል። አዲሱን የቅኝ ግዛት ዓላማ ለማክሸፍ የሚቻለው ከዳር እስከ ዳር በጋራ በመቆምና ፈተናዎችን ለማለፍ የሚያስችል ለውጥ በማካሄድ ነው።

በኢትዮጵያዊያን የተጀመረው “#በቃ” ዘመቻ በተግባር በመደገፍ ፖለቲካዊ ለውጥ ማምጣት ካልተቻለ

ከመጀመሪያው የከፋ ደረጃ ላይ መገኘት አይቀሬ ሊሆን ይችላል። ጽንፈኝነትን መዋጋት፣ ሽብርተኝነትን መከላከልና ሰላም ማረጋገጥ ያስፈልጋል። ኢ ፍትሃዊነትን ተጠቃሚነትን ማስወገድ፣ መልካም አስተዳደርን ማስፈንና ዴሞክራሲን መገንባት ጊዜው ይጠይቃል። ይህን እውን ለማድረግ የሁሉም አካላትን ተሳትፎ ይጠበቃል። የህዝቡ፣ የምሁሩ፣ የፖቲከኛውና የሲቪክ ማህበራት ርብርብ አስፈላጊ ነው።

“በቀጣይ አስርታት የፖለቲካ ትጋት፣ የፖለቲካ ምናብ፣ የፖለቲካ ፈጣሪነትና የፖለቲካ መሪነት ከመቼውም ጊዜ በላይ ያስፈልጋል። እጅግ ታላቅ የሆነ የመሪነት ብቃትን ይጠይቃል” በማለት የpost - capitalist socity መጽሀፍ ደራሲ ፒተር ኤፍ ደሩከር የገለጹት አፍሪካውያን መሪዎችና ፖለቲከኞች ሊያጤኑት የሚገባ ነጥብ ነው።

21ኛ ክፍለዘመን በአዲስ መንፈስ

ኢትዮጵያ በለውጥ ሂደት ውስጥ ናት። ለውጧ በብዙ ፈተናዎች የታጀበና ጋሬጣ የበዛበት ቢሆንም ለውጧን አስቀጥላ በመጓዝ ላይ ትገኛለች። ዘመኑን በሚመጥን አካሄድ ለመጓዝ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ማሻሻያዎች በማድረግ ላይ ትገኛለች። ሌሎች የአፍሪካ አገሮች በለውጥ ጎዳና ውስጥ መሆን ይጠበቅባቸዋል። አፍሪካዊያን ህብረታቸውን ማጠንከር የግድ ይላቸዋል። ዛሬ በተለያዩ አካባቢዎች የሚታዩት ኢ ህገመንግስታዊ

ድርጊቶች መወገዝ ብቻ ሳይሆን ዳግም እንዳይታሰቡ አድርጎ መፍትሄ መስጠት ይገባል።

አፍሪካ በዓለም አቀፍ መድረኮች ተገቢውን ስፍራ ማግኘት አለባት። ሁሉም አገራት ተገቢውን ትኩረት ሰጥተው በቁርጠኝነት መስራት ይኖርባቸዋል። በተባበሩት መንግስታት የጸጥታው ምክር ቤት አፍሪካ ቋሚ መቀመጫ እንድታገኝ የቀረበው ጥያቄ ተገቢና ወቅታዊ ነው። ይህን እውን ለማድረግ የውስጥ ጥንካሬ፣ ሰላምና መረጋጋት ያስፈልጋል።

የአድዋ ድል በጥንካሬ የተገኘ ነው። አፍሪካዊያን ይህን መንፈስ ዳግም መላበስ አለባቸው። ዛሬም ድል ለማብሰር አንድነት፣ ትብብርና በጋራ መስራት ትልቁ መሳሪያ ነው። የታሪክ ምሁሩ ፕሮፌሰር አደም “መሪዎች በአፍሪካ ሕብረት መሰብሰብ፣ መወያየት ብቻ አይደለም። የመጀመሪያ ዓላማቸው ድህነትን መዋጋት፣ ስራ አጥነትን ማቃለል፣ የሕዝብን አንድነት መመስረት ነው። በአፍሪካዊነታችን መብታችን ተጠብቆ “አፍሪካዊ ነኝ” የሚለውን አርማ ይዘን በአንድ ብንቀሳቀስ በአጭር ጊዜ አፍሪካ ከድህነት፣ ከጥገኝነት ትወጣለች። ከውጭ ጣልጋ ገብነት የምትድንበት ሁኔታ ይኖራል” ብለዋል።

“ለአፍሪካዊያን ጥንካሬ፣ የአድዋ ጦርነት ውጤት የጀርባ አጥንት ጥንካሬ ሰጥቷታል” እንደሚባለው ዛሬም በተመሳሳይ መልኩ መድገም ያስፈልጋል፤ ይገባል።



48

የዳግማዊ አድዋ ብስራት

ዐብይጉዳይ



49

መንደርደሪያ

ሚራዥ በዐይኔ ሞልቷል። የዐይኖቼ ብሌን ሚራዥን ሰነጣጥቀው ክብረ-ሰማይ መሰል ውሃ ላይ አርፈዋል፤ ከተንጣለለ ሐይቅ መሃል። የቆምኩባት ኮረብታም ታሪክ ሆናለች። ከፊት ለፊት የተሰቀለ ‘የተባበሩ ክንዶች የፈጠሩት ታምር’ የሚለው አርበ ጠባብ ባነርም ይህን ያረጋግጣል። በታሪካዊ ስፍራ፣ ታሪካዊ ኹነት ታዳሚ መሆኔ ውስጤን ደስታ ንጦታል።

ስመ-ግዙፍ፣ ትዕምርተ-ደማቅ፣ ትውፊተ-ቱባ፣ ምስጢረ-ረቂቅ፣ ታሪከ-ጠሊቁ ፈለገ ግዮን እነሆ ብርሃን ሆኖ አየሁት። የሰከላው ጠበል፣ የአገሬ ተራሮች ብጣት፣ የጣና ሐይቅ ንጉስ፣ የምድራችን አፍላጋት አለቃ ዓባይ ውሃ ነዳጅ ሆኖ በራ። የጥንት ስልጣኔ የሚቶሎጂ ፍልስፍናዊ መሰረት፣ የምድራዊና ሰማያዊ እሳቤዎች ማጠንጠኛ፣ የማሾሪያው ዛቢያ ዲበ ኩሉ ተድርጎ የሚሳለው ጥቁር ዓባይ(ናይል) እነሆ መልኩን ለወጠ፤ ሌላ የትዕምርት ካባ ሊላበስ።

ዓባይ ወንዝ ለኢትዮጵያ የታሪክ ምዕራፍ መክፈቻና መዝጊያ በር ሆኖ ሊከተብ እነሆ ጉባ ሰማይ ሥር ታሪክ ሆነ። ‘ዓባይ ታሪክ ሆነ’ የሚያሰኘው የኹነቱ ከፍታም በሰው ልጆች ታሪክ አዲስ ምዕራፍ መክፈቻነቱ ዝናው ከናኘው ከአድዋ ድል ጋር በአንድምታም፤ በጊዜም ተገጣጠመ!!

እንዴት ቢሉ እነሆ…

በአየለ ያረጋል

የዳግማዊ አድዋ ብስራት



50

የዘመናት ጥንስስ ሲቀመስ

እድሜ ልኩን አፈር እየሸረሸረ

ዘርፎ እየሸፈተ - ጎረቤት ካደረ፤

እንዲያው አጉል ዝናው - ስሙ ከሚተርፈን

ምን አለበት አሁን - አባይ ጠላ ቢሆን ?

የኛ ወንዝ ሆኖ - ለኛ ካልገበረ

ስንዴ ገብስ አብቅሎ - ጎተራ ካልሻረ

በመስኖ ተጠልፎ - ጤፍ ካላዘመረ

ዓባይን ጠላ አርጎት - አገር በሰከረ።

እባክህ ጌታዬ - ልመናዬን ስማ

ወንዛችን እያሉ - ሕዝብም ከሚጠማ

ያው እንደልማድህ - ተዓምር ስራና

ዓባይን ወይን አርገው - “እፍ” በለውና።

ከዚያማ ምድረ አዳም - ካያለበት ወጥቶ

ሲፈልግ በባልዲ - ሲፈልግ ለግቶ

ቢሻው ዳር ተኝቶ - ቢሻው መሀል ገብቶ

ያንተን ጠበል ጣዲቅ - ጠጥቶ ጠጥቶ

. . . . ጠጥቶ፤ ጠጥቶ

. . . . በቃ !

ዓባይም አይቆምም፤ ጠጪም አያቆምም

ዓባይ ጠላ ቢሆን . . .!

ይህ የገጣሚና ጋዜጠኛ ሞገስ ሀብቱ(ኮሎኔል) ’ዓባይ ጠላ ቢሆን’ በሚል ርዕስ የጻፈው ግጥም ነው። መልዕክቱ ስለሚናገር ሌላ መናገር አይሻም። የዓባይ ወንዝ መመንጫዋ ኢትዮጵያ የወንዟን ታሪክና ይትባሃል ለመለወጥ ሀሳብና እንቅስቃሴዋ ውሎ አድሯል። ከዓባይ ወንዝ ኤሌትሪክ ኃይል አመንጭቶ የመጠቀም የሀሳብ ጥንስስን ወደ ተግባራዊ እንቅስቃሴ የቀየሩት ቀዳማዊ ዓፄ ኃይለሥላሴ ናቸው።

በወቅቱ የስራና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር የነበሩት ደጃዝማች ዘውዴ ገብረስላሴ(ዶክተር) እንደሚነግሩን ንጉሠ ነገሥቱ በ1950 ዓ.ም በኢትዮጵያዊያንና በአሜሪካዊያን ባለሙያዎች በተውጣጣ ቡድን በዓባይ ተፋሰስ ግድቦችን ለመገንባት ጥናት አስጀምረው ጥናቱ ከአምስት ዓመታት በኋላ በ314 ገጾች ተጠናቆ ቀርቦ ነበር። በጥናቱም 433 ሺህ 754 ሄክታር መሬት የሚያለሙ እና 8 ሺህ 660 ሜጋ ዋት በላይ ኃይል

የሚያመነጩ የኃይል ፕሮጀክቶች ተለይተዋል። ለዚህ ጥናቱ በወቅቱ 20 ሚሊዮን ብር(10 ሚሊዮን የአሜሪካ ዶላር ገደማ) ወጭ ተደርጓል። በዓባይ ተፋሰስ ቅድመ ጥናት መሰረትም የታላቁ ሕዳሴ ግድብ የተገነባበትን አካባቢ ጨምሮ 33 ግዙፍ የግድብ ፕሮጀክቶች ተለይተው ነበር። ንጉሱ ጥናቶቹን ካስጨረሱ በኋላ (ከፊንጫ ሃይድሮ ኤሌክትሪክ በስተቀር) ሁሉም ፕሮጀክቶችን ተግባራዊ ለማድረግ በውጫዊ ጫና አልተሳካላቸውም። ንጉሱም “ተተኪው ትውልድ ይገነባዋል” በሚል የራሳቸውን የቤት ስራ ሰርተው፣ ባይሳካም የቤት ስራውን ለተተኪ ትውልድ አደራ ጥለው አልፈዋል።

መጋቢት 24 ቀን 2003 ዓ.ም በመተከል ዞን ጉባ ወረዳ ላይ መሰረተ ድንጋይ የተቀመጠለት ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ፕሮጀክትም ወደ ግንባታ የገባው በቀደመ እርሾ ላይ ነበር። እነሆ እርሾው ተቦክቶና ተጋግሮ የምድራችን ረጅሙ ወንዝ ለኢትዮጵያም ብርሃን ፈነጠቀ፣ ተስፋው ተጨበጠ። ፈለገ ግዮን በጉባ ሰማይ ስር ለሚሊዮን ኢትዮጵያዊያን ሕልምና ምኞትን ሊያሟላ የተስፋ ፍሬው ተቀመሰ።

ዓባይ ወንዝ በኢትዮጵያዊያን ትውፊትና ይትባሀሉ የቁጭት፣ የቁዘማ፣ እንጉርጉሮና ወቀሳ ዜማ ሆኖ፣ በማደሪያ ቢስነቱ በሊቃውንትና ጠቢባን ዘንድ አርዕስት ሆኖ ለዘመናት ተወቅሷል። የዓባይ ውሃ ጠላ ሆኖ እንዲጠጣ፣ መና ሆኖ እንዲጎረስ፣ ሲሳይ ሆኖ እንዲቆረስ የእልፍ ኢትዮጵያዊያን ምኞት ነበር። በትችትና ምኞት፣ በተስፋና ወቀሳ የተወገረው የዓባይ ወንዝ ግንድ አዟሪነቱ ሊገታ፣ የልጅ ባዕዳነቱ ሊያከትም፣ ለማደሪያ ቢስነቱ ለከት ሊበጅለት... የተወጠነው በታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ጥንስስ ነበር። ግድቡም በሕዝብ የድጋፍ ማዕበል ታጅቦ፣ በጠላት ዐይን ተገርምሞ፣ ዳፋና ተግዳሮቶች ተሻግሮ ከ11 ዓመት በኋላ... የተስፋ ፍሬ ተቀመሰ። ከ375 እስከ 400 ሜጋ ዋት የሚያመነጩ 13 የኃይል ማመንጫ ዩኒቶች/ተርባይኖች መካከል 10ኛዋ ተርባይን ስራ መጀመሩ ተበሰረ።

ርዕሰ ብሔር ሣሕለወርቅ ዘውዴ የዓባይ ጉዳይ የነበረውን የትውልድ ቅብብሎሽ፣ አብሮነትና መደማመጥ ውጤት አስመልክተው ‘‘በንጉሡ ራዕይ ተጀመረ፤ ድፍረት ተከተለ፤ አስቀጣዮች መጡ፤ ግድባችን ኃይል አመነጨ! እንኳን ደስ አለን!.... ሀሩርን ተጋፍጦ፤ ጤናውን ሕይወቱን ሰዉቶ፤ የአገርን ጥቅም የሙጥኝ ይዞ ተደራድሮ፤ ካለው አካፍሎ፤ አገሬ ብሎ ለተነሳ ሁሉ ቀኑ የእናንተ ነው፤ እጅ እነሳለሁ… ከተነጋገርን፣ ከተደማመጥን፣ ከተግባባን፣ ከተከባበርንና ከተባበርን የሚያቅተን ነገር የለም፤ ከሚያዘናጋንም እንራቅ” በማለት ነው ደስታቸውን የገለጹት። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ በበኩላቸው “ግድቡ ለአህጉራችን እና አብረናቸው ሠርተን በጋራ ለመጠቀም ለምንሻ የታችኛው ተፋሰስ አገራት የምሥራች ነው። ለኢትዮጵያ

የብርሃን መባቻ ነው” ብለውታል።

በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል፣ በጉባ ወረዳ የሚገኘው ታላቁ ሕዳሴ ግድብ ዋናው ግድብ ከባሕር ጠለል በላይ 640 ሜትር ከፍታ አለው። ግድቡ ሲጠናቀቅ 1 ሺህ 680 ስኩዌር ኪሎ ሜትር ስፋት ይኖረዋል። ውሃ የሚተኛበት መሬትም 246 ኪሎ ሜትር ሲረዝም ግድቡ 74 ቢሊዮን ኪዩቢክ ሜትር ውሃ መጠንም ይይዛል። የጣና ሐይቅን ሁለት ዕኩል እጥፍ የሚያህል ሰው ሰራሽ ሐይቅም ይፈጠራል። የግድብ ግንባታ ሲጠናቀቅ 5 ሺህ በላይ ሜጋ ዋት ኃይል ያመነጫል። በግድቡ ግርጌ እና ቀኝ የሚገኙ 13 ተርባይኖችን ከዋናው ግሪድ/የኃይል ቋት/ጋር በ500 ኪሎ ቮልት እና በ400 ኪሎ ቮልት ማስተላለፊያ መስመሮች ተሰርተዋል። በአፍሪቃ ውስጥ ትልቁ የኤሌትሪክ ኃይል ማመንጫ ግድብ ይሆናል።

የታላቁ ሕዳሴ ግድብ አገራዊ፣ አፍሪካዊና ዓለም አቀፋዊ ሚና

የምስራቅ አፍሪካ የውሃ ማማ የምትሰኘው ኢትዮጵያ ከየትኛም አገር ውሃ አትቀበልም። ጎረቤቶቿን ግን ከተራሮቿ ምንጭ እያፈሰሰች ታረሰርሳለች። በሕዝብ ቁጥሯ ከአፍሪካ ሁለተኛ ደረጃ የተቆናጠጠችው የውሃ ማማዋ አገር ውሃ ተጠምታለች፤ ብርሃን ርቋታል። ከ60 በመቶ ሕዝቧ በኤሌክትሪክ ኃይል እጦት በጨለማ ይማስናል። በሚሊዮን የሚቆጠሩ ዜጎቿ የአየር ንብረት መዛባት በወለደው ተደጋጋሚ ጎርፍና ድርቅ አደጋ ሳቢያ በርሀብና እርዛት ሰለባ ሆነዋል። ኢትዮጵያ ነዳጅ ብቻ ሳይሆን ገቢና ወጪ ንግዶችን የምታሳልጥበት የባሕር በር ወይም ወደብ የላትም።

በዚህ መሃል የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ዕውን መሆን ብዙ ታሪክ ይቀይራል። ለኢትዮጵያ ምጣኔ ሀብትና በድህነት አረንቋ ለሚማቅቁ ሕዝቦች በርግጥም የብርሃን መባቻና የተስፋ መጨበጫ ነውና። ግድቡ በገንዘብ አይተመኔ አበርክቶትም ይወልዳል፤ ልክ እንደ አድዋ አገር ክብርና ሉዓላዊነትን!

ግድቡ ሲጠናቀቅ ሰፊ ዕድሎችን ያመጣል። በግድቡ ብዙ ደሴቶች ይፈጠራሉ። ይህም ለቱሪዝም መዳረሻነቱ ዓይነተኛ ሚና አለው። ከኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጫነቱ ባሻገር ለዓሣ ምርት፣ ለመዝናኛና ትራንስፖርት ዘርፎች ከፍተኛ ኢኮኖሚያዊ ዕድሎችን ይፈጥራል። ከቱሪዝም ዘርፍ ባሻገርም በኃይል አቅርቦት ችግር ለሚፈተነው የማምረቻ/የማኑፋክቸሪንግ/ ዘርፍ ትልቅ እፎይታ እንደሚፈጥር መገመት አያዳግትም።

ግድቡ ለጎረቤት አገሮችና ለቀጣናዊ ትብብር የሚኖረው ሚናም ጉልህ ነው። ግድቡ ሲጠናቀቅ ኤርትራ፣ ጅቡቲ፣ ኬኒያ፣ ሱዳንና ደቡብ ሱዳን ከግድቡ ኤሌክትሪክ ኃይል ተጠቃሚ ይሆናሉ። ኢትዮጵያ ከግድቡ የኃይል ፍጆታዋን ካሟላች በኋላ 2000 ሜጋዋት ገደማ ለጎረቤት አገሮች በመሸጥ በዓመት ከግማሽ ቢሊዮን ዶላር በላይ ገቢ ማድረግ እንደምትችል የባለሙያዎች



51

ግምቶች ተቀምጠዋል። ከኃይል ተጠቃሚነቱ ባለፈም ሌሎች የተፋሰሱ አገሮች በቅኝ ግዛት ውሎችና ሴራዎች ሳይበገሩ የተፈጥሮ ሀብታቸውን እንዲጠቀሙ፣ የዘመኑ አፍሪካዊን የመበዝበዝና አደህይቶ የመግዛት የእጅ አዙር ቅኝ ግዛት ለማስቆም የሚካሄደው ትግል እንዲፋፋም ታላቁ ሕዳሴ ግድቡ ጠንካራ ማነቃቂያ ይሆናል። የአገሮቹ በኢኮኖሚ መተሳሰርም አድዋ ድል የወለደው የፓን አፍሪካዊነት ስሜት እንዲጎለብት፣ የአፍሪካ ነፃ ንግድ ቀጣናም በብዙ አማራጮች ገቢራዊ እንዲሆን ያስችላል።

በአገሮቹ መካከል ኢ-ፍትሃዊ የውሃ አጠቃምን ችግር ያቃልላል። እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ ኢትዮጵያ በዓባይ ወንዝ ላይ ባይተዋር ነች። ግብጽና ሱዳን ግን ፍጹም ተጠቃሚ ናቸው። ለምሳሌ ግብጽ ከሦስት ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬት በመስኖ ታለማለች፤ ሱዳን ደግሞ ከአንድ ነጥብ ስምንት ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬት መስኖ ተጠቃሚ ሆናለች። ኢትዮጵያ ግን ምንም። ኢትዮጵያ ኃይል አመንጭታ ለመጠቀም መነሳቷ ሁልጊዜም የብቸኝነት ሸውራራ አጠቃቀምን ታሪክ ማስቀጠል ለምትሻው ግብጽ የራስ ምታት ሆኗል። በዘርፉ ባለሙያዎች ሀተታ በግብጽ ግድቦች 45 በመቶ ውሃ በከንቱ በትነት ይባክናል። በኢትዮጵያ በሚገነባው ግድብ ግን የዚህ ዓይነቱ ብክነት አይኖርም። ከታላቁ ሕዳሴ ግድብ የሚተነው መጠን ከግብጹ አስዋን ግድብ ጋር ሲነጻጸር በ250 በመቶ ይቀንሳል።

የግብጽ መንግሥት በየጊዜው የሚያወጣው አመክንዮም እርባና የለውም። “ከዓለም አቀፍ የውሃ ሕግም ሆነ ከሞራል የተፋታ አካሄድ ነው” ይሉታል ምሁራን። ግብጽ በሃሰተኛ መረጃ ህዝቧን በማደናገርና በማሸበር የውስጥ ፖለቲካ መጠቀሚያ ለማድረግ ወይም ኢትዮጵያ በተፈጥሮ ሀብቷ እንዳትጠቀም ጫና ለማሳደር ካልሆነ የኃይል ማመንጫ ግድብ በግብጽ ላይ ተጨባጭ ጉዳት እንደማያመጣ ይታወቃል።

ግድቡ በየዓመቱ በሚያጋጥማት ከፍተኛ የጎርፍ መጥለቅለቅ እና የሚያደርስባት ጉዳት ላስመረራት ሱዳንም የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ጠቀሜታው ጉልህ እንደሆነ ከራሳቸው በላይ ምስክር የለም። ባለሙያዎች እንደሚሉት ደግሞ በኢትዮጵያ የሚገነቡ የኃይል ማመንጫ ግድቦች ተርባይኑን እየመቱ ስለሚያልፉ የሚጠራቀመው ውሃ በሰከንዶች ልዩነት በሚፈሰው ውሃ ወንዙ ከፍተኛ መጠን ያለው ፍሰት እንዲኖር ያስችላል። ይህም ወንዙ ግድብ ሳይኖር ከሚፈሰው ይልቅ በጋ ከክረምት ከግድቡ በቋሚነት የሚፈሰው ውሃ ለታችኛው ተፋሰስ አገሮች የውሃ አቅርቦት አስተማማኝ ነው። ከዚህ አኳያ ታላቁ ሕዳሴ ግድብ ለሁለቱ አገሮች መርዶ ሳይሆን በረከት ይዞ የመጣ ነው። ሌሎች ጎረቤት አገሮችን በረከሰ ዋጋ የኃይል ተጠቃሚ ስለሚያደርግ ግድቡ ለቀጣናው አገሮች እንጀራ እንጂ መከራ ይዞ እንዳልመጣ ደፍሮ መናገር ይቻላል።

ከእነዚህ ጠቀሜታዎች አኳያ ኢትዮጵያ በሱዳንና ግብጽ ጫና ሊደረግባት ቀርቶ “ካሳ መጠየቅ ነበረባት” የሚሉ ምሁራንም አሉ። ዋናው ነጥብ ግን በዚህ ሁሉ አዙሪትና ሴራ መሃል፣ በውስጣዊ ፈተናዎች እየተፈተነች ታላቁ ሕዳሴ ግድብ በአንዲት ተርባይንም ቢሆን ለአቅመ ኃይል ማመንጨት መድረሱ ለሌሎች አፍሪካ አገሮች ተምሳሌትነቱ ከፍተኛ ነው።

ታላቁ ግድብ ከኃይል አቅርቦቱ በተጨማሪ በዲፕሎማሲ እና በተለያዩ መስኮች ሁሉን አቀፍ ጥቅም ይሰጣል። በታዳሽ ኃይል ረገድም ከኢትዮጵያ አልፎ ለዓለም የሚተርፍ ትልቅ አበረክቶት አለው። የግድቡ ግንባታ ተሳታፊ የሆነው ታዋቂው ተቋራጭ የሳሊኒ ኩባንያ ባለቤትና ዋና ስራ አስኪያጅ ፔድሮ ሳሊኒ በኃይል ማመንጫው ብስራት ኹነት ላይ ባደረጉት ንግግር “ራሴን እንደ ኢትዮጵያዊ ስለምቆጥር ለእኛ ለኢትዮጵያዊያን የግድቡ ኃይል ማመንጨት ጅማሮ ትሩፋቱ መልከ ብዙ ነው። ዓባይ ፈጣሪ ኢትዮጵያን የቸራት ነጭ ነዳጅ ነው” ሲሉ ገልጸውታል። ይህ ነዳጅ ግን በታዳሽ ኃይል ማመንጫነት ሲውል ለምድራችን ያለው አስተዋጽኦ ከአየር ንብረት ለውጥ ጋር አዛምደውታል።

እንደ እርሳቸው ገለፃ፤ የዓለማችን ዘላቂ የልማት ግቦች አንዱ ለአየር ንብረት የማይበገር ኢኮኖሚ መገንባት ነው። “ኢትዮጵያ በዚህ ረገድ የድርጊቱን ግቦች ለማሳካት ከተጓዘችባቸው ተግባራት ትልቁ ማሳያ የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ነው” ብለዋል። ግድቡ የእስካሁን ጉዞው ግንባታው እንዳይሳካ በርካታ ጠላቶች ቢረባረቡም ውጣ ውረዶችን አልፎ የብርሃን መባቻውን በማየታቸው ደስታ ተስምቷቸዋል።

በጥቅሉ ኢትዮጵያ በዓባይ ወንዝ ላይ የምትገነባው የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ለአየር ንብረት ለውጥ ዓይነተኛ መፍትሔ ነው። ከኢትዮጵያና አፍሪካ አልፎ ለዓለም ሕዝብ አዎንታዊ አበርክቶት አለው። የኢትዮጵያ ተራሮች መራቆት አንዱ መንስኤው አንዱ ኋላቀር ግብርና እና ለማገዶ የሚሆን እንጨት በመፈለግ የሚፈጸም ደን ጭፍጨፋ ነው። እናም የመንግሥታቱ ድርጅት ኢትዮጵያን የታዳሽ ኃይል ከማደናቀፍ ይልቅ ድጋፍና ማበረታቻ ቢሰጥ ለአረንጓዴ ኢኮኖሚና አካባቢ ጥበቃ ግቦች ስኬት ያግዛል። በሌላ በኩል የሰሐራ

በርሃማነት መስፋፋትና ድርቅን መቋቋም የሚቻለው አረንጓዴ ግድግዳ (ግሪን ዎል) የሚሰኘውንና ከጋምቤላ እስከ ምዕራብ ጎንደር የሚዘረጋውን አረንጓዴያማ አካባቢ ከታላቁ ሕዳሴ ግድብ መገንባትና መልማት ጋር ከታየ ከፍተኛ አቅም የሚፈጥር ነው።

እናም ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ በሁሉም መስክ ሲፈተሽ በማንም ላይ ጥቅም እንጂ አንዳች ጉዳት የለውም።

ዳግማዊ አድዋ

ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብን ሊሂቃኑ በዳግማዊ አድዋነት ይመስሉታል። ዳግማዊ አድዋ ከማለታችን በፊት አድዋን በወፍ በረር መጥቀስ ያሻል።

አድዋ ዝም ብሎ ድል ሳይሆን እንደ ዓባይ ወንዝ መልከ ብዙ፣ ትዕምርቱ የሰፋ፣ ቀለመ ደማቅ፣ አድማስ ዘለል ትሩፋቶችን አዋልዷል። አገራዊ፣ አህጉራዊና ሉላዊ እሳቤን ለውጧል። ድሕረ አድዋ ድል ኢትዮጵያ ውስጥ ዘመናዊነት እንዲስፋፋ፣ የባቡር፣ ስልክ፣ ትምህርት፣ ፖስታ፣ ቴሌ፣ መንገድና ሌሎች መሰረተ ልማቶች እንዲዘረጉ፤ ኢትዮጵያ የትኛውም አፍሪካዊ አገር ያላገኘውን የራሷን የፖለቲካ ኢኮኖሚ እንድትመራ አስችሏታል።

ታላቁ የአድዋ ድል ዘመናዊት ኢትዮጵያን ከጥንታዊ ታሪኳ ጋር ያዋደደ፤ የጥንቶቹን አባቶቻችን ጀግንነትና ለአገር ያላቸውን ፍቅር ያስመሰከረ፣ የነፃነት አይበገሬነት ወኔን ያሳዬ፣ የሕዝቦች አንድነት ህያው ማሳያ ታሪካዊ ኹነት ነው። ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ መድረኮች እንድትታወቅ፣ ዝናዋ እንዲናኝና እንድትከበር ምክንያት ሆኗል፤ ለኢትዮጵያ የዲፕሎማሲ ማዕከልነት እርሾ ሆኗል። ኃያላኑ የምዕራብ አገሮች ኤምባሲዎቻቸውን በአዲስ አበባ ከፍተው ለኢትዮጵያ ነፃና ሉዓላዊነት ‘አሜን’ ብለው ዕውቅና ሰጥተዋል። ቅኝ ገዥዎች የአገዛዝ ፖሊሲያቸውን ጭምር እንዲመረምሩ ያደረጋቸው አድዋ፤ ከድሉ ማግስት ኢትዮጵያ ሉዓላዊት አገር መሆኗ እንዲረጋገጥና ድንበሯን እንድትካለልም አስችሏታል።

ቀድሞውኑ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ይዘት ቢኖረውም በኋላ ግን የአፍሪካዊያን የነፃነት እንቅስቃሴ ትዕምርት ሆኗል፤ የ‘ኢትዮጵያዊነት’ ጽንሠ ሃሳብ። እናም አድዋ



52

ለ’ኢትዮጵያዊነት’ እና ለ’ፓን አፍሪካዊነት’ ጉዞ መሰረት ሆኗል፤ ቅኝ ግዛት እጣ-ፈንታ አለመሆኑን አብስሯል። በርካታ የአፍሪካ አገሮች ከቅኝ ግዛት ቀንበር ሲላቀቁ አረንጓዴ፣ ቢጫና ቀይ ቀለማትን ከኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ ቀለማትን ተሻምተዋል። አድዋ በሌሎች አገሮች ሕዝቦች የነፃነት ትግል ተምሳሌት ሆኖ በተለይም የጥቁር ዓለም ሕዝቦችን ያነሳሳ፣ የኢትዮጵያዊነት መንፈስ በዓለም አቀፍ ደረጃ እንዲቀነቀን ያስቻለ ድል ነው።

ከአድዋ ድል በኋላ ኢትዮጵያዊያን የጀግንነት፣ የአገር ፍቅር፣ የአገር ሉዓላዊነት የማይበገር ወኔና ስነ ልቦና እሴቶችን አዳብሯል። ለአብነትም በአምስት ዓመቱ የፋሽስት ጣሊያን ወረራ፣ በደርግ ዘመን በነበረው የሶማሊያ ወረራ እንዲሁም በባድመ የነበረው የኢትዮጵያዊያን ኅብረት ከአድዋ የተገኘ የአብሮነትና አይበገሬነት እሴት መሆኑን የታሪክ ምሁራን ያብራራሉ። በርግጥ ኢትዮጵያዊያን በአድዋ ጦርነት ርህራሄንና ሰብዓዊነትን በቅኝ ገዥነት መንፈስ ለሰከሩት ነጮች አስተምረዋል።

ፕሮፌሰሩ ባሕሩ “ከዳር እስከ ዳር ነው የተነሳው። ያኮረፈም ሳይቀር ገብቷል። ያኮረፈም ቢሆን በምንም መልኩ አያገባኝም ያለ የኢትዮጵያ ክፍል አልነበረም።…. ያ ኢትዮጵያዊ ስሜት ነው። ዋናው የአድዋ እሴት ይሄ ነው” ይሉታል።

ከእነዚህ የድሕረ አድዋ ትሩፋቶች አኳያ ታላቁ ሕዳሴ ግድብ ሲፈተሽ በእርግጥም ዳግማዊ አድዋ ያሰኘዋል። ታላቁ ሕዳሴ ግድብ በአፍሪካ አህጉር የድሕረ ቅኝ ግዛት አስተሳሰብን በመስበር፣ የእጅ አዙር ቅኝ ግዛትን በማስወገድና የኢትዮጵያን ትናንታዊ ፋና ወጊነት ዛሬም ለመድገም የአፍሪካ ሕዳሴ ያሰኘዋል። በተለይም ኢትዮጵያ አድዋ ላይ በየካቲት 23 ቀን 1888 ዓ.ም ድል በተቀዳጀችበት ከ126 ዓመታት በኋላ ከምዕራባዊያ ድህረ-ቅኝ ግዛት ጣልቃገብነትና የዓረቡ ዓለም ጫናን ተቋቁማ በልጆቿ የተባበረ ክንድ ገንብታ ለድል በበቃችበት ወርሃ የካቲት ግድቡ ብርሃን መስጠቱ ሌላው የጊዜ ግጥምጥሞሽ ነበር። ይህ የድል ጅማሮ ብስራትም አገሬውን በደስታ አስፈንድቋል።

የምዕራብ ዘመም ዓለም አቀፋዊ ጫናዎች ብርታትና የግድቡ የስኬት ግስጋሴ አንዱ መገለጫ ነው። አሜሪካንን ጨምሮ ምዕራባዊያን አገሮች ግድቡን ሂደት በድርድር ሰበብ በማዘግየትና እንዲቀር በማድረግ ኢትዮጵያን ለማሽመድመድ ያልሞከሩት እርምጃ የለም። ጉዳያቸውን ለማስፈጸም በሚጠቀሙበት በሰላምና ፀጥታ ስጋት ላይ ብቻ በሚመክረው በጸጥታው ምክር ቤት የቀረበ ብቸኛው ጉዳይ ሕዳሴ ግድብ ነው።የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ውስጣዊና ውጫዊ ፈተናዎችን ተሻግሮ ለዚህ ብስራት መብቃቱ ለአፍሪካዊያን አንድምታው ከፍተኛ ነበር።

ኢትዮጵያ በመልክዓ-ምድራዊ አቀማምጧ ሳቢያ ዓባይ

ወንዝን እንዳትጠቀም ጫና እንዲበረታ ሰበብ ሆኗል። ከጥንትም ጀምሮ ምዕራባዊያንና ዓረቡ ዓለም ኃይሎች የዓለምን ምጣኔ ሀብት የሚዘወርበትን የቀይ ባሕር ጂኦ-ፖለቲካን ለመቆጣጠር ዓባይ ወንዝን መቆጣጠር ሁነኛ አማራጭ አድርገው በመውሰዳቸው አንድም ኢትዮጵያን ማንበርከክ፣ አንድም የተፈጥሮ ሀብቷን ተጠቅማ ኃያል አገር እንዳትሆን ሳንካ ሆነው ኖረዋል። እናም ከ60 ዓመታት በፊት የተጠነሰሰው ዓባይን ገድቦ የመጠቀም እርምጃ በቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ቢጀመርም በዓለም አቀፍ ጫና ብድር በመከልከሏ አልተሳካላትም። ዘመናትን አልፎ በፈታኝ ጫናዎች ውስጥም ተሁኖ በዚህ ትውልድ ጥረት ይህን ሕልም ለማሳካት የተወጠነው ጥንስስ ፍሬ ማፍራቱም የኢትዮጵያን በጽናትና በትግል ጠላትን የማሳፈር ትናንታዊ እሴት ማሳያ በመሆኑ እንደ አድዋ ድል የአሸናፊነትና የምዕራባዊያንን የተዛባ ትርክት የመለወጥ ታሪክ ይሆናል። የዚህ ዘመን ትውልድ ገድልና አሻራ በመሆኑ ዳግማዊ አድዋ ያሰኘዋል።

ኢትዮጵያ ካለ ማንም ውጫዊ ኃይል ድጋፍ በራሷ አቅም ለመገንባት ወስና የገባችበት እና በማገባደድ ላይ ያለችው ፕሮጀክት ነው። በ4 ዓመታት ውስጥ በ78 ቢሊዮን ብር ያልቃል የተባለው ይህ ግድብ በአሸባሪው ህወሓት መሰሪ ስርዓት ብልሹ አሰራር ከመጓተቱ ባለፈ እስካሁን ከ162 ቢሊዮን ብር በላይ ወጪ ተደርጎበታል፤ እስኪጠናቀቅም 220 ቢሊዮን ብር በላይ ይፈጃል ተብሎ ይጠበቃል። ይህን ያህል ግዙፍ ሀብት ወጭ የተደረገው ግን ያለምንም የውጭ እርዳታ እና ድጋፍ ከኢትዮጵያ ሕዝብ እና መንግሥት ብቻ ነው። አገሬው በዘመናት ቁጭት ተነሳስቶ በስጦታና ቦንድ ግዥ አንጡራ ሀብቱን እየለገሰ የገነባው የመላው ኢትዮጵያዊ የላቡና ደም ግድብ ነው። ይህም በጋራ ትብብር የተገነባው ይህ ግድብ የነፃነት፣ ጥገኝነትና ተረጂነትን ድል የመንሳት፣ ጥርስን ነክሶ በተደረገ ውስጣዊ ተጋድሎ አቅምን የመገንባት ፕሮጀክትን የድል ጮራ ያሳዬና የይቻላል መንፈስን ያጎላ በመሆኑ ‘አድዋነት’ ይሆናል።

ለዓመታት በግብጽ፣ በሱዳንና በኢትዮጵያ መካከል ከተደረገው የሦስትዮሽ ድርድር አልፎ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የጸጥታው ምክር ቤት የደረሰ ጉዳይ ነው። ጸጥታው ምክር ቤት የግድቡን ውዝግብ ሰምቶ ወደ አፍሪካ ሕብረት እንዲመለሱ ምክር ለግሶ አልፏል። አፍሪካ ሕብረትን ጨምሮ በተለያዩ አሸማጋዮች እልባት እንዲያገኝ ቢሞከርም፣ በእንጥልጥል ላይ ነው። የድርድሩ አለመሳካት ሰበቡም በግብጽ በኩል የሚንጸባረቅ የቅኝ ግዛት አስተሳስብ ነው። ግብጽ የቅኝ ግዛት ውሎችን ሙጥኝ ብላ ኢ-ፍትሃዊና አግላይ የሆነውን ስምምነት ተቀባይነት እንዲያገኝ ጫና ብታደርግም ኢትዮጵያም የቅኝ ግዛት እሳቤውን እየተዋጋች ነው።

ኢትዮጵያ በሌለችበት በጎርጎሮሳዊያኑ አቆጣጠር 1959 በሱዳንና ግብጽ መካከል የተፈረመው ስምምነት በዓባይ

ወንዝ 77 ቢሊዮን ሜትር ኪዩብ ውሃ ለምታመነጨው ኢትዮጵያ ፍጹም ውሃ ይነፍጋል፤ ተፈጥሯዊና ሕጋዊ መብት ይነጥቃል። በአንጻሩ በዓባይ ወንዝ ምንጭነት ድርሻ የሌላቸው የታችኛው ተፋሰስ አገሮች ለግብጽ 55 ነጥብ 5 ቢሊዮን ኪዩቢክ፤ ለሱዳን ደግሞ 18 ነጥብ 5 ቢሊዮን ኪዩቢክ ውሃን ይፈቅዳል። ግብጽ “ግድቡ በመገንባቱ ወደ ግዛትዋ የሚፈሰው የውሃ መጠን ይቀንስብኛል” በሚል ሰበብ ኢትዮጵያ ከወንዟ እንዳትጠቀም ለዘመናት የሄደችበትን ትግል የሕዳሴ ግድብ ፕሮጀክት ዕውን እንዳይሆን የተቻላትን ሁሉ ስታደርግ ቆይታለች። ኢትዮጵያ በበኩሏ ግድቧ ከድህነት መውጫ፣ የዜጎቿን ተጠቃሚነት ማረጋገጫ እንጂ የተፋሰሱን አገሮች እንደማይጎዳ አበክራ አሳስባለች።

እናም ግብጽ በቅኝ ግዛት ስምምነት ሙጥኝ ብላ ታሪካዊ ተጠቃሚነት ላይ ስታተኩር ኢትዮጵያ በበኩሏ አግላይና ኢ-ፍትሃዊ ስምምነቱን እያወገዘች፤ ሉዓላዊነትን እንደሚጥስ በመከራከር ውድቅ እያደረገች እስከዛሬ ዘልቃለች።

በዚህ ከጉባ እስከ ፀጥታው ምክር ቤት በደረሰው ግድብ በተለይም ከሙሌቱ ጋር ተያይዞ አሳሪ ስምምነት ሳይኖር መከናወን የለበትም በሚል ግብጽና ሱዳን ቢሞግቱም በ2012 እና በ2013 ክረምቶች ሙሌቱ በተሳካ ሁኔታ ተከናውኗል። አሁን ደግሞ ኃይል ማመንጨት ጀምሯል። ይህም የጠላቶችን ጫና ተቋቁማ የመጀመሪያውን ፍሬ የማየት የድል ጮራነት ነው።

ከሁሉም በላይ ደግሞ ከላይ እንደተጠቀሰው ግድቡ ልክ



53

እንደ አድዋ አገር ክብርና ሉዓላዊነት ትዕምርት ነው!!

በጉባ ሰማይ ስር የከረሙ ፅኑ እጆች

የዓባይ ወንዝ የብርሃን ወጋገን ሲፈነጥቅ በተስፋ የናፈቁ መላ ኢትዮጵያዊያን በሐሴት ፈንድቀዋል። ለ11 ዓመታት ውሎ አዳራቸውን በጉባ ሰማይ ስር ካደረጉ ሠራተኞች ፌሽታ ጋር ግን አይስተካከልም። ከግድብ ከቁፋሮ እስከ ኃይል ማመንጨት ጅማሮ የዘለቀው ጉዞ ውጫዊና ውስጣዊ ጫናዎች ባሻገር በግንባታ ሂደቱ ያጋጠሙ ውጣ ውረዶች ሳይበግሯቸው አልፈዋል። ከግድቡ ውጥን እስከ አሁኑ አካለ መጠን መድረስ ከጉልበት ሠራተኞች እስከ ከፍተኛ መሃንዲሶች ካለ ፆታ ልዩነት የእልፍ የግንባታ ሠራተኞች መስዋዕትነት ከፍለዋል። የላብና ድካም ውጤታቸው ዓባይ ወንዝ ብርሃን ሆኖ ማየት ነበርና ድካማቸው ብርሃን ሆኖ ሲመለከቱ ሐሴታቸው ከቃላት በላይ ነው። በአፍሪካ አህጉር ግዙፍነትን በተላበሰው ግድብ ግንባታ ላይ አሻራቸውን ያኖሩ ክንዶችና አዕምሮዎች ለመጀመሪያ ጊዜ ደስታን ያጣጣሙበት ቅጽበት ነበርና።

ሰራተኞቹ በሙያ፤ በአካባቢና ብዝሃ ማንነት ያላቸው፤ ዳግማዊ ግድቡ ግን ያስተሳሰራቸው ዜጎች ናቸው። በፕሮጀክቱ እስከ 10 ሺህ የሚሆኑ ኢትዮጵያውያን፣ 500 ገደማ ከ40 ሀገሮች የተውጣጡ የውጭ ዜጎች ተሳትፈዋል።

በተለያዩ ሙያ ዘርፎች ልምድ እያካበቱ፣ አገርን ለብርሃን ጸጋ ያላበሱ ባለሙያዎች የ11ኛ ዓመት የስራ ጓደኝነት በዓላቸውን በኃይል ማመንጫው ዋዜማ ጉባ ላይ ተሰባስበው አክብረዋል። በ11 ዓመታት የሌት

ተቀን ስራቸው የሕይወት መስዋዕትነት የከፈሉ በርካታ ናቸው። ሰራተኞቹ የደስታ በዓላቸውን ሲያከብሩም የደስታ ቀናቸውን ሳያዩ በተለያዩ ምክንያቶች ሕይወታቸው ያለፉ ላብ አደሮችን በሕሊናቸው በማሰብ ነበር።

የዚህ ጽሁፍ አዘጋጅ በስፍራው ተገኝቶ ያነገጋገራቸው ሠራተኞች ከባድ የአየር ንብረትና መልከ ብዙ ውጣ ውረዶች ተሻግረው ዓባይን ወደ ብርሃን በመለወጣችን ከሌላው ሕዝብ በላይ ደስታቸው ወደር አልባ መሆኑን ገልጸውለታል። ከሙያተኞቹ መካከልም ግልገል ጊቤ እና ጣና በለስን ጨምሮ በተለያዩ የኃይል ማመንጫ ግድቦች ለአስርት ዓመታት ያገለገሉ ሠራተኞች የሕዳሴ ግድብ ቆይታቸውን ልዩ ትርጉም ይሰጡታል። ከግድቡ ጅማሮ እስከ አሁን ባሉት ዓመታት የድካማቸውን ፍሬ የቀመሱበት ወርሃ የካቲት ነውና “ከጨለማ ወደ ብርሃን የተሻገርንበት ወቅት” ይሉታል። በ11 ዓመታት የስራ ሕይወታቸው የካቲት 13ን ያህል የደስታ ምሽት የማጣጣም ጊዜም አልነበራቸውምና።

ከባሕር ጠለል በላይ ከ500 ሜትር ከፍታ ባለው የታላቁ ሕዳሴ ግድብ አካባቢ የበሽታዎች ወረርሽኝ ስርጭት ይበዛበታል። የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ቆይታቸው እናት አርግዛ እስክትወልድ እንዳለ የምጥ ስሜት በመሆኑ ‘ግድቡ ኃይል ሲያመነጭ በአካል መመልከቴ ደስታውም እጥፍ ድርብ ነው’ ይላሉ። የግድቡ ሠራተኞች ተጋድሎ ‘ኢትዮጵያዊያን ጨለማውን በብርሃን መግፈፍ ጀምረዋል፤ እኛም የአባይ ዘመን ልጆች የመባል ደማቅ ታሪክ ተጎናጽፈናል’ ይላል።

የታላቁ ህዳሴ ግድብ ፕሮጀክት ግንባታ “ሴቶች የነበራቸው ሁለንተናዊ ተሳትፎ ጉልህ ነበር” ይላሉ። ሌላው የግድቡ ግንባታ ትሩፋት የውጭ ዜጋን ጨምሮ የማይተዋወቁ ሠራተኞችን ማህበራዊ መስተጋብርን አጠናክሯል። ለሰራተኞቹ የእውቀትና የሙያ ልምድን ሽግግር ፈጥሮላቸዋል። የኢትዮጵያዊያንን አንጡራ ሀብት ባሰባሰበው በዚህ ግዙፍ ግድብ ሠራተኞች ከጋብቻ ጀምሮ ማህበራዊ ግንኙነትና የመቻቻል እሴትን ስለማጠናከራቸው ይናገራሉ።

በጥቅል ለሰራተኞቹ ታላቁ የሕዳሴ ግድብ ትንሿ የኢትዮጵያ ማለት ይቻላል። ግድቡ ከኢትዮጵያና ከአፍሪካ አልፎ በታዳሽ ኃይልነቱ ለዓለም የሚኖረውን አበርክቶት በቅጡ የተረዱት ሰራተኞቹ የእስከ አሁን ውጣ ውረዱ አልበገራቸውም። ይልቁኑም እስከ ፕሮጀክቱ ፍጻሜ በጽናትና እና በትጋት እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል።

ከሶስት ዓመታት ወዲህ በግድቡ ግንባታ በተወሰደው እርምጃ በግንባታው ቅልጥፍና ላይ ትልቅ ለውጥ እንዳመጣ ይናገራሉ። በግድቡ ላይ የታየው የ24 ሰዓታት ስራም ለሌሎች ፕሮጀክቶች ምሳሌ እንደሚሆን ያምናሉ። ለፕሮጀክቱ የእስካሁኑ ስኬት በርካታ ሠራተኞች በስራ ላይ የሕይወት መስዋዕትነት ከፍለዋል። በቀጣይም መንግሥት የሚያጋጥሙ ክፍተቶችን እንዲያሟላና በፕሮጀክት ግንባታ ሠራተኞች አንዳንድ ማበረታቻዎች እንዲሟሉ ያቀረቡት ጥያቄ ምላሽ እንዲሰጠው እግረ መንገዳቸውን ይጠይቃሉ።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ የኃይል ማመንጫውን በይፋ ሲያበስሩ ባደረጉት ንግግር ምስጋና ትልቅ ስፍራ ነበረው። ከዓጼ ኃይለስላሴ ጀምሮ በየዘመኑ በዓባይ ወንዝ ላይ ግድብ ለመገንባትና እየተገነባ ባለው ኃይል ማመንጫ ግድብ አስተዋጽኦ ላበረከቱ የአገር መሪዎች፣ የመንግሥት የስራ ኃላፊዎች፣ ምሁራን፣ ለግድቡ ስኬት ሁለንተናዊ የነቃ ተሳትፎ ያደረጉ በአገር ውስጥና በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን ምስጋና ቸረዋል። ከሁሉም በላይ ግን የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ግንባታ ሠራተኞች “በአገር ሕልውና ማስከበር ጦርነቱ መሳተፍ እንፈልጋለን፤ ግድቡ እንዲቆም ግን አንሻም ማለታቸውን አስታውሰው፤ ይህን ትውልድ ወክለው ላስቀመጡት አሻራ በእጅጉ አመስግነዋል።

መሰናበቻ…

አያቶቹ በክንዳቸው መከዳነት፣ በአጥንታቸው ምሰሶነትና በደማቸው ቡኬት በሕብረት አስከብረው ባቆዩዋት ኢትዮጵያ በአድዋ የአንድነት ታሪኩ ተምሮ በዳግማዊ አድዋው የሰንደቅ ዓላማ ፕሮጀክቱን በተባበረ ክንድ ገንብቶ መጨረስ፣ ተፈጥሮ የቸራቸውን ዓባይን መሰል ፀጋዎች አልምቶ መበልፀግ የዚህ ትውልድ ዕድል-ፈንታ ነው።



54

የአፍሪካ ጉዳይ

በግብርና ሚኒስቴር እና በኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ትብብር የተዘጋጀ

ግብርና - ኢኮኖሚውን ለመታደግ



55

በፍቅርተ ባልቻ

ግብርና - ኢኮኖሚውን ለመታደግ

ኢትዮጵያ በየዘመናቱ ብዙ ውጣ ውረዶችን አሳልፋለች። ከእክሎቹ መንስኤ ከፊሉ በአገር ውስጥ የሚከሰት የስልጣን ሽኩቻን ተከትሎ የሚደረጉ የእርስ በእርስ ግጭቶች ናቸው። ከዚህ በተቃራኒው ያላትን ጂኦግራፊያዊ አቀማመጥ እንዲሁም እምቅ አቅም እና የተፈጥሮ ኃብት ለመቀራመት ዓይናቸውን የጣሉ የውጪ ኃይሎች የቀጥታ አልያም የእጅ አዙር ትንኮሳ እና ደባ በዕድገቷ ብሎም

በሠላሟ ጥቁር ነጥብ አሳርፏል፣ እያሳረፈ ይገኛል።

አሁንም በአገር ውስጥ ያለውን ልዩነት በመጠቀም ረጃጅም እጃቸውን ዘርግተዋል። የታሪክ ምሁራን እንደሚገልጹት ኢትዮጵያ በዘመኗ አስተናግዳቸው የማታውቃቸው የጭካኔ ተግባራት ተፈጽመዋል።

አገሪቱ ግጭትና ድርቅ የሚፈራረቅባት ሆና በመቆየቷ ኢኮኖሚዋ ተጎድቷል። የምግብ ዋስትና ችግሩም ጎልቶ ይታያል። በተለይ በሰሜኑ የአገራችን ክፍል የተከሰተው ግጭት አርሶና አርብቶ አደሩን ከምርት ሂደት ያስተጓጎለ በመሆኑ ችግሩን አባብሶታል። በዚህም በቀጥታ ተጎጂ የሆነው (በተለይ በአማራ እና አፋር ክልሎች ያለው) አርሶ እና አርብቶ አደር ቁጥር ቀላል የሚባል አይደለም። ወረራው የሀገሪቱን ኢኮኖሚ የኋልዮሽ የሚጎትተው ነው። በተጨማሪም የማሕበራዊ ቀውሱ እና ስነልቦናዊ ጠባሳውም የከፋ ነው።

ስለሆነም ከወራሪ ነጻ በሆኑ በተለይ በአማራና በአፋር ክልሎች ያሉ አርብቶ እና አርሶ አደሮችን በማቋቋም በምርት ሂደት ውስጥ እንዲገቡ በማስቻል በግብርናው መስክ የሚያሳርፈውን ተጽዕኖ ለመግታት በተለየ ትኩረት መስራት ይጠይቃል።

በፍቅርተ ባልቻ



56

ነጋሪ በዚህ ዕትሟ በሀገራችን ያለውን ወቅታዊ ሁኔታ እና ያለውን ችግር በመቋቋም የግብርና ዘርፍ አጠቃላይ አፈጻጸም የተሻለ በማድረግ በምግብ እራስን ለመቻል እየተከናወኑ ያሉ ተግባራትን፣ ጉዳት የደረሰባቸውን አርሶ እና አርብቶ አደሮችን መልሶ ለመቋቋም የተቀመጡ የትኩረት አቅጣጫዎች ላይ የሚያጠነጥኑ ነጥቦችን በማንሳት ከግብርና ሚኒስትር ዲኤታ ዶ/ር መለስ መኮንን ጋር ቆይታ አድርጋ እንደሚከተለው አሰናድታዋለች። መልካም ንባብ!

....................................................

ነጋሪ፡- በቅድሚያ ለጊዜዎ ከልብ እናመሰግናለን! ዶ/ር መለስ መኮንን፡- መረጃ እንድሰጥ ስለጋበዛችሁኝ እኔም አመሰግናለሁ!

ነጋሪ፡- የመኸር ምርት በተለያዩ የሀገሪቷ አካባቢዎች እየተሰበሰበ ነው። አፈጻጸሙ ምን ይመስላል? በምርት ስብሰባ ወቅት ብክነትን ለመቀነስ ምን ዓይነት አሰራሮች ተከትላችኋል? ዶ/ር መለስ፡- ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ እንደ አገር የ2013/14 ምርት ዘመንን የመኸር የሰብል መርሃ ግብር ውጤታማ ለማድረግ ተንቀሳቅሷል። በዚህ የምርት ዘመን አንደኛ ለአገር ውስጥ ፍጆታ ማለትም ለምግብነት የምንጠቀማቸውን ሰብሎች ለይቶ ሁለተኛ ወደ ውጪ አገር ገበያ የሚላኩ የግብርና ምርቶችን በብዛትና በጥራት ለማምረት ታቅዶ የተቀናጀ ርብርብ ተደርጓል። ሦስተኛ ወደ አገር ውስጥ የሚገባውን የግብርና ውጤት ለመተካት (import substitution) እና ለኢንዱስትሪ ግብዓት ሊሆኑ የሚችሉ የግብርና ምርቶች በሚል ተለይተው እየተሰራባቸው ነው።

ከ13 ሚሊዮን ሔክታር ያላነሰ መሬት በማልማት በዋና ዋና ሰብሎች በመሸፈን ከ375 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ለማምረት ግብ ተጥሏል። በዚህም መሠረት በምርት ዘመኑ 12.7 ሚሊዮን ሔክታር (99 በመቶው) መሬት በሰብል መሸፈን ተችሏል።

ይህ የምርት ዘመን በወራሪው ኃይል ምክንያት በበርካታ አካባቢዎች የምርት ሂደቱ የተስተጓጎለበት ነው። በመሆኑም የደረሰውን ጉዳት ለማካካስ የምርት ብክነትን



57

በቀነሰ መልኩ ምርት መሰብሰብ አስፈላጊ ነው። ጥራቱን የጠበቀ ምርት ማምረትም ጠቀሜታው የጎላ ነው። ለዚህ አንዱ አማራጭ ዘመናዊ የሆኑ መሳሪያዎችን ተጠቅሞ ምርት መሰብሰብ ነው። ኮምባይነሮቹ በሁሉም አካባቢ ተዘዋውረው ምርት እንዲሰበስቡ ቅድመ ዝግጅት ተደርጓል። በዚህ ዓመት ከአንድ ሺህ ሁለት መቶ በላይ ኮምባይነሮች በእህል አሰባሰብ ተሰማርተው በተቀላጠፈና የምርት ብክነት በቀነሰ መልኩ አሰባሰቡን አግዘዋል። በዚህም መሰረት በሶማሌ፣ ደቡብ ክልሎች ቀድመው የደረሱትን ሰብሎች የተሰበሰበ ሲሆን በመቀጠልም ኮምባይነሮቹ በኦሮሚያና በአማራ ክልሎች እየተዘዋወሩ ምርት ሰብስበዋል።

እስከ የካቲት ሁለተኛ ሳምንት ድረስ ከዕቅዱ በ12.2 ሚሊዮን ሔክታር መሬት ላይ የለማ ሰብል ተሰብስቧል። ከዚህ ውስጥ በ651,058 ሔክታር ላይ የለማው የሰብል ምርት የተሰበሰበው በዘመናዊ ቴክኖሎጂ ታግዞ ነው። ኮምባይነር ለምርት አሰባሰብ መጠቀማችን እየሰፋ መምጣቱ ለምርት ብክነት ቅነሳ ያለው አስተዋጽኦ የላቀ ከመሆኑም በላይ የግብርና ትራንስፎርሜሽንን እያሳለጠ ነው።

ነጋሪ፡- በህወሓት ወረራ ምክንያት ጉዳት ከደረሰባቸው ዘርፎች ውስጥ በጉልህ የሚጠቀሰው ግብርና ነው። በወራሪው ኃይል ከወደሙት የግብርና ተቋማት ውስጥ ማሳያ የሚሆኑትን ቢገልጹልን? ዶ/ር መለስ፡- ወረራው በተካሄደባቸው አካባቢዎች የግብርና ተቋማት ከዞን ጀምሮ እስከ ቀበሌ ድረስ ተዘርፈዋል፣ ፈርሰዋል። ትልልቅ ተቋማቶችም ጉዳት ደርሶባቸዋል። ትልልቅ እርሻ ፕሮጀክቶችን ጨምሮ የምርምር ተቋማት ከጥቅም ውጪ ሆነዋል። ትልልቅ የፕሮጀክት እርሻዎችም በሙሉ የጠፉበት አካባቢዎችም አሉ።

የቆቦ ሲሪንቃ የእርሻ ምርምር አንዱ ሳይት ከጥቅም ውጪ ሆኗል። በአትክልት እና ፍራፍሬ ዘመናዊ የመስኖ ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም ትልቅ ስራ የሚሰራ የቆቦ ጊራና ሸለቆ ልማት ፕሮጀክት ሙሉ በሙሉ ወድሟል። በውስጡ የነበረ የአትክልት ልማት፣ የአትክልት እና ፍራፍሬ ችግኝ ጣቢያ፣ የመስኖ መሰረተ ልማት በሚያሳዝን ሁኔታ ወድሟል። የነበሩ የውሃ ፓምፖችን (ከሃይድሮ ኤሌክትሪክ ጋር ተገናኝቶ ከጉድጓድ ውሃ የሚያወጣ) እንዲሁም ጄኔሬተሮችን ጨምሮ የሚጭኑትን ጭነው ወስደዋል፣ የሚያፈርሱትን አፍርሰዋል።

የሲሪንቃ ግብርና ምርምርም በመንግሥትም፣ በባለሙያውም ለዓመታት የተደከመበት ተቋም ነው። እንደአብሸር፣ ጎብዬ፣ ሆርማት የመሳሰሉ በርካታ በጣም

የታወቁ አርሶ አደሩ የሚወዳቸው ምርታማ የሆኑ የማሽላ ዘሮች መነሻቸው እዚያ ነው። ይህ የበርካታ ዓመታት ድካም፣ ልፋት፣ ምርምር እና ውስብስብ ስራ ውጤት ነበር። ለዘመናት የተለፋባቸውን እነዚህን ዝርያዎች ተመራማሪዎቹ ከሚገለገሉባቸው ግብዓቶች ጋር በአንድ ላይ ነው ያወደሙት።

ሌላው የሰቆጣ የግብርና ምርምር ማዕከል ነው። ይህንን ማዕከል ማረፊያቸው (ካምፕ) አድርገውት ነበር። ከአካባቢው የአየር ንብረት ተስማሚነት አንጻር ምን ቢሰራ ውጤታማ መሆን እንደሚቻል ምርምር ይካሄል። ከተቋቋመበት ጊዜ አንስቶ ከአስር እና አስራ አንድ ዓመታት በላይ በተደረገው ምርምር የአበርገሌን ፍየል ማሻሻል ተችሏል። እነዚህን ልክ ተራ ገበያ ላይ እንደሚያገኙት ፍየል ነው ያወደሟቸው። ቴክኖሎጂ እንጂ ፍየል ወደመ አልለውም። በስንት ማሻሻል እና ድካም የተገኙ ዝርያዎች ነበሩ። እነዚህን እና ሌሎች ትልልቅ ቤተሙከራዎችን (ላቦራቶሪዎችን) ጭምር ነው ያጠፉት።

ጨፋ እርሻ ልማት ላይ በጣም ትልቅ እና ዘመናዊ የሆነ የዶሮ ጫጩት ማስፈልፈያ በባለኃብቶች ተገንብቶ ያለቀ ነበር። ይህን ወደ ስራ ይገባል ብለን በምንጠብቅበት ወቅት ነው ገብተው ያወደሙት። ከግብርና ጋር ተያያዥ የሆኑትን ለማንሳት ነው እንጂ ሌሎች በርካታ ጉዳቶችም በወረራ ተይዘው በነበሩ አካባቢዎች ጉዳት ደርሶባቸዋል።

ነጋሪ፡- በርካታ ወገኖቻችን በሰሜኑ የሀገራችን ክፍል በተፈጸመው ወረራ ምክንያት ከቀያቸው ለመፈናቀል ተገደዋል። በጦርነቱ ጉዳት የደረሰባቸውን አርሶ እና አርብቶ አደሮችን በማቋቋም ወደ መደበኛ ሕይወታቸው እንዲመለሱ ለማስቻል የተቀመጡት አቅጣጫዎች ምን ምን ናቸው?

ዶ/ር መለስ፡- የመኸር እርሻ እንቅስቃሴ በተጀመረበት ወቅት ወራሪው የህወሓት ኃይል በተለይ በትግራይ አጎራባች የሆኑ የአማራ እና አፋር አካባቢዎች ላይ የእርሻ ስራ እንዲስተጓጎል አድርጓል። እየቆየም ቡቃያው እንክብካቤ እንዳያገኝ ሆኗል። አርሶ አደሩ የዘራውን እንዳይንከባከብ እና የደረሱትን ሰብሎች እንዳይሰበስብ ተገዷል።

ይባስ ብሎም በማሳዎቹ ላይ ታንክ ነድቶባቸዋል፣ ለምሽግነትም አውሏል። ቡድኑ የተከበረውን የሰው ልጅ አስክሬን እርሻ መሀል እስከመቅበር የደረሰ አጸያፊ ተግባርም ፈጽሟል። በማሳዎቹ ላይ የጅምላ መቃብሮችም ተገኝተዋል። በዚህም ሳቢያ በአፋር እና በአማራ ክልሎች ከአንድ ነጥብ አምስት ሚሊዮን ሔክታር ያላነሰ መሬት ከጥቅም ውጪ ሆኗል። ከማሕበረሰቡ ስነልቦና ጋር አብሮ የማይሄድ ድርጊት ተፈጽሟል። ስለሆነም ለመዝራትም ሆነ የተዘራውን ለመንከባከብ ብሎም ለመሰብሰብ አስቸጋሪ ሁኔታን ፈጥሮ ሰንብቷል።

በአርሶ እና አርብቶ አደሩ ሕልውና ላይ አደጋ በተጋረጠበት ወቅት ከአሁን ጀምሮ የሚደርሰውን ጉዳት ለመቋቋም ምን መስራት እንዳለብን በሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ እና በአገር

አቀፍ ደረጃ ከተወያየን በኋላ ዕቅድ ተዘጋጅቷል። በዕቅዱ ከተያዙ የትኩረት አቅጣጫዎች ውስጥ አንዱ የመኸር እርሻ እንቅስቃሴ የተመለከተ ነው።

ባልተወረሩና ነጻ በሆኑ አካባቢዎች የተሻለ አፈጻጸም ለማግኘት በቁጭት መስራት እንደሚጠይቅ ታሳቢ ተደርጓል። ይህም በተወረሩት አካባቢዎች የጠፋውን ጥፋት ባይመልስ እንኳን የራሱን አስተዋጽኦ እንዲያደርግ የሚያስችል ነው። የመኸር ስራውን በተገቢው በማከናወን ውጤታማ ለማድረግ ሁለገብ ጥረት ተደርጓል። እንቅስቃሴውም ሰብል መሰብሰብን ጨምሮ ሌሎች የመኸር ወቅት ስራዎችንም አካቷል።

ወራሪውን ለመመከት በርካታ አርሶ አደሮቻችን ወደ ግንባር ዘምተዋል። የተቀሩትም ቢሆን ተያያዥ በሆኑ ስራዎች ጊዜያቸውን ያሳልፉ ነበር። ስለሆነም የዘማች ቤተሰቦችን እርሻ የማረስ፣ ዘር የመዝራት፣ የመንከባከብና ሲደርስም የመሰብሰብ ተግባር በፌዴራልም በክልሎችም ትኩረት አግኝቶ እንዲከናወን የሚደረገው ድጋፍ እና ክትትልም እንደቀጠለ ነው።

ሁለተኛ ትኩረት የሰጠነው ከወረራ ነጻ የወጡ አካባቢዎች እንደተለቀቁ ፈጥነው ወደ ወቅታዊ እርሻ ስራ እንዲገቡ ማድረግ ነው። ለዚህ የሚያስፈልጉ ግብዓቶችን እንደዘርና ማዳበሪያ ያሉትን በመለየት በዕቅዱ እንዲያዙ ተደርጓል። ሽምብራ፣ ምስር፣ ጓያ፣ የመሳሰሉትን በቅብብሎሽ ማምረት ይቻላል። በተለቀቁትም ሆነ ባልተወረሩት አካባቢዎች የመኸር ሰብል እየተነሳ መሬቱ እርጥበቱን ሳያጣ ሁለተኛ ሰብል እንዲያመርቱ ለማስቻል በሁሉም ክልሎች እየተሰራ ነው ያለው።

የበልግ አብቃይ የሆኑ አካባቢዎች ወረራ ተፈጽሞባቸው ነበር። በዚህም ሳቢያ የምናጣውን ምርት ለመተካት የምንከውነው ሌላው ተግባር የበልግን ወቅት በተገቢው መጠቀም ነው። ስለሆነም እነዚህ አካባቢዎች ላይ እንቅስቃሴ ተጀምሯል። ባለሙያውን፣ አርሶ እና አርብቶ አደሩን በማወያየት ወደ ስራ እንዲገቡ እየተደረገ ነው። ይህንን እንቅስቃሴም የበለጠ አጠናክረን የምንቀጥል ይሆናል። ባልተወረሩትም የበልግ አብቃይ አካባቢዎች ጥሩ ወቅት እንደሚሆን እንጠብቃለን። ከቅድመ ዝግጅት ጀምሮ ግብዓት በማቅረብ እንክብካቤውን ከእስከዛሬው በተሻለ ቁጭት በመስራት በበልግ የምናገኘውን ምርት ከፍ እናደርጋለን ብለን ቅድመ ዝግጅት እየሰራን ነው ያለነው።

የደረሰብን ጥፋት በአንድ መኸር፣ በአንድ መስኖ፣ በአንድ በልግ ወቅት በሚገኝ ማካካሻ የሚመለስ አይደለም። ጥፋቱ ከፍተኛ ስለሆነ የቀጣይ መኸር ወቅትም የዕቅዱ አካል ሆኗል። ለዚህም የምንዘጋጀው ከአሁን ጀምረን ነው። በስንዴም ሆነ በሌሎች ሰብሎች ምርትን መጨመር ይጠበቅብናል፤ የጠፋውንም ማካካስ አለብን። እንደ አገርም ምርትና ምርታማነትን መጨመር እንዳለብን በማመን በትኩረት እየሰራን ነው ያለነው።

የማሳ ኩታ ገጠም ልማታችንን ማስፋፋት፣ የፓኬጅ



58

በደቡብ፣ በአፋርና በሲዳማ ክልሎች በስፋት በመከናወን ላይ ነው። እስከ ጥር ወር ሁለተኛ ሳምንት ድረስ 424,099 ሔክታር መሬት ታርሶ የተዘጋጀ ሲሆን ከዚህ ውስጥ 404,900 ሔክታር መሬት በመስኖ ስንዴ ዘር በመሸፈን ዕቅዱን ማሳካት የተቻለ ሲሆን የላቀ ምርት እንዲሰጥ የሰብል እንክብካቤ እየተደረገ ነው። የሚጠበቀው ምርት በተመለከተ እንደየአካባቢውና እንክብካቤ ሁኔታ የሚለያይ ቢሆንም በአማካኝ ከ18 እስከ 20 ሚሊዮን ኩንታል ስንዴ በመስኖ ብቻ ማምረት እንችላለን።

በመስኖ ስንዴን በማልማት ብቻ ከውጪ የምናስገባውን አልያም በተፈጸመው ወረራ ሳቢያ ያጣነውን ምርት እንተካለን የሚል እሳቤ የለንም። የበለጠ ምርታማ ለመሆን ሦስቱን ወቅቶች በአግባቡ መጠቀም አለብን። እንደየወቅቱ ከሰብል ፈረቃ ጋር ተያይዞ የሚጨምርበትና የሚቀንስበት ሁኔታ ቢኖርም በአማካኝ ከሦስት ሚሊዮን ያላነሰ ሔክታር መሬት በመኸር ወቅት በስንዴ ይሸፈናል። ምርጥ ዘር እና ማዳበሪያ በመጠቀም፤ አረምን፣ በሽታን፣ ተባይን የመከላከል ተግባራትን በማከናወን እንዲሁም ምርቱን ከብክነት በመከላከል እና በተገቢው ቴክኖሎጂ ታግዞ በመሰብሰብ ምርት እና ምርታማነት መጨመር እንችላለን።

ክትትል እያደረግን አሰራሮቻችንን ካዘመንን፣ ለመስኖ የምንጠቀመውን መሬት መጠን ካሳደግን፣ የመስኖ አውታሮች ከተገነቡ ስንዴን ከአገር ውስጥ ፍጆታ አልፎ ወደ ውጪ መላክ የሚያስችል አቅም በሀገራችን መኖሩን በእርግጠኝነት መግለጽ ይቻላል። ለዚህም ነው የግብርና ሚኒስቴርም የአስር ዓመት ዕቅዱ ላይ ስንዴ አመራረት ማዘመን አንዱ የትኩረት አቅጣጫ ያደረገው፤ በተለይ ደግሞ የመስኖ ስንዴ ልማት።

ስንዴን በአገር ውስጥ በማምረት ከውጭ የሚገባውን በማስቀረት የውጪ ምንዛሬን ማዳን ይቻላል፣ በምግብም ራሳችንን ለመቻል ትልቅ አስተዋጽኦ ይኖረዋል። የግብርና ሚኒስቴርም ለዚህ ስራ የተለየ ትኩረት ሰጥቶ ክልሎችንም በማስተባበር እስከታች ያለውን አቅም አሟጦ በመጠቀም ለመስራት ጥረት እያደረገ ነው።

ሰርቶ ደክሞ ሰለቸኝ የማይል ታታሪ የሆነ አርሶ አደር እና የግብርና ባለሙያ፣ ለዚህ ስራ የሚውል በቂ እና ሰፊ መሬት እንዲሁም የውሃ ኃብት አለን። እነዚህን ኃብቶች አቀናጅተን በተነሳሽነት ከሰራን ውጤታማ ከመሆን የሚገታን ነገር አይኖርም።

ነጋሪ፡- አሲዳማ አፈርን በማከም ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ የተያዘው ውጥን እና አፈጻጸሙ ምን ይመስላል?

ዶ/ር መለስ፡- ለዘመናት ተደጋግሞ የታረሰ እና እንክብካቤ ያልተደረገለት አፈር ለምነቱ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየቀነሰ ይሄዳል። በዚህም ምክንያት በአብዛኛው

ሁለተኛው የመደበኛ መስኖ ልማት ነው። በመደበኛ መስኖ ልማታችን የተለያዩ የሆርቲካልቸር፣ ፍራፍሬ እና ስራስር የመሳሰሉትን የምናመርትበትና የተወሰኑ አዝዕርትም ልማት የተካተተበት ነው። እንደበቆሎ ያሉትን በመስኖ ለማልማት እንደ አንድ መርሃግብር ይዘን እየሰራን ነው። አትክልት እና ፍራፍሬ ላይም እናተኩራለን። ስለሆነም አንደኛ እና ሁለተኛ ዙር የመስኖ ስራ ይኖረናል ማለት ነው።

የዓመቱ የመደበኛ መስኖ ልማት ዕቅዳችን 991,863 ሔክታር መሬት የሆርቲካልቸር ሰብሎች ምርት ለማምረት ነው። እስከጥር ወር ሁለተኛ ሳምንት ድረስ ያለን አፈጻጸም የሚያሳየው በአንደኛ ዙር መስኖ ብቻ 987,870 ሔክታር መሬት ላይ የተለያዩ የሆርቲካልቸር ሰብሎች በመስኖ ማልማት መቻሉን ነው።

ከውጪ ወደ አገር ውስጥ የሚገባውን ስንዴ ለማስቀረት የመስኖ ስንዴ ልማቱ በተለየ ትኩረት እየተሰራ ነው። የመስኖ ስንዴ ልማት ስራው ከሦስት ዓመት በፊት በሦስት ሺህ ሔክታር መሬት ላይ ነበር የተጀመረው። ይህ እያደገ መጥቶ በዚህ ዓመት 400 ሺህ ሔክታር መሬት በመስኖ ስንዴ ለመሸፈን አቅደን እየተንቀሳቀስን ነው። ለውጤታማነቱ የባለድርሻ አካላትን ተሳትፎ ለማሳደግ ርብርብ እየተደረገ ነው።

የውሃ አካላት ልየታ፣ በውሃው ሊለማ የሚችል መሬት ልየታ፣ የዘር አቅርቦት ሌሎች ማዳበሪያ የመሳሰሉ ግብዓቶች ቅድመ ዝግጅት ተከናውኗል። ለአርሶ አደሩ እና ለባለሙያው ስልጠና ከተሰጠ በኋላ በሁሉም አካባቢዎች ወደ ስራ ተገብቷል።

የመስኖ አውታር ባልተዘረጋባቸው አካባቢዎች ቀደም ብለው የነበሩት የውሃ መሳቢያ ቴክኖሎጂዎች ጥገና ተከናውኗል። ሌሎች አስፈላጊ የሆኑ ግብዓቶችም ተሟልተዋል። ከፌዴራል ጀምሮ የግብርና ሚኒስቴር፣ የኢትዮጵያ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት፣ የኢትዮጵያ ግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት እና ሌሎች ተቋማትን በማቀናጀት ነው ቅድመ ዝግጅቱን ከዕቅድ ጀምሮ ስናከናውን የቆየነው።

ክልል ላይ ዩኒቨርሲቲዎች እና ሌሎች ለስራው የሚጠቅሙ ተቋማትን ሁሉ በማቀናጀት የዘንድሮው የመስኖ ስንዴ በተሻለ ለማከናወን ጥረት ተደርጓል። ምክንያቱ ደግሞ ቀደም ሲል የነበረው ከውጪ የምናስገባውን ስንዴ በአገር ውስጥ የመተካት ዕቅድ ማሳካት ስለሚገባን ነው።

አሁን ግን በተጨማሪ በወራሪው ምክንያት ያጣነውን ምርት ማካካስም ጭምር የሚጠይቅበት ወቅት ላይ የምንገኝ በመሆኑ በተለየ ትኩረት መንቀሳቀስ ያስፈልጋል። ጎን ለጎን የምርምር ማዕከላትንና ሌሎች ከዚህ ስራ ጋር ተያያዥነት ያላቸውን ተቋማትን በመጠቀም የስንዴ ምርጥ ዘር ለማባዛት እየተሞከረ ነው።

ለዚያም ነው 400 ሺህ ሔክታር መሬት በማልማት ውጥኑን ለማሳካት እየሰራን ያለነው። ይህም በመሆኑ የመስኖ ስንዴ ልማት ስራው በኦሮሚያ፣ በአማራ፣

አጠቃቀማችንን በማሻሻል ሙሉ ፓኬጅ በመጠቀም የቀጣይ መኸርንም በዕቅድ ውስጥ አካቶ መስራት ይጠይቃል። በምርት መርሃ ግብሮቻችን በመስኖ፣ በበልግና በመኸር ያለውን የምርት ክፍተት ለመሙላት ከወትሮ በተለየ ሁኔታ ትኩረት ሰጥተን እየሰራን ነው።

አርሶ እና አርብቶ አደሩ ከዶሮ ጀምሮ እስከ በሬ ድረስ እንስሳቱን አጥቷል። ይህም ሌላው መፍትሔ የሚያሻው ጉዳይ ነው። ዘር፣ የእርሻ በሬዎቹን፣ ላሞቹን፣ ፍየሎቹን ሁሉም ታርደውበታል፣ የተወሰዱትም ተወስደዋል። መጠቀም እና መውሰድ ያልቻሉትን ገድለዋቸዋል። ችግሩ በዚህ ብቻ አያበቃም። ከዕለት ቀለብ፣ ለዘር ብሎ እስከሚያስቀምጠው ድረስ ተወስዶበታል። ስለሆነም ዘንድሮውን አለማምረት ብቻ ሳይሆን ለቀጣይ የምርት መርሃ ግብር የሚውል ዘር አይኖረውም።

በዚህ ሂደት በአብዛኛው የሚጎዳውና ምርቱን የሚያጣው፣ የሚጎሳቆለውም አርሶ አደሩ ነው። ለተጎዳው አካል የአደጋ ጊዜ ምላሽ (emergency response) መስጠት ያስፈልጋል። ባልተወረሩ አካባቢዎች ያለውን አርሶ አደር፣ የመንግሥት ተቋማትን፣ ረጂ ድርጅቶችን፣ የግል ባለኃብቶችን፣ ዳያስፖራውንም ጭምር በማስተባበር በዓይነትም፣ በገንዘብም እገዛ ሊደረግ የሚችልበትና መልሰን ልናቋቁም የምንችልበት ዝርዝር ዕቅድ ተዘጋጅቷል። አሁንም የተጀመሩ ስራዎች አሉ።

በጋራ በመሆን እንስሳትን ለአርሶ እና አርብቶ አደሩ ገዝቶ መስጠት፣ ካልሆነም ለእርሻ ስራ የሚሆን የበሬ ኪራይ መደገፍ ይቻላል። ለዘር የሚሆን እህል ድጋፍ ማድረግም አስፈላጊ ነው። ትራክተርን በኪራይ ማቅረብ እንደ አማራጭ ተቀምጧል። ሁሉንም አማራጮች ለሕዝቡ፣ ለክልል መንግሥታት፣ ለባለሀብቶች እንዲሁም ለረጂ ድርጅቶች በማስረዳት በሚችሉት እና በሚያመቻቸው መንገድ ድጋፋቸውን እንዲሰጡ ነው እየተደረገ ያለው።

በሰሜን ሸዋ እንዲሁም ደቡብ ወሎ አካባቢዎች ፈጥነው ወደ ልማት ስለገቡ የመስኖ ስንዴ ዘር እንዲደርሳቸው እየተሰራ ነው። ሌሎችም ድጋፎች እንዲሁ እየተላኩ ነው። በአፋርም በሌሎችም አካባቢዎች ላይ እንደዚሁ እያገዝን አርሶ አደራችን ወደ ስራው እንዲመለስ በማስቻል ካለበት መከፋት፣ መተከዝ እና ማሰላሰል እንዲወጣ ለማድረግ እየተሰራ ነው።

ነጋሪ፡- የመስኖ ልማት ስራው የሚገኝበት ደረጃ ምን ይመስላል? አፈጻጸሙስ እንዴት ይገለጻል? ስራው ስኬታማ እንዲሆን የሚደረገው ክትትልና ድጋፍ ምንድን ነው? ዶ/ር መለስ፡- የመስኖ ልማታችንን በሁለት መልኩ አቅደን እየሰራን ነው። አንዱ የመስኖ ስንዴ ማምረት ሲሆን



59

የእርሻ እንቅስቃሴ በሚዘወተርባቸው ደጋማና ወይና ደጋማ አካባቢዎች የአፈር አሲዳማነት (Soil Acidity) እየጨመረ ከመሄዱ ጋር ተያይዞ የመሬት ምርታማነት ከመቀነሱም በላይ ከምርት ውጭ እንዲሆን ያደርገዋል። የአፈር አሲዳማነት የመሬቱ ምርታማነት ከ50 እስከ 100 በመቶ እንዲቀንስ እያደረገ ነው። በመሆኑም የአፈር ደህንነትና ጤንነት በመጠበቅ ለምነቱን ማሻሻል ምርትና ምርታማነት ለማሳደግ የሚሰራ ስራ ሌላው የትኩረት ጉዳይ ነው።

መሬቱን በማከም የአፈር ለምነት በማሻሻል ምርት መጨመር የሚቻልበት አሰራር አለ። አሲዳማ አፈር ሆኖ መቶ በመቶ ከምርት ውጪ የነበሩትን በኖራ በማከም መቶ በመቶ ምርታቸውን መጨመር ተችሏል። በአማራ፣ ኦሮሚያ፣ ደቡብ፣ ቤኒሻንጉል እና ሌሎችም ክልሎች አሲዳማ አፈር በብዛት አለ። ሁሉንም በአንድ ጊዜ ማከሙ አስቸጋሪ ነው። ሆኖም በጊዜ ሂደት ከስር ከስር እያከምን አሰራራችንን እያሻሻልን ከሄድን መሬቱን በአግባቡ መጠቀም ስለሚያስችለን ምርታማነታችንን ማሳደግ ይቻላል። በአሲዳማነት የተጠቁ መሬቶችን በኖራ እያከሙ ወደ ምርትና ምርታማነት ሂደት ውስጥ በማስገባት በእነዚህ መሬቶች ስንዴን በማምረት አገራዊ የስንዴ ምርት ፍላጎት ለማሟላት መስራት ሌላኛው ትኩረት ሰጥተን እየሰራንበት ያለ የአሰራር ዘዴ ነው።

ነጋሪ፡- ዳያስፖራው ወደ አገር ቤት እየመጣ ነው። የመጡትን ዳያስፖራዎች በግብርና መስክ ኢንቨስት እንዲያደርጉ ለማነሳሳት ምን የታሰበ ውጥን አለ? ዶ/ር መለስ፡- ዳያስፖራ ወገኖቻችን ወደ አገር ቤት እንዲመጡ ጥሪ ሲደረግ አንድም የደረሰውን ጉዳት በመመልከት እውነታውን እንዲረዱ ነው። ከሚመጡት መካከል አገር ጎብኝተው፣ ዘመድ አዝማድ ጠይቀው የሚመለሱ አሉ። የተወሰኑትም ‘በሀገራችን ላይ ለመስራት ምን አማራጭ አለ? ምን ላይ ኢንቨስት ብናደርግ ራሳችንና ሀገራችንን እንጠቅማለን?’ በሚል ሁኔታውን ለማጤን የሚመጡም ናቸው።

ስለዚህ በሁሉም ክልሎች ያሉትን የኢንቨስትመንት አማራጮች ተጠንተው ምን ላይ ቢሰማሩ ውጤታማ እንደሚሆኑ፣ በግብርናው እና በሌሎችም መስኮች ያሉትን እምቅ አቅሞች ለማሳየት እየተሞከረ ነው።

በዚህም መሰረት ግብርና አንዱ የትኩረት መስክ ነው። ያሉትን ምቹ ሁኔታዎች ለማሳየት የኢንዱስትሪ ሚኒስቴር፣ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን እና ጉዳዩ የሚመለከታቸው አካላት ሁሉ በቅንጅት እየሰሩ ነው። ስለሆነም የመጡትን ዳያስፖራዎች ለኢንቨስትመንት እንዲነሳሱ ጥረት ይደረጋል።

ሲጠቃለል አሁን በአገራችን እንደተከሰተው ዓይነት

ችግሮች ሲያጋጥሙ ተጎጂ የሚሆነው ማሕበረሰቡ ነው። ከማሕበረሰብ ሰፊው ቁጥር የሚይዘው አርሶ አደሩ የበለጠ የችግሩ ሰለባ ነው። ነገር ግን የተለያዩ ተፈጥሯዊ እና ሰው ሰራሽ አደጋዎች ሲከሰቱ ለአርሶ እና አርብቶ አደሩ የሚሰጠው ትኩረት እዚህ ግባ የሚባል አይደለም።

ይልቁንም ትኩረት የምንሰጠው በከተሞች አልያም ተቋማት ላይ ለደረሱት ጥፋቶች ነው። አርሶ እና አርብቶ አደሩ እንደከተማው ሰው ያመዋል ብሎ ካለማሰብ ይሁን በሌላ ምክንያት ድጋፉ ብዙ ጊዜ ያን ያህል አይደለም። በጠፋበት ንብረትም፣ እንስሳትም፣ በዘርም፣ በሌላም ቢሆን እራሱን አጎሳቁሎ ለአገር ደፋ ቀና የሚል እስከ ሆነ ድረስ የሚደረጉ ድጋፎች አርሶ አደሩን የዘነጉ መሆን የለባቸውም። ስለሆነም ድጋፎቹ አርሶ እና አርብቶ አደሩን ያማከሉ እንዲሆኑ መስራት ይጠይቀናል።

አርሶ እና አርብቶ አደሩን፣ የግል ባለሀብቱ፣ የውጪ ድርጅቶች እና ዳያስፖራውን ማኅበረሰብ በሙሉ ይዘን የግብርናውን ዘርፍ ስኬታማ ለማድረግ ወደ ተግባራዊ እንቅስቃሴ ገብተናል። ኢትዮጵያዊያን ሁላችን የዚህ እንቅስቃሴ አካል በመሆን ለውጤታማነቱ በጋራ መስራት ይጠይቀናል።

ነጋሪ፡- ስለነበረን ቆይታ እናመሰግናለን! ዶ/ር መለስ፡- እኔም አመሰግናለሁ።

ግብርና ሚኒስትር ዲኤታ ዶ/ር መለስ መኮንን

ሰርቶ ደክሞ ሰለቸኝ የማይል

ታታሪ የሆነ አርሶ አደር እና

የግብርና ባለሙያ፣ ለዚህ ስራ

የሚውል በቂ እና ሰፊ መሬት

እንዲሁም የውሃ ኃብት አለን።

እነዚህን ኃብቶች አቀናጅተን

በተነሳሽነት ከሰራን ውጤታማ

ከመሆን የሚገታን ነገር

አይኖርም።



60

በቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል ሚሊኒየም የሕክምና ኮሌጅ እና በኢዜአ ትብብር የተዘጋጀ

የእውቀት ማዕድ

ኢኮኖሚ



61

የእውቀት ማዕድ በፍቅርተ ባልቻ

በሰው ልጅ አጠቃላይ ስብዕና ላይ ግዙፍ ተጽዕኖ የሚያሳርፉትን መጽሐፍትን የምናገኝበት፣ አግኝተንም ከመጽሐፍቱ ጋር ጓደኝነት መስርተን ከምንጨዋወትባቸው ቦታዎች አንዱ ቤተ- መጽሐፍ ነው። መጽሐፍቱን በዓይነታቸው፣ በይዘታቸው በወጉ ተሰድረው እናገኛቸዋለን - በቤተ መጽሐፍቱ። ቤተ- መጽሐፍት ከፍተኛ የሆነ ታሪካዊ፣ ባሕላዊ፣ ማኅበረሰባዊና ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ ያላቸውን የመረጃ

ኃብቶች ጠብቀው ለትውልድ በማስተላለፍ እንደ ባሕል ማዕከል ያገለግላሉ።

ቤተ-መጽሐፍቱ መጽሐፍትን፣ ጥናታዊ ጽሑፎችን፣ መጽሔቶችን፣ ጋዜጦችን፣ ጆርናሎችን፣ ቀረጸ ድምፅና ምስሎችን፣ ካርታዎችን፣ የማጣቀሻ መጽሐፍትን ወዘተ.. .እንደየተጠቃሚዎቻቸው ፍላጎት መረጃዎችን በማሰባሰብ እና በማደራጀት ለአንባቢያን እነሆ ይላሉ። የተጠቃሚዎቻቸውን ፍላጎት መሰረት አድርገው መረጃን ከመረጃ ፈላጊዎች ጋር ማገናኘት የቤተ-መጽሐፍቱ የዕለት ተዕለት ተግባር ነው።

“ተማሪ እንደመሆኔ በብዛት የማነበው ለትምህርቴ አጋዥ የሆኑትን መጽሐፎች ነው። በቤተ-መጽሐፍት ውስጥ ሀሳብን ሙሉ በመሉ በማሰባሰብ ማንበብ ይቻላል። ለዛም ነው ቤተ-መጽሐፍትን በብዛት የምጠቀመው።” ስትል ተማሪ የአብስራ ሰውመሆን ስለቤተ-መጽሐፍት ጠቀሜታ ከተመክሮ በመነሳት ታስረዳለች።



62

በልጅነቷ በአቅራቢያዋ ቤተመጽሐፍ በመኖሩ እየሄደች ታነብ እንደነበር ታስታውሳለች። ይህም አልባሌ ቦታ ከመዋል እንድትቆጠብ እንደረዳት፤ ቤተሰብም እንድታነብ ያበረታቷት እንደነበር፣ አሁን ለደረሰችበት ደረጃ ቤተመጽሐፍት ስትጠቀም ማደጓ ትልቅ አስተዋጽኦ እንዳለው በመግለጽ የራሷን የሕይወት ተመክሮ እንደማሳያ አቅርባለች።

የሕክምና ቤተ-መጽሐፍትን ማቋቋም በርካታ ጠቀሜታ እንዳለው ይነገራል። በተያያዘም ቤተ-መጽሐፍቱ የመማር ማስተማር ሂደቱን ቀና እንዲሆን ከማገዛቸውም ባሻገር በርካታ ጥናት እና ምርምሮች እንዲሰሩ እንደሚያነሳሱ መረጃዎች ያመለክታሉ።

የሕክምና ቤተ-መጽሐፍት ጥናት እና ምርምሮችን በብዛት እንዲሰሩ ብሎም ጥራታቸውን የጠበቁ እንዲሆኑ ለማስቻል ትልቅ ሚና እንዳላቸው Tehran University of Medical Sciences Research Gate በተሰኘው ድረ ገጽ በ2018 ያሳተመው እና new roles of medical li- brarians in medical research በሚል ርዕስ የቀረበው ጥናት ያሳያል።

ከየት - ወዴት? በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ስር ሆኖ ለ75 ዓመታት አገልግሎት ሲሰጥ የቆየ አንጋፋ ተቋም ነው። ከ2000 ዓ.ም ጀምሮ የተዋሐደ የሕክምና ስርዓተ ትምህርት (Integrated curriculum) በመቅረጽ ሆስፒታል እና የሕክምና ኮሌጅ በመሆን እየሰራ ነው - የቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል ሚሊኒየም የሕክምና ኮሌጅ። ስያሜው

እንደሚያመላክተው ለኮሌጁ ትኩረት ተሰጥቶት መስራት የተጀመረው የሚሊኒየም በዓል ከተከበረበት ወቅት አንስቶ ነው። ተቋሙ የጤና ችግርና የባለሙያ ፍላጎት ግምት ውስጥ በማስገባት ዕቅድ ነድፎ ዘርፈ ብዙ ተግባራትን በማከናወን ላይ ነው። በሕክምና ኮሌጁ በትምህርት እና ምርምር ዘርፍ ስር ከተደራጁት የስራ ክፍሎች አንዱ የቤተ-መጽሐፍትና ዶክመንቴሽን አገልግሎት ዳይሬክቶሬት ነው።

የቅዱስ ጳውሎስ ሚሊኒየም ሕክምና ኮሌጅ ቤተ-መጽሐፍ አሁን ባለው መልኩ ከመደራጀቱ አስቀድሞ በተለያዩ (ሦስት) ቦታዎች አገልግሎት ይሰጥ ነበር። በሦስት ቦታዎች ይሰጥ የነበረውን አገልግሎት ወደ አንድ በማምጣት ለትምህርት ፕሮግራም ማስፋፊያነት በተገነባው ሕንጻ በ2006 ዓ.ም ተዘዋውሯል።

“አገልግሎት ይሰጥ የነበረው በጥቂት ባለሙያዎች አማካኝነት ነበር። የስራ ክፍሎቹ እና አገልግሎቱም እንደ ሌሎች ቤተ-መጽሐፍት መዋቅር የተደራጀ አልነበረም። የመጽሐፎችም ቁጥር በቂ አልነበረም። የኢንተርኔት ኮኔክሽን ሆነ ቤተ-መጽሐፉ አገልግሎት በዘመናዊ ቴክኖሎጂ የታገዘ አልነበረም።” በማለት ቤተ-መጽሐፉ የነበረበትን ሁኔታ የሚያስታውሱት በዚሁ ቤተ-መጽሐፍ ከ2007 ዓ.ም ጀምሮ እየሰሩ ያሉት ወ/ሪት ሕይወት አበበ ናቸው።

ቤተ-መጽሐፉን በግብዓት፣ በአደረጃጀት፣ በአሰራር እንዲሁም በሰው ኃይል የተሻለ ለማድረግ ብዙ በመሰራቱ በአጭር ጊዜ ውስጥ ለውጥ ማምጣት ተችሏል። እ.ኤ.አ 2018 ወርሃ የካቲት ጀምሮ የቤተ-መጽሐፉ የአሰራር

መመሪያ (Library & Documentation Services Poli- cy Manual) ተዘጋጅቶ ስራ ላይ ውሏል።

ክምችቱን ለማሳደግም በ2007 ዓ.ም በዓይነት 578፣ በብዛት ከ14 ሺ ቅጂ በላይ መጽሐፍት ግዥ ተካሂዷል። በአስራ አራት ዓመታት ቆይታው ከሌሎች አንጋፋ ቤተ- መጽሐፎች ከሚገኙበት ደረጃ ጋር የተስተካከለ እንዲሆን ለማስቻል ብዙ ጥረቶች ተደርገዋል።

የንባብ አገልግሎት የሚሰጥበት ስፍራ በዲዛይነሮች አማካኝነት ምቹ እና ተስማሚ እንዲሆን ተሰርቷል። ይህን ተከትሎም የኔትዎርክ መስመር ተዘርግቷል። ቤተ- መጽሐፉን በመጽሐፍት ከማሟላት ባሻገር የሶፍት ኮፒ መረጃዎችንም ለተጠቃሚዎች ለማቅረብ መሰራቱን ነው ወ/ሪት ሕይወት የተናገሩት። እያንዳንዱ ስራ ጉዳዩ በሚመለከታቸው ባለሙያዎች (proffesionals) እንዲከናወን ተደርጓል።

በኮሌጁ ቤተ-መጽሐፍ ዲጂታላይዜሽን፣ የአውቶሜሽን እና ኤሌክትሮኒክ ሪሶርስ ክፍል ኃላፊዋ ወ/ሪት ሕይወት እንደሚያስረዱት፤ ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂን በመጠቀም ዘመናዊ የአውቶሜሽንና ዲጂታላይዜሽን ሲስተሞችን በመተግበር የተቀላጠፈ አገልግሎት መስጠት የጀመረው ከ2009 ዓ.ም በኋላ ባለው ጊዜ ነው።

የኮሌጁ ቤተ- መጽሐፍትና ዶክመንቴሽን አገልግሎት ዳይሬክተር አቶ ዓለማየሁ ብሥራት “ቤተ- መጽሐፉን እዚህ ደረጃ ለማድረስ የተቋሙ ኃላፊዎች ያላሰለሰ ጥረት አድርገዋል” ይላሉ። የቤተ-መጽሐፍ ሳይንስ ባለሙያዎች ጊዜያቸውንና ጉልበታቸውን በማፍሰስ

የኮሌጁ ቤተ- መጽሐፍትና ዶክመንቴሽን አገልግሎት ዳይሬክተር አቶ ዓለማየሁ ብሥራት



63



64

በኃላፊነት እንደመሩት፣ አጋር ተቋማትም ትልቅ ተሳትፎ ማድረጋቸውን አቶ ዓለማየሁ ያስታውሳሉ።

በተደረገው ማሻሻያም የተጠቃሚዎች አገልግሎት፣ የቴክኒካል ፕሮሰስ፣ ኤሌክትሮኒክ ሪሶርስ እንዲሁም የምርምር፣ ማማከርና ስልጠና የኮሌጁ ቤተ-መጽሐፍት የስራ ሂደቶች እንዲኖሩት ተደርጓል። የአንባቢያን አገልግሎት የስራ ሂደት በስሩ የሰርኩሌሽን፣ ሪፈረንስ፣ ፔሬዲካልስ፣ ቡክ ስቶር እና የቤተ-መጽሐፍ ደህንነት (ሴኩሪቲ) የስራ ክፍሎችን ይዟል።

የቴክኒካል ፕሮሰሲንግ የስራ ሂደት የካታሎጊንግና ክላሲፊኬሽን፣ የአኩዚሽን እንዲሁም የጥረዛና ፎቶ ኮፒ፣ የስራ ክፍሎች ያሉት ሲሆን፤ ዲጂታይዜሽን፣ የአውቶሜሽን እና ኤሌክትሮኒክ ሪሶርስ አገልግሎት የስራ ሂደት በስሩ ዲጂታይዜሽን፣ የዲጂታል ቤተመጽሐፍት (ኮምፒውተር ላብ) እና ሪፕሮግራፊ አገልግሎት ክፍሎች አሉት።

የኮሌጁ ቤተ-መጽሐፍ የሕክምና ሳይንስ የመረጃ ውጤቶችን በማሰባሰብ የኢንፎርሜሽን ኮሙዩኒኬሽን ቴክኖሎጂን በመጠቀም በተገቢው መንገድ በማደራጀትና በማቆየት ተገልጋዮች በራሳቸው መጠቀም እንዲችሉ በማብቃት ተደራሽነታቸውን ማረጋገጥ ተልዕኮው አድርጓል።

የመረጃ ክምችቱንም ለማሳደግ የሕክምና መጽሐፎችን፣ መጽሔቶችን፣ ጆርናሎችን፣ ሲዲ፣ የመመረቂያ ጽሑፍ (ቴሲስ)፣ የመሳሰሉትን የህትመት ውጤቶችን እና በሶፍት ኮፒ እያሰባሰበ ይገኛል። ቤተ-መጽሐፉ ለሌሎች የሕክምና ሳይንስ ተቋማት ቤተ-መጽሐፍቶች ሞዴል የመሆን ራዕይ ሰንቆ በመስራት ላይ ነው።

ከዘመኑ ጋር አብሮ ለመዘመን … የቤተ-መጽሐፍቱ ተጠቃሚዎች በዋናነት የኮሌጁ ቅድመ ምረቃና ድህረ ምረቃ ተማሪዎች ናቸው። የሆስፒታሉ የአካዳሚክና የአስተዳደር ሰራተኞች እንዲሁም ተመራማሪዎችም በቤተ-መጽሐፉ ይገለገላሉ። ከሌሎች የትምህርት ተቋማት የሚመጡ ተማሪዎችና ተመራማሪዎችም በልዩ ፈቃድ የሚስተናገዱበት አሰራርም አለ።

በኮሌጁ የሁለተኛ ዓመት ተማሪዋ የአብስራ ሰውመሆን የቤተ-መጽሐፉ አገልግሎት አሰጣጥም ሆነ የመጽሐፍቱ ስብስብ ጥሩ እንደሆነ ነው የምትገልጸው። ለ24 ሰዓት አገልግሎት መሰጠቱም ተማሪው በተመቸው እና በሚስማማው ሰዓት እንዲያነብ ዕድል ያገኛል ትላለች።

ቤተ-መጽሐፉ የመማር ማስተማር፣ የምርምርና የሕክምና ስራውን ለማሳለጥ አጋዥ ኃይል በመሆኑ ዘወትር የ24 ሰዓት አገልግሎት ይሰጣል። ቤተ-መጽሐፉን በቀን በአማካይ እስከ 300 ተጠቃሚዎች ይጎበኙታል። በዓመት በአማካይ መቶ ስምንት ሺህ (108,000) ጊዜ ተጠቃሚዎች ይስተናገዱበታል እንደማለት ነው።

አንባቢያኑ መጽሐፍትን ተውሰው ለአጭር ጊዜ ማንበብ፣ እንዲሁም ለረጅም ጊዜ ተውሰው በመውሰድ መጠቀም ወይም ከቤተ-መጽሐፍቱ ዳታቤዝ አውርደው ማንበብም ሆነ ለራሳቸው ማስቀረት የሚችሉባቸው አሰራሮች መዘርጋታቸውን ነው አቶ አለማየሁ የሚናገሩት።

ከተገልጋዮች አንዷ የሆነችው የአብስራ “ዲጂታል ቤተ- መጽሐፍ መኖሩ ከዘመኑ ጋር ለመጓዝ ያስችላል” ብላለች።

ከኮሌጁ የሁለተኛ ዲግሪውን ዘንድሮ የሚያገኘው መልካሙ ጌታነህ እንደሚናገረው፤ በቤተ መጽሐፉ አገልግሎት አሰጣጥ ደስተኛ ነው። ችግር ሲያጋጥምም ፈጣን መፍትሔ ይገኛል።

የሕትመት ውጤት የሆኑ መጽሐፎቹ KOHA Integrated Library Management System በሚባል የአውቶሜሽን አሰራር ነው የተደራጁት። የዲጂታይዜሽን፣ የአውቶሜሽን እና ኤሌክትሮኒክ ሪሶርስ ክፍል ኃላፊዋ እንደገለጹት፤ ይህን አሰራር የቤተ መጽሐፉን ተጠቃሚ መረጃ ለመመዝገብ፣ ለማዋስና ለመመለስ፣ ለካታሎጊንግና ክላሲፊኬሽን፣ እንዲሁም ስታትስቲካል መረጃዎችን ለማግኘት እና ለተመሳሳይ ስራዎች ይገለገሉበታል።

ይህ አሰራር “ተጠቃሚዎችን Online Public Access Catalogue (http://197.156.83.155/) አድራሻ ላይ በቤተ-መጽሐፉ ያሉትንና የሌሉትን መጽሐፎች መረጃ ባሉበት ሆነው ለማወቅ ይረዳል” ሲሉ የገለጹት ወ/ሪት ሕይወት ናቸው። የመለያ ቁጥራቸውን (Call Num- ber) በማግኘት፣ መጽሐፎቹ የት እንዳሉ ስለሚያሳይ

በቀላሉ አገልግሎት ማግኘት ይቻላል። ብዛታቸውን ለማወቅ፣ በውሰት ላይ ያለ መሆን አለመሆኑን እንዲሁም የመጽሐፎቹን ዝርዝር መረጃ ለማየትም ይጠቅማል። ስለሆነም ይህ አሰራር በቤተ-መጽሐፉ የሚሰጠውን አገልግሎት ቀላል፣ ቀልጣፋ እና በትክክለኛ መረጃ ላይ የተመሰረተ እንዲሆን ያስቻለ ነው።

የዲጂታል ቤተመጽሐፉ ክምችት “Greenstone Digital Library Software” በመጠቀም እንዲደራጅ ተደርጓል። ከ10‚000 የሚበልጡ በየጊዜው የሚያድጉ የሕክምና የዲጂታል መጽሐፎችን ይዟል። መጽሐፍቱ በ25 ዋና ዋና የሕክምና ትምህርት ዘርፎች የተደራጁ ናቸው። እነዚህን መረጃዎች በጳውሎስ ካምፓስ ኔትዎርክ ውስጥ ብቻ ሆኖ ነው መጠቀም የሚቻለው።

ከዚህ ባሻገር የHINARI, PubMed, Clinical Key, Up To Date - Most Trusted Clinical Decision Sup- port Tool እና ሌሎችም ኦንላይን ጆርናሎችን፣ ዳታ ቤዞችን ለመጠቀም የሚያስችል የስምምነት ውሎችና የተቋም የተለየ የተጠቃሚ ስያሜና የይለፍ ቃል (User Name & Password) መኖሩን የሚያስረዱት የቤተ- መጽሐፉ ኃላፊ ናቸው።

እነዚህ የምርምርና የመረጃ ውጤቶች በአብዛኛው በወቅታዊና ተአማኒነት ባላቸው የሕክምና መረጃዎች ላይ በመመስረት የተዘጋጁ ናቸው። ይህም በመሆኑ መረጃዎቹን ሐኪሞችም ሆኑ ተማሪዎች የሕክምና ውሳኔ ለመስጠትና የታካሚዎችን ሁኔታ ለማሻሻል እንዲሁም የትምህርትና ምርምር ስራውን ለመደገፍ ይጠቀሟቸዋል።

“የዲጂታል ክምችቱ አገልግሎት በጊዜ እና በቦታ ምክንያት እንዳይገደብ፤ የመጽሐፍትና ተማሪ ቁጥር ጥምርታ ላይ ለሚያጋጥመው ችግር እልባት ሰጥቷል” ይላሉ የቤተመጽሐፉ ኃላፊ። የአምስተኛ ዓመት የሕክምና ተማሪ የሆነው እስከአጥናፍ ዮሴፍ በዲጂታል ቤተ- መጽሐፉ ያሉት መረጃዎች ከሚሰጡት ትምህርቶች ጋር በቀጥታ ተያያዥነት እንዳላቸው ገልጿል።

በዲጂታል ቤተ-መጽሐፉ የሚገኙትን 220 ኮምፒዩተሮች ተገልጋዮች ፈጣን የኢንተርኔት አገልግሎት ለማግኘትና መረጃዎችን (ሶፍት ኮፒ) ለማንበብ ይጠቀሙባቸዋል። ይህን አስመልክቶ በኮሌጁ የስድስተኛ ዓመት የሕክምና ተማሪ የሆነው ወጣት ልዑልሰገድ ኃብቴ ሲገልጽ፤ “የበይነ መረብ ግንኙነት (internet connection) መረጃዎችን ቶሎ አውርዶ ለመጠቀም አስችሎኛል” ብሏል። የኮሌጁ የትምህርት ክፍሎች በዲጂታል ቤተ-መጽሐፉ አማካኝነት ለተማሪዎቻቸው ፈተና ይሰጣሉ፤ በተጨማሪም በአገር አቀፍ ደረጃ ለሚዘጋጁት ፈተናዎች በማዕከልነትም እያገለገለ ነው።

እንደቤተ-መጽሐፉ ዳይሬክተር ገለጻ፤ ከስዊዘርላንድ የተገዙ ሁለት ግዙፍ የዲጂታል ስካነር ማሽኖች መኖራቸው ቤተ-መጽሐፉን ከሌሎች አቻ ተቋማት ልዩ ያደርገዋል። ማሽኖቹን በመጠቀም መጽሐፎችን ወደ

በሕዝብ ገንዘብ የሚሰሩ የምርምር

መረጃዎችን ለመያዝና ለማቆየት

የሚያገለግል Dspace ሶፍትዌር

በመጠቀም ለማደራጀት በሂደት

ላይ ነው እንደ ዳይሬክተሩ ገለጻ።

የምርምር ውጤቶቹን በአግባቡ

ለመጠቀም የሚያስችል ፖሊሲ

እንዲኖር ጥረት እየተደረገ እንደሆነ

ከተቋሙ የተገኘው መረጃ

ያመላክታል።



65

ሶፍት ኮፒ በመቀየር፣ ሶፍት ኮፒውን ወደ ዲጂታል ሰርቨር በመጫን ለተጠቃሚዎች አገልግሎት እንዲውሉ ለማድረግ እየተከናወነ ያለው ተግባር በመልካም የሚታይ ነው።

በሕዝብ ገንዘብ የሚሰሩ የምርምር መረጃዎችን ለመያዝና ለማቆየት የሚያገለግል Dspace ሶፍትዌር በመጠቀም ለማደራጀት በሂደት ላይ ነው እንደ ዳይሬክተሩ ገለጻ። የምርምር ውጤቶቹን በአግባቡ ለመጠቀም የሚያስችል ፖሊሲ እንዲኖር ጥረት እየተደረገ እንደሆነ ከተቋሙ የተገኘው መረጃ ያመላክታል።

የቤተ-መጽሐፉን ንብረት እንዲሁም የተጠቃሚዎቹንም ደህንነት ለማረጋገጥ ብሎም ምቹ የማንበቢያ አካባቢ ለመፍጠር በቀጣይ ዓመታት የRFID Library man- agement system እና ሰርቪላንስ ካሜራ ቴክኖሎጂ ለመተግበር እየተሰራ መሆኑን ኃላፊው ጠቁመዋል።

ልቆ ለመገኘት … በአገራችን የተለመደ አባባል አለ፤ ‘ሰው አፉን ሲከፍት፣ ውስጡ ይታያል’ የሚል። ሰውን ውስጣዊ እሳቤውን፣ አመለካከቱን እና ብስለቱን፣ እምነቱን እና አቋሙን ወዘተ … በንግግሩ ሁናቴ መመዘን እንደሚቻል ቀደም ሲል የተጠቀሰው ኢትዮጵያዊ ብሂል ያስረዳል። በዚህ ረገድ ብዙውን ጊዜ ንግግራቸው የማይጠገብ እና በሀሳባቸው በተመስጦ ውስጥ የሚከቱንን ሰዎች ልማድ መለስ ብለን ብንመለከት አብዛኛውን ጊዜያቸውን መጻሕፍትን በማንበብ እንደሚያሳልፉ በእርግጠኝነት መግለጽ ይቻላል።

የሚያነብ ሰው አስተሳሰቡ የበሰለ፣ አስተዋይ፣ ነገሮችን በሁሉም አቅጣጫ የሚመለከት ነው። ትላንትን የኋልዮሽ እንዲመለከት፣ ዛሬን እንዲመረምር፣ ነገንም አሻግሮ እንዲመለከት ጓደኞቹ የሆኑት መጽሐፍት መንገድ

ይመሩታል። በንባብ ልምድ፣ ዕውቀትና ብልሃት ይገበያል።

የሚያነብ ሰው ጠለቅ ያለ ዕውቀት ይኖረዋል፣ በየጊዜውም ራሱን ያሳድጋል። ከመጻሕፍት የሚያገኘውን ዕውቀት ምክንያታዊ ሆኖ ይመረምራል። በንግግሩም በመረጃ የተደገፈ ሀሳብን ያንጸባርቃል። በማንበብ ክህሎቶቻችንን እናሳድጋለን፣ ልምድ እናገኛለን፣ ሀሳባችንን ለሰዎች እናካፍላለን። የዕውቀት ማዕዱም ማዕከል ቤተመጽሐፍት ናቸው።

የንባብ ባሕል ባልዳበረበት ሁኔታ ሰፊ ግንዛቤ ያለውን ባለሙያ ማፍራት አዳጋች ይሆናል። በቂ መጽሐፍትን ሳያነቡ፣ ሁለገብ እውቀት ሳይኖራቸው ወደ ስራ መሰማራታቸው አሉታዊ ተጽዕኖ ማሳደሩ ሳይታለም የተፈታ ነው። ሁነኛ መፍትሔውም የመማር ማስተማር ሂደቱን በመፈተሽ የማስተካከያ እርምጃ መውሰድ ነው።

ተማሪ የአብስራ የንባብ ባሕልን ለማዳበር ከልጅነት ጀምሮ ቢሰራ፣ የትምህርት ተቋማት እና ቤተሰብ ለዚህ ትኩረት ቢሰጠው መልካም ነው ትላለች። ማንበብ ልምድ በመሆኑ በልጅነት እያደገ የሚመጣ እንጂ ድንገት የሚከሰት አይደለም ስትል ታክላለች። ይህ ልማድ ለማዳበር መጽሐፍትን በማቅረብ፣ ለማንበብ የሚረዱ ምቹ ሁኔታዎችን በማመቻቸት ጭምር ታዳጊ ሕፃናትን ማበረታታት እንደሚገባም ትመክራለች።

ተማሪዎች መጽሐፎችን እንዲያነቡ የሚያስችሉ ስልቶች በመማር ማስተማር ሂደቱ ላይ ማካተት ያስፈልጋል። የማንበብ ባሕልን ለማሳደግ ጉልህ አስተዋጽኦ ያላቸውን ቤተ-መጽሐፍት የመጠቀም ልምምዱን ማዳበር የሚያስችሉ ስራዎችን መከወን ያስፈልጋል።

ጊዜው የዲጂታል ዘመን እንደመሆኑ የምናነበው ርዕሰ ጉዳይ በመጽሐፎች ወይም በመጽሔት በህትመት ብቻ የሚገኝ አይደለም። እጅግ ብዙ የሆኑ መጣጥፎች በተለያዩ

የኢንተርኔት ድረገፆች፣ ዳታቤዞች እና በማኅበራዊ ሚዲያዎች ላይ ተለጥፎ ይገኛል። የተጻፈ ሁሉ እውነት አይደለምና የተጻፈውን ሁሉ ለማንበብ መሞከር አይኖርብንም። ከስራችን ወይም ከትምህርታችንና ከምርምር ስራችን ጋር ግንኙነት ያላቸውን መለየት እና የትኞቹ የመረጃ ምንጮች ጠቃሚ መረጃ እንደሚይዙ ማወቅ ይጠይቀናል። ይህን በማድረጋችን ጊዜያችንን በአግባቡና በቁም ነገር ላይ እንድናሳልፍ ይረዳናል።

የምናነባቸው ጽሑፎች በተለይ ለትምህርትና ምርምር እንዲሁም ለሕክምና ስራ ግብዓትነት የምናውላቸው ከሆነ ጥንቃቄያችንን ጠበቅ ማድረግ ይጠይቀናል። ማነው የጻፈው? መቼ ተጻፈ? የጸሐፊው ትምህርትና ችሎታ እስከምን ደረጃ ነው? የተጠቀመው መረጃ ተአማኒነቱ እንዴት ነው? የጽሑፉ ዓላማ ምንድንነው? ያሳተመው ማነው? እና የመሳሰሉትን ጥያቄዎች መጠየቅና መመለስ፣ በአግባቡ መመርመርና መረዳት ያስፈልጋል ሲሉ የቤተ- መጽሐፉ ዳይሬክተር ይመክራሉ።

ስለሆነም ክቡር የሆነውን የሰውን ልጅ ለማዳን የሚታትሩት የሕክምና ባለሙያዎች በትምህርት ዓለምም ሆነ ወደ ስራ ከተሰማሩ በኋላ ንባብን የሕይወታቸው አንዱ አካል ሊያደርጉ ይገባል። ይህን ልማድ ሲያዳብሩ እውቀት እና ክህሎታቸውን በማሳደግ ልቀው እንዲገኙ መንገድ ይከፍታል። በውጤቱም ከዘመኑ ጋር አብሮ ለመዘመን ብሎም የሰውን ልጅ ሕመም እና ስቃይ በመቀነስ መንፈሳዊ እርካታን መሸመት ይቻላል።

በኮሌጁ በትምህርት ላይ ያሉ ተማሪዎች፣ መምህራን እና ባለሙያዎች በቤተ-መጽሐፉ ያሉትን ፈርጀ ብዙ መረጃዎች በማንበብ ክህሎታቸውን እንዲያዳብሩ፣ የአስተሳሰብ አድማሳቸውን እንዲያሰፉ የሚያስችሉ የእውቀት ማዕዶች መሆናቸውን ቤተ-መጽሐፉ በልበ ሙሉነት እየገለጸ ነው።



66

ኢኮኖሚ



67

የሴቶች እና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ከኢዜአ ጋር በመተባበር የተዘጋጀ

የሁሉንም ትኩረት የሚሻው

የጾታ ጥቃት

በፍቅርተ ባልቻ

የሰው ልጅ የሚወለደው በጾታ፣ በሃይማኖት ወይም በመሳሳለው ልዩነት ኖሮት አይደለም። በምድር ላይ ያለው የሰዎች አኗኗር ግን ይህን ሁኔታ ይቀይረዋል። አንዱ የበላይ ሌላው የበታች፣ አንዱ ፈላጭ ቆራጭ ሌላው የጥቃት ሰለባ እንዲሆን ይገደዳል። ይህም የሕይወትን ሚዛን ያጋደለ ያደርገዋል።

በርካታ ጥናቶች በተዛባ የሕይወት ዘይቤ፣ እሳቤ እና ድርጊት ለጥቃት ተጋላጭ የሚሆኑ የሕብረተሰብ ክፍሎችን በመለየት በየጊዜው ይፋ እያደረጉ ነው። በተለይ ሴቶች፣ ሕፃናት፣ አረጋዊያን እና አካል ጉዳተኞች ጥቃት ከሚደርስባቸው የሕብረተሰብ ክፍሎች ውስጥ ናቸው። ጥቃቱ ከአገር አገር፣ ከአህጉር አህጉር ደረጃው ቢለያይም ዓለም አቀፍ ገጽታ ያለው ድርጊት ነው።

በሴቶች እና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር የሴቶች ግንዛቤ ንቅናቄ ባለሙያ የሆኑት አቶ ደስታው ገበያው ጥናቶችን ዋቢ አድርገው እንደሚገልጹት፤ በዓለማችን ካሉ ሦስት ሴቶች አንዷ በቅርብ ሰው አካላዊ ወይም ጾታዊ ጥቃት ይደርስባታል። ባለሙያው አያይዘውም እ.ኤ.አ በ2017 የተሰራን ጥናት ዋቢ አድርገው በዓለም ዙሪያ ታስቦበት 87 ሺህ ሴቶች መገደላቸውን በመረጃነት ይጠቅሳሉ። ከእነዚህም መካከል 58 በመቶው በቅርብ አጋሮች ወይም የቤተሰብ አባላት ለሕልፈተ ሕይወት ተዳርገዋል። ይህም የሚያሳየው 137 ሴቶች በዓለም ላይ በየቀኑ በቤተሰብ አባሎቻቸው እንደሚገደሉ ነው። በዓለም ላይ 15 ሚሊዮን የሚሆኑ ታዳጊ ሴቶች አስገድዶ መድፈር ይደርስባቸዋል። ከሚደርሱ ጾታዊ ትንኮሳዎች 20 በመቶው ብቻ ሪፖርት ይደረጋሉ።



68

በሴቶች ላይ በአብዛኛው ጥቃት የሚፈጸመው በፍቅረኞቻቸው እና በትዳር አጋሮቻቸው ነው። ስድብ፣ ድብደባ፣ ያለፍላጎት የግብረስጋ ግንኙነት መፈጸም (አስገድዶ መድፈር) ከጥቃቶቹ መካከል መሆናቸውን የጠቀሰው World Savvy Monitor ‘Global Status of Women’ በሚል ርዕስ እ.ኤ.አ 2009 ይፋ ያደረገው ሰነድ ነው። ሰነዱ አያይዞም ከሦስት ሴቶች መካከል አንዷ በፍቅረኛዋ አልያም በትዳር አጋሯ ከላይ የተጠቀሱት ጥቃቶች እንደሚደርስባት አመላክቷል።

የስታትስቲክስ ኤጀንሲ (Gender Statistics Report) እ.ኤ.አ በ2017 የስርዓተ ጾታ ሪፖርት እንደሚያመለክተው፤ በአገራችን ከ15 እስከ 49 የዕድሜ ክልል ውስጥ ካሉ ሴቶች 23 በመቶው አካላዊ ወይም ጾታዊ ጥቃት ገጥሟቸዋል። በትዳር ውስጥ ካሉት ሴቶች አራት በመቶው በአጋሮቻቸው ጥቃት ደርሶባቸዋል። ሪፖርቱ እንዳረጋገጠው በተጠቀሰው ዕድሜ ክልል ካሉት 63 በመቶው ሴቶች በባሎቻቸው አልያም በፍቅረኞቻቸው ድብደባ ይፈጸምባቸዋል።

በኢትዮጵያ የሴቶችን የአካል ክፍሎች (ሰውነት) መንካት፣ መቆንጠጥ፣ መደብደብ እንደወንጀል አይቆጠርም ሲል Closing the Gender Gap በሚል ርዕስ Global Ma- jority E-Journal, Vol. 11, June 2020) አስነብቧል። በአገሪቷ ገጠራማ አካባቢዎች ያሉ ወንዶች ይህንን ልምዳቸውን ወደ ከተሞች ሲሔዱም እንደሚያንጸባርቁ ነው ያመላከተው። በሌላ በኩል ደግሞ “የአስገድዶ መድፈርን ወንጀል ለፖሊስ ሪፖርት ማድረግ እንግዳ ተግባር ነው” ይላል ጽሑፉ።

አስገድዶ መድፈርን ጨምሮ ጾታዊ ጥቃቶች በፍትሕ አካላት ዘንድ በተገቢው መንገድ አይስተናገዱም። አካላዊ ጥቃት እና ወሲባዊ ትንኮሳዎችን ሪፖርት የሚያደርጉት ሴቶች ይፌዝባቸዋል፤ አልያም ጉዳያቸው ‘ውሃ አያነሳም’ በሚል ወደ ጎን ይባላል። በአገራችን ሴቶች በአደባባይ - በጠራራ ፀሀይ የጥቃት ሰለባ ሲሆኑ መስማት እና ማየት የተለመደ ተግባር ነው።

የጥቃቱ ምንነት አንድ ሰው በሕይወት ለመኖር፣ ደኅንነቱ እንዲጠበቅ፣ ሰብዓዊ ክብሩ እንዳይነካና በአካልና በአእምሮ ጤናማ ሆኖ ለመኖር ያሉትን መብቶች የሚጎዳ ተግባር መፈጸም በጥቅሉ ጥቃት እንለዋለን። ጥቃቱ ሰዎች ኃይልን፣ ሥልጣንን ወይም አቅምን ያለአግባብ በመጠቀም ራስን ከማጥፋት ጀምሮ ሆን ብለው ራሳቸውን እንዲጎዱ የሚያደርጓቸውን ተግባሮችንም ያካትታል።

ጾታን መሰረት ያደረገ ጥቃት በተዛባ የስርዓተ ጾታ ግንዛቤ እና አስተሳሰብ ምክንያት በተለያየ መንገድ በሴቶች፣ በሕፃናት እና በወንዶች ላይ ይፈጸማል። ጥቃቱ በሁሉም

ጾታ እና ዕድሜ ክልል ውስጥ ባሉ ሰዎች ላይ ሊፈጸም ይችላል። ጾታዊ ጥቃት በአብዛኛው የሚፈጸመው በሕፃናት፣ በአካል ጉዳተኞች፣ በኢኮኖሚ ዝቅተኛ በሆኑ የሕብረተሰብ ክፍሎች፣ የቤት ውስጥ ሰራተኞች ላይ ነው።

በሴቶች እና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር የሴቶች ግንዛቤ ንቅናቄ ባለሙያ አቶ ደስታው እንደሚገልጹት፤ ጾታዊ ጥቃት ተጎጂውን/ዋን ሰው ሙሉ በሙሉ በመቆጣጠር ወይም ኃይልን በመጠቀም የሚፈጸም ተግባር ነው። ጥቃቱ የግለሰቦችን ነፃነት በመንፈግ ጾታን መሰረት ያደረገ አካላዊ፣ ስነ ልቦናዊና ኢኮኖሚያዊ ጉዳት የሚያስከትል፣ ማስገደድን፤ ማሰቃየትን፣ በቤተሰብ ወይም በሕብረተሰብ ደረጃ ነጻነት ማሳጣትን ያካተተ የኃይል ተግባር ነው።

ጾታን መሰረት ያደረገ ጥቃት በብዛትና በስፋት በሴቶች ላይ ነው የሚፈጸመው፤ ይህም በመሆኑ ጾታዊ ጥቃት በሴቶች ላይ የሚፈጸም ጥቃት ተብሎ ነው የሚጠራው። የዚህ ጽሑፍ ማጠንጠኛም በሴቶች ላይ የሚፈጸመው ጾታዊ ጥቃት ነው።

በሴቶች ላይ የሚፈጸሙ ጥቃቶች ንብረት ወይም ሀብት እንዳያፈሩ እና በንብረታቸው እንዳያዙ ማድረግን፣ የባለቤትነት መብታቸውን በመንፈግ እንዲሁም ለሰሩት ስራ ተገቢውን ክፍያ ባለመፈጸም በጥገኝነት እንዲኖሩ ማድረግን ይጨምራል።

ሌላኛው የጥቃቱ ገጽታ በማንኛውም መንገድ በአካል ላይ የሚፈጸም የኃይል ጥቃት ወይም አካላዊ ጥቃት ነው። ይህ ጥቃት መምታት፣ መገፍተር፣ መተንኮስና እስከነፍስ ማጥፋት ያሉትን ያጠቃልላል።

ወሲባዊ ጥቃት ኃይልን በመጠቀም በሌላ ሰው ላይ ያለፍላጎት የሚፈጸም ማንኛውም ዓይነት የወሲብ ድርጊትን የመሰሉ ለመልካም ጸባይ ተቃራኒ የሆኑ ድርጊቶችና ትንኮሳዎችን ያካትታል። አስገድዶ መድፈር፣ ጾታዊ ትንኮሳና የመሳሰሉት ድርጊቶች ከወሲባዊ ጥቃት መገለጫዎች መካከል ናቸው። ጾታን መሰረት በማድረግ ሆን ተብሎ የሴቶችን ሞራልና ስሜታቸውን በሚጎዳ መልኩ በማዋረድና በማሸማቀቅ የሚፈጸም የስነ ልቦና ጥቃትም የጾታዊ ጥቃት አካል ነው።

ጾታዊ ጥቃት ለምን እንደተባባሰ መጠየቅ ወደ መፍትሔው ለማምራት የሚረዳ መንገድ ነው። የሴቶች እና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር እንደሚገልጸው፤ ጾታዊ ጥቃትን ለመፈጸም ከሚያነሳሱ ምክንያቶች ውስጥ በማሕበረሰቡ ዘንድ ያሉ እሳቤዎች እና አሉታዊ ማኅበራዊ ወጎች ትልቁን ድርሻ ይይዛሉ።

“የባል በትር ትክክል ነው” ብሎ ማመን፣ ሚስትን በቁጥጥር ስር የማድረግ ልማዶች በትዳር ውስጥ ባሉ ሴቶች ላይ ለሚፈጸሙት ጥቃቶች መንስኤዎች ናቸው። ሕብረተሰቡ ስለስርዓተ ጾታ ያለው ግንዛቤ አናሳ መሆንም ተያይዞ

የሚነሳ ነጥብ ነው። የሴቶች ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ አቅማቸው የዳበረ አለመሆኑ ሌላው ምክንያት ነው።

ጥቃት የተፈጸመባቸው ሴቶች ለተለያዩ ውስብስብ አካላዊ አዕምሯዊ እንዲሁም ለተላላፊ በሽታዎች፣ ላልተፈለገ እርግዝና፣ የስነ ተዋልዶና ወሲባዊ የጤና ችግሮች እና ለሞት ይጋለጣሉ። በጥቅሉ የስነ ልቦናና፣ ማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ ችግሮች ይገጥሟቸዋል። በጥቃቶቹ ሳቢያ ጤናቸውን ለመጠበቅ፣ ሰርተው ለመግባት፣ በማኅበራዊ ጉዳዮች ለመሳተፍ፣ ራሳቸውን በትምህርትም ሆነ በሌላ መንገድ ለማሳደግ እንደሚቸገሩ የስታትስቲክስ ኤጀንሲ መረጃ ያመላክታል።

በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ በጦርነት ወቅት ሴቶች እና ሕፃናት ለደኅንነታቸው ከለላ የሚያደርጉላቸው የቤተሰብ አባላት በአካባቢው ስለማይኖሩ ተጋላጭ የመሆን ዕድላቸው ይበልጥ ይጨምራል። በግጭት ወቅት ጾታዊ ጥቃትን መፈጸም የጦር ወንጀል እንደሆነም ዓለም አቀፍ የጦር ሕግ ይደነግጋል።

ይህን ወደ ጎን ያለው አሸባሪው የህወሓት ቡድን በሰሜኑ የአገራችን ክፍል መውረሩን ተከትሎ እጅግ ዘግናኝ በሆነ መልኩ ጾታዊ ጥቃቶች በስፋት ሲፈጽም መቆየቱ ገሃድ ከወጣ ሰነባብቷል። ጦርነቱ በሴቶች ላይ ተጨማሪ ጫና አሳድሯል። ቡድኑ ወረራ በተፈጸመባቸው አካባቢዎች ንጹሐን ዜጎችን በጅምላ ገድሏል፤ የማኅበራዊ አገልግሎትና የመሠረተ ልማቶች ወድመዋል።

“ወረራ በተፈጸመባቸው አካባቢዎች ያሉ ሴቶች ለጥቃትና ለችግር ተጋልጠዋል። ድርጊቱ ከፍተኛ የስነ ልቦና ጫና አሳድሮባቸዋል። ከትምህርት ቤት መውጣት፣ የጤና አገልግሎት ማጣትና ለአስከፊ ስቃይና ሞት መዳረግ እጣ ፋንታቸው ሆኗል። የውሃ እና የኤሌክትሪክ ኃይል አቅርቦት አለመኖር ለተጨማሪ ልፋቶችና የጤና ችግሮች አጋልጧቸዋል” ሲሉ የሁኔታውን አስከፊነት የጠቀሱት በሴቶች እና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር አማካሪዋ ወ/ሮ ጽጌ ታደለ ናቸው።

ጥቃት ፈጻሚዎቹን ተጠያቂ ለማድረግ እንዲሁም ተጠቂዎች የሚያጋጥማቸውን ማኅበራዊ፣ የስነ ልቦናዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና መሰል ችግሮችን እንዲቋቋሙ ማስቻል የሴቶች እና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴርን ኃላፊነት እጥፍ ድርብ አድርጎታል።

የሴቶች እና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር እንደሚገልጸው፤ በአሸባሪው የህወሓት ቡድን ጾታዊ ጥቃት ለተፈጸመባቸው ሴቶች ድጋፍ ለማድረግ ከጤና ሚኒስቴር፣ የአዕምሮ ሐኪሞች እና የዘርፉ ማሕበራት ጋር በመሆን እየሰራ ነው። ጥቃት ፈጻሚዎችን ተጠያቂ ከማድረግ አኳያ ከፍትሕ መዋቅር ጋር በቅርበት እየሰራ ይገኛል። ከተለያዩ አካላት



69

በሴቶች ላይ የሚፈጸሙ ጥቃቶች ንብረት ወይም

ሀብት እንዳያፈሩ እና በንብረታቸው እንዳያዙ ማድረግን፣ የባለቤትነት መብታቸውን በመንፈግ

እንዲሁም ለሰሩት ስራ ተገቢውን ክፍያ

ባለመፈጸም በጥገኝነት እንዲኖሩ ማድረግን

ይጨምራል።



70

ሀብት በማሰባሰብ ለተጎጂዎቹ የማድረስ ተግባር የድጋፉ አካል ነው። የወደሙ ቢሮዎችን መረጃ በማሰባሰብ መልሶ ለማቋቋም ጥረት እየተደረገ ነው።

ድንጋጌዎች ምን ይላሉ? ጾታዊ ጥቃት በአብዛኛው በሴቶች ላይ የሚፈጸም ጥቃት ነው። ጥቃቱ በዓለም አቀፍ ደረጃ የሰብዓዊ መብት ጥሰት ከሚባሉት ተርታ የተመደበ ነው። ጾታዊ ጥቃትን ለመከላከል የተዘጋጁ ዓለም አቀፍ የሕግ ማዕቀፎች ውስጥ ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ድንጋጌ (UDHR) ይገኝበታል። The Convention on the Elimination of All Forms of Discrimination፣ Against Women - CEDAW ሌላው ድንጋጌ ነው። ማፑቶ ፕሮቶኮል (Acts or Threats of Violence in Both the Private and Public Spheres, in peace time as well as during armed conflict) ከማዕቀፎች አንደኛው ነው።

ኢትዮጵያ የሴቶችን መብቶችን ለማስጠበቅ የተዘጋጁ ዓለም አቀፍ እና አህጉራዊ ስምምነቶችን ተቀብላ አጽድቃለች። ከእነዚህም ውስጥ Convention on the Elimination of Discrimination against Women, and the Protocol to the African Charter on the Rights of Women in Africa ይገኙበታል።

የኢፌዴሪ ሕገመንግሥት በአንቀጽ 9 ንዑስ አንቀጽ 4 ኢትዮጵያ ያጸደቀቻቸው ዓለም አቀፍ ስምምነቶች የአገሪቷ ሕግ አካል ናቸው ይላል። በአንቀጽ 35 አንቀጽ (3) ሴቶች በፖለቲካዊ፣ በማኅበራዊ እና በኢኮኖሚያዊ መስኮች እንዲሁም በመንግሥት እና በግል ተቋሞች ውስጥ ከወንዶች እኩል ተወዳዳሪ እና ተሳታፊ መሆን እንዳለባቸው ተደንግጓል።

አገራችን የሴቶችን መብቶች ለማስጠበቅ በርካታ የሕግ ማዕቀፎችን እና ፖሊሲ አዘጋጅታ ስራ ላይ እንዲውሉ አድርጋለች። በኢትዮጵያ ያለውን የሕግ ማዕቀፍ ዝግጅት አስመልክቶ አቶ ደስታው ሲያብራሩ፤ የተሻሻለው የቤተሰብ ሕግ፣ የመንግሥት ሰራተኛ አዋጅ 1064፣ የአሰሪና ሰራተኛ አዋጅ 1156 ዋነኞቹ ናቸው።

በተሻሻለው የወንጀል ሕግ አንቀጽ 620 አስገድዶ የደፈረ ከ5 ዓመት እስከ ዕድሜ ልክ እስራት እንደሚቀጣ ደንግጓል። በአንቀጽ 626፣ ዕድሜያቸው ከ13 በላይና ከ18 ዓመት በታች በሆኑ ሕፃናት በፈቃዳቸውም ቢሆን ግብረ ስጋ ግንኙነት ያደረገ ከ3 እስከ 25 ዓመት ጽኑ እስራት ይቀጣል ይላል። እነዚህ ድንጋጌዎች ጾታዊ ጥቃት የሚፈጽሙ አካላትን ሕግ ፊት አቅርቦ ተጠያቂ ለማድረግ ከተዘጋጁ የሕግ ማዕቀፎች መካከል እንደሆኑ የገለጸው በሴቶች እና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር የሴቶች፣ ግንዛቤ፣ ንቅናቄ፣ ተሳትፎ፣ ማስፋፊያ ዳይሬክቶሬት ነው።



71

የክንውኑ ከፊል ገጽ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የሴቶች ጥቃት መልኩን እየቀየረና አፈጻጸሙም ውስብስ እየሆነ፣ ይባስ ብሎም ጥቃቱ በቤተሰብ ውስጥ እና የትዳር አጋር ጭምር እየተፈጸመ መምጣቱ “የመከላከል ስራውን አዳጋች አድርጎታል” ይላል የሴቶች እና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር።

ስለሆነም ጥቃቱን መከላከል፣ ከተፈጸመም በኋላ የድርጊቱን ፈጻሚዎችና ተባባሪዎች ተጠያቂ ለማድረግ ዘርፈ ብዙ ተግባራትን ማከናወን ያስፈልጋል። መንግሥት ለችግሩ ትኩረት በመስጠት ተፈጻሚ እንዲሆን የሚያስችሉ አደረጃጀት እና አሰራሮችን አበጅቷል። የሕግ ማዕቀፎችን ማዘጋጀት አንደኛው እና ቀዳሚው ተግባር ነው። ሕጎቹን ወደ መሬት አውርዶ ተፈጻሚ ለማድረግ በፌዴራል እና ክልል ደረጃ የሴቶችን ጉዳይ የሚከታተሉ ቢሮዎች ተቋቁመው ወደ ስራ እንዲገቡ መደረጉ ሌላው ክንውን ነው።

ሕግ የማስከበር ኃላፊነት የተሰጠው ፖሊስ የሴቶችን ጥቃት በትኩረት እንዲከታተል በየፖሊስ ጣቢያው ጭምር መዋቅር ተሰርቶለታል። በፍርድ ቤቶችም ቢሆን በልዩ ሁኔታ ጾታዊ ጥቃትን የሚመለከቱ ችሎቶች እንዲቋቋሙ ጥረት መደረጉን የስታትስቲክስ ኤጀንሲ ጥናት (CSA 2016, Ethiopia Demographic and Health Survey) ጠቁሟል።

የፖሊስ ዩኒቨርሲቲ በሚሰጠው የፖሊስ መኮንኖች ስልጠና የሴቶች ጥቃት መከላከልን በማካተት ችግሩን በሁሉም ክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች ምርመራውን ውጤታማ ለማድረግ ልዩ አስተዋጽኦ እንዲያበረክት ከስምምነት ተደርሷል ብሏል ሚኒስቴሩ።

የሴቶች እና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር እንደሚገልጸው በአገራችን እየተፈጸሙ ያሉ ጾታዊ ጥቃቶች መንስኤ የተዛባ የስርዓተ ጾታ አረዳድ ነው። በተለይ በትዳር ውስጥ ባሉ ሴቶች ላይ የሚፈጸሙትን ጥቃቶችን ማሕበረሰቡ እንደወንጀል አለመቁጠሩ ድርጊቶቹ እንዲስፋፉ የሚያደርግ አንዱ ምክንያት ነው። ጥቃቶቹ ወንጀል መሆናቸውን የሚደነግጉ ሕጎች መውጣታቸውና ያሉትም እንዲሻሻሉ መደረጉ ይህን እሳቤ ለመቀየር የራሱ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው እሙን ነው።

ሚኒስቴሩ የተዛቡ አመለካከቶችን ለማረቅ ሰፊ የግንዛቤ ማስጨበጫ ተግባራትን እያከናወነ ነው። በአገር ሽማግሌዎች፣ በሃይማኖት አባቶች እና በባለድርሻ አካላት በጥምረት እየተደረገ ያለው የግንዛቤ ማስጨበጥ እንቅስቃሴም የሚጠቀስ ነው።

ጥቃት የፈጸመ ሰው ጉዳይ በተራ የወንጀል ሕግ ከመታየቱና ፍርድ ከማግኘቱ ባሻገር ቀሪ ሕይወቱን በማኅበራዊ አገልግሎቶች እንዳይሳተፍ የሚያደርግ

ብሔራዊ የጥቃት አድራሾች ምዝገባ ስርዓት እንዲዘረጋ በአስር ዓመቱ መሪ ዕቅድ ተይዞ እየተሰራ ነው።

የአንድ መስኮት እና የተሃድሶ አገልግሎት መስጫ ተቋማት እንዲቋቋሙና ተደራሽ እንዲሆኑ ተሰርቷል። ጥቃት ተፈጽሞ ሲገኝ ድርጊቱ የተፈጸመባቸው ሴቶች ለተጨማሪ የጤና እክል እንዳይጋለጡ የጤና፣ የሕግ፣ የስነ ልቦና እና ሌሎች ተያያዥ ጉዳዮችን በአንድ ቦታ አገልግሎት እንዲያገኙ የአንድ መስኮት አገልግሎት በሆስፒታሎች ተቋቋሞ አገልግሎት እየተሰጠ ነው።

የሴቶች ግንዛቤ እና ንቅናቄ ባለሙያው አቶ ደስታው ማንዋሎች መዘጋጀታቸው ውጤት ለማምጣት እንደሚያግዙ አመላክተዋል። እንደ አቶ ደስታው ገለጻ፤ የማሕበረሰቡ ንቃተ ሕሊና በማደጉ ጥቃት ፈጻሚዎችን ወደ ሕግ የማቅረብ እንቅስቃሴዎች ተጀምረዋል። ሴቶች መብታቸውን የመጠየቅና የማስከበር አቅማቸውን አሳድገዋል። የጾታዊ ጥቃትን የተመለከቱ ጥቆማዎች እየቀረቡ መሆኑ ማሕበረሰቡ በጾታዊ ጥቃት ላይ ያለው ግንዛቤ ለማደጉ አመላካች ነው።

የቤት ስራዎቻችን … ሚኒስቴሩ ከጾታዊ ጥቃት ጋር በተያያዘ የያዛቸው ውጥኖች እና የቀጣይ የትኩረት አቅጣጫዎችን አስቀምጧል። ተቋሙ የሴቶችን አካላዊ፣ ወሲባዊ፣ ስነ ልቦናዊ ጥቃቶች ለመከላከል ግንዛቤ ለመፍጠር በትኩረት ይሰራል። የተዘረጋውን የወሲባዊ ጥቃት ወንጀል አድራሾች ብሔራዊ መረጃ ስርዓት (National Sex Offenders Registration System) ተግባራዊነት ይከታተላል። የተጠናከረ የተሃድሶ መስጫ ማዕከላት ጥምረት (Network) ማስፋፋት ሌላው የቤት ስራ ነው።

ሴቶች ጥቃት ሲደርስባቸውና ለጥቃት ተጎጂ ከመሆናቸው በፊት የማሳወቂያ መስመሮች (Hotline service) እንዲዘረጉ ክትትል ይደረጋል። የጸረ ጾታዊ ጥቃት ግብረ ኃይል ማጠናከር ወሳኝ ነው። የሕግ አፈጻጸም ሂደቱን

መከታተልና ማስፈጸም በዋናነት የፍትሕ ሚኒስቴር የቤት ስራ ነው።

ሴቶች በቤት ውስጥ የሚደርስባቸውን ጾታዊ ጥቃቶች ለመከላከልና ፍትሕ ለማግኘት የሚያስችላቸውን ምቹ ሁኔታዎች ማመቻቸት ያስፈልጋል። ጾታዊ ጥቃቶችን ለመከላከልና ለማስወገድ የሚረዱ ሁሉን አቀፍ የሆኑና ማኅበረሰቡን መሰረት ያደረጉ የግንዛቤ ማስጨበጫ ንቅናቄዎችን ማከናወን ያሻል። ጥቃት የደረሰባቸው ሴቶች ወደ ፍትሕ አካላት እንዲሄዱ ሕብረተሰቡ ኃላፊነቱን እንዲወጣ የሚያስችሉ አሰራሮችን ማበጀት እና እንዲያውቃቸው መስራት ይጠይቃል።

በቂ ገቢ የሌላቸው ሴቶች ነፃ የሕግ ከለላና የድጋፍ አገልግሎት እንዲያገኙ ማመቻቸት፣ እንዲሁም በሴቶች ላይ ለሚፈጸሙ የጾታ ጥቃቶች አስተማሪ የሆኑ የቅጣት እርምጃዎች እንዲወሰዱ ማድረግ ተገቢ ነው።

የተለያዩ ጥቃቶች የተፈጸሙባቸው ሴቶች ሁሉን አቀፍና የተቀናጀ ድጋፍና እንክብካቤ እንዲሁም የማገገሚያ አገልግሎት የሚሰጡ ተቋማትን ማስፋፋትና ማጠናከር፣ ጥቃት የደረሰባቸው ሴቶች ቀልጣፋ እና ፍትሃዊ ውሳኔ እንዲያገኙ መስራት ይገባል። በፍትሕ አሰጣጡ ላይ ሕግን የሚያዛቡ የፍትሕ አካላት ተጠያቂ የሚሆኑበትን አሰራር ለማጠናከር ሚኒስቴሩ በትኩረት ይንቀሳቀሳል።

ከባለድርሻ አካላት ጋር ቅንጅታዊ አሰራርን በማጎልበት የተጠናከረ ስራ መስራት ይጠይቃል። ጾታዊ ጥቃትን በተመለከተ ሚና ያላቸው ባለድርሻ አካላት እንቅስቃሴያቸውን ማስፋት እና ተሳትፏቸውን ማሳደግ ይኖርባቸዋል።

ሲጠቃለል እያንዳንዱ ግለሰብ ጾታዊ ጥቃትን ከራሱ ጀምሮ በመከላከል ማሕበረሰቡን ማስተማር፣ መረጃ መስጠት፣ ድጋፍ ማድረግ ሲችል የሚያስከትለውን ጉዳት ለመግታት የሚደረገው ጥረት ስኬታማ ይሆናል።



72

ሴቶች

እንመርመር፤ እንከተብ! ጤና ሚኒስቴር ከኢዜአ ጋር በመተባበር የተዘጋጀ



73

እንመርመር፤ እንከተብ! ኮቪድ-19 በዓለም አቀፍ ደረጃ በወረርሽኝ መልክ ከተከሰተበት ጊዜ ጀምሮ በዓለም አቀፍ ደረጃ

ማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ፣ ሥነ ልቦናዊ እና ሌሎች ተዛማጅ ችግሮችን እያደረሰ ይገኛል። የዓለም ጤና ድርጅት ከኮቪድ-19 ጋር በተያያዘ አገሮች ቁጥጥርና ክልከላዎች እያላሉ መምጣታቸውን ተከትሎ የኮቪድ-19 ወረርሽኝ አሁንም የወቅቱ አሳሳቢ የጤና ስጋት መሆኑን እየገለጸ ይገኛል።

ወረርሽኙ ከተከሰተ ሁለት ዓመት ያለፈው ቢሆንም እስከ አሁን በሽታውን የሚፈውስ መድኃኒት ማግኘት አልተቻለም። በዚህም አገሮች የኮቪድ-19 ሥርጭትን ለመከላከል፣ ለመቆጣጠርና የሚያስከትለውን ጉዳት ለመቀነስ ዜጎቻቸውን ማስከተብ ቀዳሚ ምርጫቸው አድርገዋል። የኮቪድ-19 ሥርጭትን ለመግታት የቅድመ ጥንቃቄ መከላከያ መንገዶችን ተግባራዊ ከማድረግ ቀጥሎ ዋነኛውና ቁልፍ መከላከያ መንገድ ክትባት እንደሆነ የዘርፈ ባለሙያዎች ይመክራሉ። ክትባቱ የበሽታውን ስርጭት ከመቀነስና ከመግታት ባሻገር በሽታው የከፋ ጉዳት አድርሶ ሰዎች ለአካል ጉዳትና ለሞትም እንዳይደርሱ ያለውን ሂደትም ይቀንሳል።

የዓለም አገሮች ውጤታማነታቸው በሳይንሳዊ መንገድ ተፈትሸው የተረጋገጡ የኮቪድ-19 ክትባቶች ለዜጎቻቸው በመስጠት ላይ ሲሆኑ እስከአሁን ከአጠቃላይ የዓለም ሕዝብ 63 ነጥብ 1 በመቶ የሚሆነው ቢያንስ አንድ ጊዜ እንደተከተበ ከዓለም ጤና ድርጅት የተገኘ መረጃ ያሳያል። የበለጸጉ አገሮች ዜጎቻቻውን ለመከተብና ሁሉንም ለማዳረስ ጥረት እያደረጉ ሲሆን፤ በአንጻሩ የለጋሽ አገሮችንና ተቋማትን እጅ ከመጠበቅ ውጭ በራሳቸው ገዝተው

መንገሻ ገ ⁄ ሚካኤል



74

ሆነ አምርተው ዜጎቻቸውን መከተብ የማይችሉ የአፍሪካ አገሮች የኮቪድ-19 ክትባት ተደራሽነታቸው በጣም አነስተኛ ነው። የምዕራባዊያን አገሮች ዜጎች ከግማሽ በላይ ተከትበው የተቀሩት እየተጠባበቁ ሲሆን፤ የአፍሪካ አገሮች ሙሉ ለሙሉ ክትባቱን የወሰዱ ሰዎች ከ12 ከመቶ እንደማይበልጥ ከአፍሪካ በሽታ መቆጣጠርና መከላከል ማዕከል የተገኘ መረጃ ያሳያል።

ኢትዮጵያም ወረርሽኙን ለመግታትና ለመቆጣጠር ጉልህ ሚና ይኖራቸዋል ተብሎ የተገመቱና በዓለም አቀፍ ደረጃ ውጤታማነታቸው በሳይንሳዊ መንገድ የተረጋገጡ ክትባቶችን ወደ አገር ውስጥ በማስገባት ለኅብረተሰቡ መስጠት ከጀመረች 11 ወራት አስቆጥራለች። ክትባቶቹ በሁለት መልክ እየተሰጡ ነው። የመጀመሪያው መደበኛ በሆነ መልኩ በየጤና ጣቢያዎች የሚሰጥ ሲሆን፤ ሁለተኛው ደግሞ በዘመቻ መልክ የሚሰጥ ነው። በዚህም ኢትዮጵያ በመጀመሪያው ዙር በአፍሪካ አህጉር የመጀመሪያ የኮቪድ-19 በሽታ መከላከያ ክትባት ዘመቻ በማካሄድ አምስት ነጥብ አምስት ሚሊዮን ዜጎችን በአጭር ጊዜ መከተብ እንደተቻለ ከጤና ሚኒስቴር የተገኘ መረጃ አመላክቷል። በተለይም የጤና ባለሙያዎችን እና የሌሎች ተጋላጭ ተቋማት ሰራተኞች ከስራ ባህሪያቸው አኳያ ቅድሚያ ክትባቱን እንዲወስዱም ተደርጓል።

ኢትዮጵያ የኮቪድ-19 መከላከያ ክትባት መስጠት ከጀመረችበት መጋቢት 4 ቀን 2013 ዓ.ም ጀምሮ እስከ አሁን ድረስ ከ10 ሚሊዮን በላይ ሰዎች እንደተከተቡ የሚያሳየው የጤና ሚኒስቴር መረጃ የኮቪድ-19 ክትባት የወሰዱ ሰዎች ቁጥር ወደ 20 ሚሊዮን ከፍ ለማድረግ ያለመ ሁለተኛ ዙር ዘመቻም እየተካሄደ ነው።

ሁለተኛው ዙር የኮቪድ-19 ክትባት ዘመቻ በአገር አቀፍ ደረጃ ከየካቲት 07 ቀን 2014 ጀምሮ 2ኛ ዙር የኮቪድ-19 መከላከያ ክትባት እየተሰጠ ይገኛል። በጤና ሚኒስቴር የእናቶችና የሕፃናት ጤና እንዲሁም የስርዓተ ምግብ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ዶክተር መሰረት ዘላለም እንደሚሉት የኮቪድ-19 መከላከያ ክትባት እንደ አገር ላለፉት 11 ወራት ሲሰጥ የቆየ ቢሆንም በሚጠበቀው ደረጃ ብዙ ሰው ክትባቱን ማግኘት አልቻለም።

ክትባቱ በዘመቻ መልኩ መስጠት ያስፈለገውም “ተደራሽነቱን ለማስፋትና ዜጎቻችንን ለመታደግ ነው” ይላሉ።

መንግሥት በተከታታይ ክትባቶችን ወደ አገር ውስጥ በማስገባት ክትባቱ ለኅብረተሰቡ ተደራሽ ለማድረግ ጥረት ሲያደርግ የቆየ ቢሆንም አገሪቷ ካላት የሕዝብ ቁጥር አንፃር አፈጻጸሙ አነስተኛ በመሆኑ የዘመቻ ስራውን ማከናወን አስፈልጓል።

“እንደ አገር እጃችን ላይ በከፍተኛ መጠን ክትባት አለን” የሚሉት ዶክተር መሰረት፣ ይህን ክትባት መከተብ ላለባቸው ዜጎች በፍጥነት ተደራሽ ለማድረግ በዘመቻ መልኩ ማከናወን አስፈላጊ መሆኑን ነው የገለጹት።

ከዘመቻው ጎን ለጎን ማኅበረሰቡ የበሽታ መከላከል እርምጃዎችን ተግባራዊ እንዲያደርግ የጤና ባለሙያዎች “ግንዛቤ የመፍጠር ስራዎች ይሰራሉ፣ ለሕፃናት የሚሰጠው መደበኛ የክትባት መርሃ ግብር ስራዎችም ይቀጥላሉ” የሚሉት ዶክተር መሰረት፤ ኮቪድ-19 መከላከያ ክትባት በዘመቻ መስጠታችን ስራዎችን በፍጥነት አጠቃሎ ወደ

ሌሎች ስራዎች ትኩረት ለማድረግ ይረዳልም ባይ ናቸው።

ባለፈው ታህሳስ በተካሄደው የመጀመሪያው ዙር ዘመቻ አምስት ነጥብ አምስት ሚሊዮን ዜጎችን ተደራሽ ማድረግ የተቻለ ሲሆን፤ በዚህ ዘመቻ ከ20 ሚሊዮን በላይ የሚሆኑ ሰዎችን ለማድረስ ታቅዷል። በሁለተኛው ዙር ዘመቻ ላይ ከ20 ሚሊዮን በላይ የሚሆኑ ክትባቶች በየክልሎቹና በየከተሞች አስተዳደር የተሰራጩ ሲሆን፤ ክትባቱም የሚሰጥባቸው ቦታዎች በጤና ጣቢያዎችና ሕዝብ በብዛት በሚሰበሰብባቸው ጊዜያዊ የክትባት መስጫ ጣቢያዎች ነው።

በዚህ ዘመቻ ክትባቱን የሚወስዱ ዕድሜያቸው 12 ዓመትና ከዚያም በላይ የሚሆናቸውና ከዚህ በፊት የኮቪድ-19 ወረርሽኝ መከላከያ ክትባት ያልወሰዱ፣ እንዲሁም ዕድሜያቸው 12 ዓመትና ከዚያም በላይ ሆነው፣ ከዚህ በፊት የኮቪድ-19 መከላከያ የአንደኛውን ዶዝ ክትባት ወስደው ሁለተኛው ዶዝ የመውሰጃ ጊዜያቸው የደረሰው ነው። ከዚህም ሌላ ዕድሜያቸው 12 ዓመትና ከዚያም በላይ ሆኖ፣ ከዚህ በፊት ሁለቱንም ክትባቶች ሙሉ ለሙሉ ወስደው ስድስት ወራት የሞላቸው ቡስተር ዶዝ ክትባትን መውሰድ ይችላሉ። ከዚህ በፊት ጆንሰን ኤንድ ጆንሰን ክትባትን አንድ ጊዜ ብቻ የወሰዱ ሰዎች እንደ ሌሎቹ ክትባት የወሰዱ ሰዎች ስድስት ወራት መጠበቅ ሳይገባቸው፣ ከሦስት ወራት ጀምሮ ቡስተር ዶዝ መውሰድ ይችላሉ። በሁለተኛው ዙር ዘመቻ እየተሰጡ ያሉት ክትባቶች ጆንሰን ኤንድ ጆንሰን፣ ፋይዘርና ሲኖፋርም እንደሆነ ከጤና ሚኒስቴር የተገኘ መረጃ ያመላክታል።

ዶክተር መሰረት የክትባቱ አወሳሰድ በተመለከተ ሲያስረዱ ከዚህ በፊት አስትራዜኒካ የወሰዱ ሰዎች ፋይዘር መውሰድ እንደሚችሉና በፊትም ፋይዘር የወሰዱ ፋይዘር ፤ ሲኖፋርም የወሰዱ ሲኖፋርም፤ ጆንሰን የወሰዱ ጆንሰን ወስደው እንደሚጨርሱ አመላክተዋል። ሁለተኛው ዙር የኮቪድ መከላከያ ክትባት ዘመቻ ከመጀመሪያው ለየት የሚያደርገው የማጠናከሪያ ክትባት የሚሰጥበት በመሆኑ ነው። በመጀመሪያውና በሁለተኛው ዙር ሌላ ክትባት ከወሰዱ በሦስተኛው ዙር የፋይዘር ክትባትን እንዲወስዱ የሚመከር ሲሆን፤ የማጠናከሪያ ክትባቱን ሲወስዱ ከጤና ባለሙያዎች ጋር ተመካክረው በሚሰጣቸው የምክር አገልግሎት አማካኝነት መሆን እንዳለበትም ዶክተር መሰረት ያስረዳሉ።

በሁለተኛው ዙር ኮቪድ መከላከያ ክትባት ዘመቻ ከአገሪቷ የጸጥታ መደፍረስ ጋር ተያይዞ ከቤት ንብረታቸው የተፈናቀሉ የኅብረተሰብ ክፍሎች ተደራሽ የሚያደርግ ነው። በመጀመሪያው ዙር ዘመቻ “በተለያዩ የአገሪቷ ክፍሎች ጦርነት በመኖሩ በተወሰኑ በሰሜን የአገሪቷ ክፍል ክትባት መስጠት አልተቻለም” የሚሉት ዶክተር መሰረት፤ በአሁኑ ዘመቻ በእነዚህ አካባቢዎች ለሚገኙ ወገኖች ተደራሽ ለማድረግ እየተሰራ ነው ብለዋል። በተለይ በመጠለያ ውስጥ ያሉ ዜጎች ተደራሽ ለማድረግ



75

በጤና ሚኒስቴር የእናቶችና የሕፃናት

ጤና እንዲሁም የስርዓተ ምግብ

ዳይሬክተር ዶክተር መሰረት ዘላለም

አንድ ጊዜ ብቻ የሚሰጥ የጆንሰን ክትባት በስፋት መሰራጨቱን ነው የገለጹት። “በትግራይ ክልል ክትባቱን ለዜጎች ተደራሽ ለማድረግ ከመንግሥት ጋር ከሚሰሩ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት አካላት በትብብር እየተሰራ ነው” ብለዋል።

የኮቪድ -19 መከላከያ ክትባት እና የተዛቡ አመለካከቶች

በዓለም አቀፍ ደረጃ የኮቪድ-19 ክትባት በተፈለገው መጠን እንዳይሰጥ እንቅፋት ከሆኑ ምክንያቶች መካከል ሰዎች ለክትባቱ ያላቸው የተዛባ አመለካከት ዋነኛው ነው። የኮቪድ ክትባት መውሰድ ቫይረሱን ለመከላከል ከፍተኛ ጠቀሜታ እንዳለውና ያልተከተቡት ሰዎች ከተከተቡት አኳያ የመሞት ዕድላቸው በ11 ዕጥፍ እንደሚጨምር በምርምር የተረጋገጠ ቢሆንም፤ ይህ ሳይንሳዊ ግኝት የማይቀበሉ ሰዎች ቁጥር ቀላል አይደለም።

ሰዎች ክትባቱን ላለመከተብ የሚያቀርቡት ምክንያት የተለያየ ቢሆንም የሁሉም ምክንያቶች ተመሳሳይ የሚያደርገው ምንም ዓይነት ሳይንሳዊ ማስረጃ የሌላቸው መሆኑ ነው። የበለጸጉ አገሮች ዜጎች ክትባቱ የጎንዮሽ ጉዳት ያስከትላል የሚሉ ሲሆኑ፤ አፍሪካን የመሳሰሉት ያላደጉ አገሮች ዜጎች ክትባቱ የድሃው ቁጥር ለመቀነስ ታስቦ የተዘጋጀ ነው የሚል ጥርጣሬ አላቸው። በዓለም ታሪክ “የኮቪድ ክትባትን ያህል ተቃውሞ ያስተናገደ ክትባት የለም” የሚሉ የዘርፉ ባለሙያዎች ለዚህም መገናኛ ብዙኀን በክትባቱ ዙሪያ የሚያሰራጩትን የተሳሳቱ መረጃዎች ተጠያቂ ያደርጋሉ።

በአገራችንም ክትባቱ በጥርጣሬ ዓይን የሚመለከቱ ሰዎች ቁጥር ከፍተኛ ነው። ከኮቪድ-19 ክትባት ጋር በተያያዘ በርካታ የሐሰት ትርክቶች በተለያዩ የማኅበራዊ መገናኛ መድረኮች ላይ ሲሰራጩ ይታያል። በዚህ ምክንያትም በኅብረተሰቡ ዘንድ ክትባቱ የደም መርጋት ያስከትላል፣ የሕዝብ ቁጥር ለመቀነስ ታስቦ የመጣ ነው። እንዲሁም “የእግዚአብሔር ቁጣ ስለሆነ በጸሎት እንጂ በክትባት አይድንም” የሚሉ የተለያዩ የተዛቡ አመለካከቶች ይንጸባረቃሉ።

በኮቪድ-19 መከላከያ ክትባት ዙሪያ የሚነሱ “አሉባልታዎች ተገቢነት የላቸውም” የሚሉት ዶክተር መሰረት ማንኛውም ዓይነት መድኃኒት ሆነ ክትባት የራሱ የጎንዮሽ ጉዳት እንደሚኖረው በማስታወስ ነው። የኮቪድ ክትባት ቢሆንም ከዚህ የተለየ ነገር የለውም። አብዛኞቹ የጎንዮሽ ጉዳቶች ክትባቱን ከተከተቡ በኋላ ባሉት የመጀመሪያዎቹ ቀናት ውስጥ የሚከሰቱ ሲሆን፤ ከጥቂት ቀናት በኋላ የሚጠፉ ናቸው።

የማንኛውም ክትባት ውጤታማነት የሚለካው “ከምርት ጀምሮ ጥቅም ላይ እስኪውል ድረስ ባለው ሂደት ነው” የሚሉት ዶክተሯ፤ የኮቪድ ክትባት ውጤታማ የሚሆነው ያልተቆራረጠ የማቀዝቀዣ ሰንሰለት አልፎ ከመጣ መሆኑንም ያስረዳሉ። ክትባቱ ከምርት ጀምሮ ለሕዝብ እስኪዳረስ ቀዝቃዛ በሆነ ቦታ መቀመጥ ይኖርበታል።

የቅዝቃዜ ሰንሰለቱ ጠብቆ ያልመጣ ክትባት እና ባልሰለጠኑ ባለሙያዎች የሚሰጥ ክትባት የከፋ የጎንዮሽ ጉዳት ስለሚያስከትል የጤና ሚኒስቴር የክትባት መርሃ ግብሩ ከመጀመሩ በፊት የክትባቱን አሰጣጥ በተመለከተ ለጤና ባለሙያዎች አስፈላጊውን ስልጠና ሰጥቷል።

የጤና ባለሙያው ክትባቱ ከተመረተበት ጊዜ ጀምሮ ለሰው እስኪሰጥ ድረስ በቀዝቃዛ ሰንሰለት ውስጥ ማለፉን ለማረጋገጥ የሚያስችለው እውቀት እንዲያገኙ ተደርገዋል የሚሉት ዶክተር መሰረት፤ ይህን አልፎ ክትባቱ በሚሰጥበት ጊዜ አላስፈላጊ ችግር ቢከሰት እንኳን ችግሩን በመቀልበስ የሰዎችን ሕይወት መታደግ የሚቻልበት ስልጠና እንዲካተት መደረጉን ይናገራሉ።

የጤና ሚኒስቴር የኮቪድ ክትባት በጥራት እና በፍጥነት ለኅብረተሰቡ ተደራሽ ለማድረግ ከተለያዩ ባለድርሻ አካላት በቅንጅት እንደሚሰራ የሚናገሩት ዶክተር መሰረት፤ ከእነዚህ ባለድርሻ አካላት መካከል የተለያየ ሳይንሳዊ እውቀት ያላቸው ስብስብ የሆነ የጤና አማካሪ ግብረ ኃይል ዋነኛው ነው። ይህ ግብረ ኃይል ክትባቱ ወደ አገር ውስጥ ከመግባቱ በፊት ዓለምአቀፍና አህጉራዊ ተሞክሮዎችን በመተንተን ለጤና ሚኒስቴር ሳይንሳዊ ምክር የሚሰጥ ሲሆን፤ በዚህም በክትባቱ ዙሪያ የሚነሱ የጥራት ጥያቄዎች ሆነ ጎንዮሽ ጉዳት ለመቅነስ የሚያስችል ነው።

በኮቪድ - 19 ወረርሽኝ ሆነ መከላከያ ክትባቱ ዙሪያ ማኅበረሰቡን ውዥንብር ውስጥ የሚያስገቡ ትክክለኛ ያልሆኑ መላምቶችና የተሳሰቱ መረጃዎች ለማጥራት የጤና

ሚኒስቴር ከእምነት ተቋማት እና የሃይማኖት አባቶች ጋር በጥምረት እየሰራ ይገኛል።

ዶክተር መሰረት እንደሚናገሩት፤ የኮቪድ-19 ክትባት መውሰድ ከየትኛውም እምነት ጋር የሚጋጭ ነገር አይደለም። የሃይማኖት አባቶች ምዕመናን ክትባቱን እንዲወስዱ ማስተማር ይጠበቅባቸዋል። መገናኛ ብዙኀን እና የማኅበረሰብ አንቂዎችም በክትባቱ ዙሪያ የማኅረሰቡን ግንዛቤ ከፍ የማድረግ ኃላፊነት አለባቸው።

ክትባት እና ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ በአሁኑ ጊዜ አገሮች ዜጎቻቸው በፍቃደኝነት እንዲከተቡ ከማስተማር አልፈው አስገዳጅ ሕጎች እያወጡ ይገኛሉ። አንዳንድ አገሮች የዜጎቻቸውን ደኅንነት ለመጠበቅ በሚል ምክንያት ያልተከተቡ ዜጎች ምንም ዓይነት ማኅበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ አገልግሎት እንዳያገኙ የሚከለክል ሕግም አውጥተዋል። ኦስትሪያ እና ህንድ የመሳሰሉት አገሮች የክትባት ምስክር ወረቀት የሌላቸው ሰዎች ካፌና ሬስቶራንት ገብተው እንዳይጠቀሙ፣ ከዚህ አልፎ ከስራ ቦታም እስከ ማገድ የሚያስችል ሕግ አውጥተው ተግባራዊ ለማድረግ ተገደዋል።

ታዲያ እነዚህ አገሮች መሰል ሕግ ለማውጣት የተገደዱበት ዋና ምክንያት የወረርሽኙን ስርጭት በመግታት ወረርሽኙ ያስከተለውን የኢኮኖሚ መናጋት ወደ ነበረበት ለመመለስ ያለመ እንደሆነ ሲናገሩ ይደመጣሉ። ክትባት የኮቪድ ወረርሽኝ የሚያስከትለውን ዘርፈ ብዙ ጉዳት ለመቋቋም የተሻለ አማራጭ እንደሆነ ብዙዎች የሚስማሙበት ሀቅ ነው። በዚህም መንግሥታት ከፍተኛ ወጪ በማውጣት ዜጎቻቸውን እያስከተቡ ይገኛሉ።

በአገራችንም የኮቪድ-19 መከላከያ ክትባት እንደ አገር ሽፋን መጨመሩ የወረርሽኙን ስርጭት ከመግታት ባለፈ በማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎች ላይ መነቃቃትን ይፈጥራል። የኮቪድ-19 ክትባት ዘመቻ የወረርሽኙን ስርጭት ለመግታት፣ በሽታን ለመከላከልና ለመቆጣጠር ያስችላል፤ የክትባት ሽፋናችን ሲያድግ የቱሪዝምና ኢኮኖሚያዊ አንቅስቃሴዎች ላይ አዎንታዊ ሚና ይኖረዋል። መንግሥት ይህን ግምት ውስጥ በማስገባት ከፍተኛ በጀት በመመደብ እና ከ80 ሺህ በላይ የሰው ኃይል በማሰማራት ለሁለተኛ ጊዜ የኮቪድ-19 መከላከያ ክትባት በመስጠት ላይ ይገኛል።

“ዜጎችን ከዚህ ወረርሽኝ ለመታደግ የኮቪድ ክትባት ለሁሉም የኅብረተሰብ ክፍል ተደራሽ ማድረግ ያስፈልጋል” የሚሉት ዶክተር መሰረት፤ በተለይም በወረርሽኑ ምክንያት የተቀዛቀዘው የቱሪዝም ዘርፍ ለማነቃቃት ወሳኝ ሚና አለው።

በቅርቡ ”ኢትዮጵያ የአፍሪካ የመሪዎች ጉባኤ ማስተናገድ የቻለችው ቀድማ የክትባት መርሃ ግብር በማስጀመሯ ነው፤ ክትባት ባንሰጥ ኖሮ ማንም ሰው ኢትዮጵያ ውስጥ አይመጣም ነበር” በማለት የኮቪድ ክትባት ለሁሉም



76

ተዳራሽ ማድረግ ቱሪዝሙንም ለማነቃቃት ቁልፍ ሚና እንዳለው ያስረዳሉ። የክትባቱ ዋና ዓላማ ሰዎች በሽታው ከሚያስከትለው ስቃይና ሞት መታደግ ቢሆንም፤ ኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ ስብሰባዎችን እንድታስተናግድ በዕጩነት ስትቀርብ የክትባት ሽፋኑ ዋነኛው መሥፈርት ነው።

ከኮቪድ በፊት ከኢትዮጵያ ለመውጣት የሚፈልግ ሰው የሚጠየቀው ፓስፖርትና ቪዛ ነበር፤ አሁን የመጀመሪያው ጥያቄ የኮቪድ ክትባት ምስክር ወረቀት፤ የኮቪድ የምርመራ ውጤት ሳታሳይ የትኛውም አገር መግባት አይቻልም። ከአገር ብትወጣም ምግብ ለመብላት፣ ትራንስፖርት ለመጠቀም የኮቪድ ምስክር ወረቀት ማሳየት ይጠበቃል። አንዳንድ አገሮች ከበሽታው ስርጭትና ካለመከተብ ጋር ተያይዞ አየር መንገዳቸው ላይ የበረራ እገዳ እያደረጉ ሲሆን፤ ይህም የአቪዬሽን ዘርፉን በእጅጉ እንደሚጎዳው አያጠራጥርም። የኮቪድ ክትባትን መከተብ ከራሳችን አልፎ ለቤተሰባችን ለአገራችን ጠቃሚ በመሆኑ ሁሉም ሰው ክትባቱን እንዲወስድም ይመክራሉ።

ኅብረተሰቡ የኮቪድ-19 የመከላከያ ክትባት ከወሰደ በኋላም ወረርሽኙን ለመከላከል የሚረዱ የመከላከያ ዕርምጃዎችን በመተግበር ረገድ ሊዘናጋ አይገባም። ኅብረተሰቡ የዕለት ተዕለት ስራውን ሳያቋርጥ ማስኮችን መጠቀም፣ በተቻለ መጠን ስብስብን መቀነስ፣ እጅ መታጠብ፣ ስናስነጥስ አፍና አፍንጫን አለመንካት፣ ካስነጠስን በክርናችን አፍና አፍንጫችንን መሸፈን፣ ሰው ፊት ለፊት ላይ አለማስነጠስ የመሳሰሉ የመከላከያ መንገዶች እንደ ባሕል መቀጠል አለባቸው። ይህን ማድረግ ከኮቪድ ባሻገር ከእጅ ወደ አፍ የሚተላለፉና ከመተንፈሻ አካላት ጋር ተያይዘው የሚከሰቱ በሽታዎች ለመከላከል ጭምር ይረዳል።

ለማጠቃለል

በአንዳንድ አገሮች የክትባቱ በስፋት መዳረስን ተከትሎ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በመላው ዓለም በኮቪድ-19 የሚያዙትም ሆነ በዚህ ምክንያት የሚሞቱ ሰዎች ቁጥር የመቀነስ አዝማሚያ ታይቷል። ሆኖም ወረርሽኙ በታዲጊ አገሮች አሁንም አሳሳቢነቱ እንደቀጠለ ነው። ከእነዚህ አገሮች ተርታ የምትሰለፈው አገራችንም በአሁኑ ወቅት ኮቪድ-19 ወረርሽኝ ዋነኛው የኅብረተሰብ ጤና ስጋቷ ሆኖ እንደቀጠለ ነው። ከዚህ እውነታ ለመረዳት የሚቻለው የወረርሽኙን ስርጭት ለመግታትና ለመቆጣጠር የጥናቃቄ እርምጃዎችን ከመውሰድ ባሻገር የክትባት ተደራሽነቱን ማስፋት ወሳኝ እንደሆነ ነው።

የኮቪድ-19 ክትባት የሰውነትን የበሽታ መከላከል አቅምን በማሳደግ በበሽታው የመያዝ እድልን በከፍተኛ ደረጃ ይቀንሳል። መንግሥት ይህን ታሳቢ በማድረግ ክትባቱን ለበርካታ ዜጎቻቸው ለማድረስ እየሰራ ሲሆን፤ ኅብረተሰቡም የኮቪድ-19 ክትባት ዘመቻ የወረርሽኙን ስርጭት ለመግታትና በሽታን ለመከላከልና ለመቆጣጠር ያለው ሚና በመገንዘብ ዘመቻው በውጤት እንዲጠናቀቅ በክትባቱ በንቃት መሳተፍ ይኖርበታል።

“ለራሳችን፣ ለቤተሰባችንና ማኅበረሰባችን ስንል እንመርመር፤ እንከተብ”



77



78

በነጋሪ ቁጥር 19 ‘የአሸናፊዎች ምድር ኢትዮጵያ’ በሚለው ርዕስ ስር ለቀረበው ጽሁፍ የተጠቀምንባቸው እነዚህ ፎቶዎች ከጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት ያገኘነው መሆኑን እናሳውቃለን። ለተፈጠረው ስህተት ዝግጅት ክፍሉ ይቅርታ ይጠይቃል።



79



80




የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም